1. ፍጥረት

እግዚአብሔር ሁሉንም ነገር የፈጠረው እንደሚከተለው ነው፡፡እግዚአብሔር ዓለምንንና በውስጧ የሚገኙትን ነገሮች ሁሉ በስድስት ቀናት ፈጠረ፡፡ እግዚአብሔር ምድርን ከፈጠረ በኋላ ምድር ጨለማና ባዶ ነበረች፤ በውስጧ ምንም ነገር ገና አልተፈጠረም ነበር፡፡ ይሁን እንጂ የእግዚአብሔር መንፈስ በውሆች ላይ ነበር፡፡

ከዚያም እግዚአብሔር ‹‹ብርሃን ይሁን›› አለ ፤ ብርሃንም ሆነ፡፡ እግዚአብሔርም ብርሃኑ መልካም እንደሆነ አይቶ ‹‹ቀን›› ብሎ ጠራው፡፡ እግዚአብሔርም ቀኑን ከጨለማ ለይቶ ጨለማውን ሌሊት ብሎ ጠራው፡፡ እግዚአብሔርም በመጀመሪያው ቀን ብርሃንን ፈጠረ፡፡

በሁለተኛው የፍጥረት ቀን እግዚአብሔር ከምድር በላይ ያለውን ጠፈር በቃሉ ፈጠረ፡፡ በዚህ መንገድ እግዚአብሔር ከጠፈር በለይ ያለውን ውሃ ከጠፈር በታች ካለው ውሃ የሚለይ ሰማይን ፈጠረ።

በሦስተኛው ቀን እግዚአብሔር በቃሉ ውሃውን ከየብሱ መሬት እንዲለይ አደረገ፡፡ እግዚአብሔርም የብሱን መሬት ‹‹ምድር›› ውሃውንም ‹‹ባሕር›› ብሎ ጠራው፡፡ እግዚአብሔርም የፈጠረው ነገር መልካም እንደ ሆነ አየ፡፡

ከዚያም እግዚአብሔር ምድር ሁሉንም ዓይነት ዛፎችንና ተክሎችን ታብቅል አለ፣ እንዲሁም ሆነ፡፡ እግዚአብሔርም የፈጠረው ነገር መልካም እንደ ሆነ አየ፡፡

በአራተኛው የፍጥረት ቀን እግዚአብሔር ፀሐይን፣ ጨረቃንና ክዋክብትን በቃሉ ፈጠረ፡፡ እግዚአብሔርም እነዚህ ለመሬት ብርሃን እንዲሰጡ ቀንና ሌሊትንም ወቅቶችንና ዓመታትንም እንዲለዩ አደረገ፡፡ እግዚአብሔርም የፈጠረው ነገር መልካም እንደ ሆነ አየ፡፡

በአምስተኛው ቀን እግዚአብሔር በውሃ ውስጥ የሚኖሩትንና ወፎችን ሁሉ በቃሉ ፈጠረ፡፡ እግዚአብሔር ያ መልካም እንደ ሆነ አየ፤የተፈጠሩትንም ባረካቸው፡፡

በስድስተኛው ቀን፣ እግዚአብሔር ‹‹ምድር ሁሉንም ዓይነት እንስሳት ታውጣ›› አለ፡፡እነሱም ልክ እግዚአብሔር እንዳለውም ሆኑ፡፡ አንዳንዶቹ የቤት እንስሳት፣ አንዳንዶቹ በምድር የሚሳቡ፣ አንዳንዶቹ ደግሞ የዱር እንስሳት ነበሩ፡፡ እግዚአብሔርም ያ መልካም እንደ ሆነ አየ፡፡

እግዚአብሔር ‹‹ሰዎችን በመልካችን እንደ ምሳሌአችን እንፍጠር እነርሱም በምድርና በእንስሳት ሁሉ ላይ ሥልጣን ይኑራቸው›› አለ፡፡

ስለዚህ እግዚአብሔር ከምድር አፈር ወስዶ ሰው አድርጐ አበጀና የሕይወትን እስትንፋስ በአፍንጫው እፍ አለበት፡፡ የዚህም ሰው ስም አዳም ተባለ፡፡ እግዚአብሔር አዳም የሚኖርበትን የኤደን ገነት አበጀውና ስፍራውን እንዲያለማው እዚያ አስቀመጠው፡፡

በገነትም መካከል እግዚአብሔር ሁለት የተለዩ ዛፎችን ተከለ፤እነርሱም የሕይወት ዛፍና መልካምና ክፉን እንዲያውቁ የሚያስችል የእውቀት ዛፍ ነበሩ፡፡ እግዚአብሔርም አዳምን መልካምንና ክፉን መለየት ከሚያስችለው የእውቀት ዛፍ በቀር በገነት ውስጥ ካለው ከየትኛውም ዛፍ መብላት እንደሚችል ነገረው፡፡ ነገር ግን ክፉውንና መልካሙን እንዲያውቁ ከሚያስችለው ዛፍ ቢበላ እንደሚሞትም ነገረው፡፡

ከዚያም እግዚአብሔር ሰው ብቻውን ይሆን ዘንድ መልካም አይደለም አለ፡፡ ከእንስሳቱ አንዳቸውም የአዳም ረዳት ሊሆኑ አልቻሉም፡፡

ስለዚህ እግዚአብሔር በአዳም ላይ ከባድ እንቅልፍ ጣለበት። አንቀላፍቶም ሳለ ከጐድኑ አንዲት አጥንት ወስዶ ሴት አድርጎ ሠራትና ወደ አዳም አመጣት፡፡

አዳምም ባያት ጊዜ እንዲህ አለ፤ ‹‹ይህችስ እኔኑ ትመስላለች! ስለዚህ ከወንድ ተገኝታለችና ስሟ ሴት ትባል አለ፡፡” (በእብራይስጥ ከኢሽ ተገኝታለችና ስሟ ኢሻህ ትባል ይላል)፡፡ ስለዚህ ሰው አባቱንና እናቱን ይተዋል ከሚስቱም ጋር አንድ ይሆናል፡፡

እግዚአብሔር ወንድና ሴትን በራሱ መልክ ፈጠረ፡፡ እግዚአብሔርም ባረካቸው፤ አላቸውም ‹‹ብዙ ተባዙ፤ ልጆችና የልጅ ልጆችንም ውለዱ ምድርንም ሙሉአት፡፡›› እግዚአብሔርም የሠራው ነገር ሁሉ እጅግ በጣም ጥሩ እንደ ሆነ አየ፡፡ በፈጠረው ነገር ሁሉ ደስ አለው። ይህ ሁሉ በስድስት የፍጥረት ቀናት ሆኑ።

በሰባተኛውም ቀን እግዚአብሔር የመፍጠር ሥራውን ፈጸመ፡፡ ስለዚህ እግዚአብሔር ሲሠራው ከነበረው ሥራ ሁሉ አረፈ፤ ስለዚህ ሰባተኛውን ቀን ባረከው ቀደሰውም፡፡ ምክንያቱም በዚህ ቀን ከሥራው ሥራ ሁሉ አርፏልና፡፡ እግዚአብሔር ሰማይንና ምድርን በውስጣቸውም የሚገኙትን ሁሉ የፈጠረው በዚህ ሁኔታ ነበር፡፡
የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከዘፍጥረት 1-2፡፡