አማርኛ: Open Bible Stories

Updated ? hours ago # views See on DCS

1. ፍጥረት

Image

እግዚአብሔር ሁሉንም ነገር የፈጠረው እንደሚከተለው ነው፡፡እግዚአብሔር ዓለምንንና በውስጧ የሚገኙትን ነገሮች ሁሉ በስድስት ቀናት ፈጠረ፡፡ እግዚአብሔር ምድርን ከፈጠረ በኋላ ምድር ጨለማና ባዶ ነበረች፤ በውስጧ ምንም ነገር ገና አልተፈጠረም ነበር፡፡ ይሁን እንጂ የእግዚአብሔር መንፈስ በውሆች ላይ ነበር፡፡

Image

ከዚያም እግዚአብሔር ‹‹ብርሃን ይሁን›› አለ ፤ ብርሃንም ሆነ፡፡ እግዚአብሔርም ብርሃኑ መልካም እንደሆነ አይቶ ‹‹ቀን›› ብሎ ጠራው፡፡ እግዚአብሔርም ቀኑን ከጨለማ ለይቶ ጨለማውን ሌሊት ብሎ ጠራው፡፡ እግዚአብሔርም በመጀመሪያው ቀን ብርሃንን ፈጠረ፡፡

Image

በሁለተኛው የፍጥረት ቀን እግዚአብሔር ከምድር በላይ ያለውን ጠፈር በቃሉ ፈጠረ፡፡ በዚህ መንገድ እግዚአብሔር ከጠፈር በለይ ያለውን ውሃ ከጠፈር በታች ካለው ውሃ የሚለይ ሰማይን ፈጠረ።

Image

በሦስተኛው ቀን እግዚአብሔር በቃሉ ውሃውን ከየብሱ መሬት እንዲለይ አደረገ፡፡ እግዚአብሔርም የብሱን መሬት ‹‹ምድር›› ውሃውንም ‹‹ባሕር›› ብሎ ጠራው፡፡ እግዚአብሔርም የፈጠረው ነገር መልካም እንደ ሆነ አየ፡፡

Image

ከዚያም እግዚአብሔር ምድር ሁሉንም ዓይነት ዛፎችንና ተክሎችን ታብቅል አለ፣ እንዲሁም ሆነ፡፡ እግዚአብሔርም የፈጠረው ነገር መልካም እንደ ሆነ አየ፡፡

Image

በአራተኛው የፍጥረት ቀን እግዚአብሔር ፀሐይን፣ ጨረቃንና ክዋክብትን በቃሉ ፈጠረ፡፡ እግዚአብሔርም እነዚህ ለመሬት ብርሃን እንዲሰጡ ቀንና ሌሊትንም ወቅቶችንና ዓመታትንም እንዲለዩ አደረገ፡፡ እግዚአብሔርም የፈጠረው ነገር መልካም እንደ ሆነ አየ፡፡

Image

በአምስተኛው ቀን እግዚአብሔር በውሃ ውስጥ የሚኖሩትንና ወፎችን ሁሉ በቃሉ ፈጠረ፡፡ እግዚአብሔር ያ መልካም እንደ ሆነ አየ፤የተፈጠሩትንም ባረካቸው፡፡

Image

በስድስተኛው ቀን፣ እግዚአብሔር ‹‹ምድር ሁሉንም ዓይነት እንስሳት ታውጣ›› አለ፡፡እነሱም ልክ እግዚአብሔር እንዳለውም ሆኑ፡፡ አንዳንዶቹ የቤት እንስሳት፣ አንዳንዶቹ በምድር የሚሳቡ፣ አንዳንዶቹ ደግሞ የዱር እንስሳት ነበሩ፡፡ እግዚአብሔርም ያ መልካም እንደ ሆነ አየ፡፡

Image

እግዚአብሔር ‹‹ሰዎችን በመልካችን እንደ ምሳሌአችን እንፍጠር እነርሱም በምድርና በእንስሳት ሁሉ ላይ ሥልጣን ይኑራቸው›› አለ፡፡

Image

ስለዚህ እግዚአብሔር ከምድር አፈር ወስዶ ሰው አድርጐ አበጀና የሕይወትን እስትንፋስ በአፍንጫው እፍ አለበት፡፡ የዚህም ሰው ስም አዳም ተባለ፡፡ እግዚአብሔር አዳም የሚኖርበትን የኤደን ገነት አበጀውና ስፍራውን እንዲያለማው እዚያ አስቀመጠው፡፡

Image

በገነትም መካከል እግዚአብሔር ሁለት የተለዩ ዛፎችን ተከለ፤እነርሱም የሕይወት ዛፍና መልካምና ክፉን እንዲያውቁ የሚያስችል የእውቀት ዛፍ ነበሩ፡፡ እግዚአብሔርም አዳምን መልካምንና ክፉን መለየት ከሚያስችለው የእውቀት ዛፍ በቀር በገነት ውስጥ ካለው ከየትኛውም ዛፍ መብላት እንደሚችል ነገረው፡፡ ነገር ግን ክፉውንና መልካሙን እንዲያውቁ ከሚያስችለው ዛፍ ቢበላ እንደሚሞትም ነገረው፡፡

Image

ከዚያም እግዚአብሔር ሰው ብቻውን ይሆን ዘንድ መልካም አይደለም አለ፡፡ ከእንስሳቱ አንዳቸውም የአዳም ረዳት ሊሆኑ አልቻሉም፡፡

Image

ስለዚህ እግዚአብሔር በአዳም ላይ ከባድ እንቅልፍ ጣለበት። አንቀላፍቶም ሳለ ከጐድኑ አንዲት አጥንት ወስዶ ሴት አድርጎ ሠራትና ወደ አዳም አመጣት፡፡

Image

አዳምም ባያት ጊዜ እንዲህ አለ፤ ‹‹ይህችስ እኔኑ ትመስላለች! ስለዚህ ከወንድ ተገኝታለችና ስሟ ሴት ትባል አለ፡፡” (በእብራይስጥ ከኢሽ ተገኝታለችና ስሟ ኢሻህ ትባል ይላል)፡፡ ስለዚህ ሰው አባቱንና እናቱን ይተዋል ከሚስቱም ጋር አንድ ይሆናል፡፡

Image

እግዚአብሔር ወንድና ሴትን በራሱ መልክ ፈጠረ፡፡ እግዚአብሔርም ባረካቸው፤ አላቸውም ‹‹ብዙ ተባዙ፤ ልጆችና የልጅ ልጆችንም ውለዱ ምድርንም ሙሉአት፡፡›› እግዚአብሔርም የሠራው ነገር ሁሉ እጅግ በጣም ጥሩ እንደ ሆነ አየ፡፡ በፈጠረው ነገር ሁሉ ደስ አለው። ይህ ሁሉ በስድስት የፍጥረት ቀናት ሆኑ።

Image

በሰባተኛውም ቀን እግዚአብሔር የመፍጠር ሥራውን ፈጸመ፡፡ ስለዚህ እግዚአብሔር ሲሠራው ከነበረው ሥራ ሁሉ አረፈ፤ ስለዚህ ሰባተኛውን ቀን ባረከው ቀደሰውም፡፡ ምክንያቱም በዚህ ቀን ከሥራው ሥራ ሁሉ አርፏልና፡፡ እግዚአብሔር ሰማይንና ምድርን በውስጣቸውም የሚገኙትን ሁሉ የፈጠረው በዚህ ሁኔታ ነበር፡፡

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከዘፍጥረት 1-2፡፡