አማርኛ: Open Bible Stories

Updated ? hours ago # views See on DCS

3. የጥፋት ውሃ

Image

ከረጅም ጊዜ በኋላ ብዙ ሕዝቦች በዓለም ይኖሩ ነበር። እነርሱም በጣም ክፉዎችና አመጸኞች ሆኑ። ክፋትም በጣም ስለበዛ እግዚአብሔር ዓለምን ሁሉ በከባድ የጥፋት ውሃ ለማጥፋት ወሰነ።

Image

ኖኅ ግን በእግዚአብሔር ዘንድ ሞገስን አገኘ። ኖኅ በክፉ ሰዎች መካከል የሚኖር ጻድቅ ሰው ነበር። እግዚአብሔርም በምድር ላይ ሊያመጣ ስላቀደው የጥፋት ውሃ ለኖኅ ነገረው። ኖኅም ግዙፍ መርከብም እንዲሠራ እግዚአብሔር ነገረው።

Image

የመርከቢቱም ርዝመት 140 ሜትር ወርዷ 23 ሜትር ከፍታዋ 13.5 ሜትር ይሁን አለው። ኖኅ የሚሠራት መርከብ ከእንጨት የተሠራች ሆና ባለ ሦስት ፎቅ፤ ብዙ ክፍሎች፤ ጣራና መስኮት ያሉአት ነበረች። መርከቢቱም ኖኅንና ቤተ ሰቡን፣ ሁሉንም ዓይነት የምድር ላይ እንስሳት ከጥፋት ውሃ እንድትጠብቅ ነገረው።

Image

ኖኅም እግዚአብሔርን በመታዘዘ እግዚአብሔር እንደ ነገራው መርከቢቱን ሠራ። መርከቧ በጣም ትልቅ ስለነበረች ለመጨረስ ብዙ ዓመታት ፈጀ። ኖኅ ስለሚመጣው የጥፋት ውሃ ለሕዝቡ እያስጠነቀቀ ወደ እግዚአብሔር እንዲመለሱ ይነግራቸው ነበር፤ ይሁን እንጂ አላመኑትም።

Image

እግዚአብሔር ኖኅንና ቤተ ሰቡን በቂ ምግብ ለራሳቸውና ለእንስሳቱ እንዲያከማቹ አዘዘ። ሁሉም ነገር ዝግጁ በሆነ ጊዜ ለኖኅ፣ ለሚስቱ፣ ለሦስቱ ወንዶች ልጆቹና ለሚስቶቻቸው ወደ መርከቢቱ ለመግባት ጊዜው መድረሱን ነገረው። ስምንት ሰዎችም ወደ መርከቢቱ ገቡ።

Image

እግዚአብሔር ከጥፋት ውሃው እንዲድኑ የሁሉንም ተባእትና እንስት እንስሳት ወፎችንም ጨምሮ ወደ ኖኅ ላከ። ለመሥዋዕት የሚያገለግሉ ሰባት ተባእትና ሰባት እንስት ከሁሉም ዓይነት እንስሳ ወደ ኖኅ መርከብ ላካቸው። ሁሉም ወደ መርከቡ እንደ ገቡ እግዚአብሔር ራሱ የመርከቡን በር ዘጋ።

Image

ከዚያም ዝናቡ መዝነብ ጀመረ፣ ዘነበ፣ ዘነበ፣ ዘነበ ያለማቋረጥ ለ40 ቀንና ሌሊት ዘነበ፣ ከምድርም ምንጭ ይፈልቅ ነበር። በመላው ዓለም ያለው ሁሉም ነገር በውሃ ተሸፈነ፤ ረጃጅም ተራሮች እንኳ ሳይቀሩ በውሃ ተሸፈኑ።

Image

በመርከቡ ከነበሩት ሰዎችና እንስሳት በቀር በምድር ይኖር የነበረ ነገር ሁሉ ሞተ፤ መርከቢቱም በውሃው ላይ ተንሳፍፋ በውስጧ የሚገኙትን ነፍሳት ሁሉ ከሞት አዳነች።

Image

ዝናቡ መዝነቡን ካቆመ በኋላ መርከቢቱ ለአምስት ወራት ያህል በውሃው ላይ ተንሳፈፈች። በዚህም ጊዜ ውሃው መቀነስ ጀመረ። ከዕለታት አንድ ቀን መርከቢቱ በተራራው አናት ላይ አረፈች፤ ይሁን እንጂ ዓለም አሁንም በውሃ ተሸፍና ነበር። ከሦስት ወራት በኋላ የተራሮች ጫፎች መታየት ጀመሩ።

Image

ከአርባ ቀናት በኋላ ኖኅ ውሃው ከምድር ላይ ደርቆ እንደ ሆነ እንዲያይ ቁራ የተባለን ወፍ/አሞራ ላከ። ቁራው እዚህም እዚያም እየበረረ ደረቅ መሬት ቢፈልግም ሊያገኝ አልቻለም።

Image

በኋላም ኖኅ ርግብ የተባለች ወፍ ላከ። ይሁን እንጂ የምታርፍበት መሬት ማግኘት ስላልቻለች ወደ ኖኅ ተመልሳ መጣች። ከሳምንት በኋላ ኖኅ እንደ ገና ርግቧን ላካት። እርሷም የወይራ ቅጠል በአፏ ይዛ ተመለሰች። ውሃው ይቀንስ ስለ ነበር ተክሎችም ደግሞ መብቀል ጀመሩ።

Image

ኖኅ ሌላ አንድ ሳምንት ጠብቆ ርግቢቷን ለሦስተኛ ጊዜ ሰደዳት፤ በዚህ ጊዜ የምታርፍበት ስፍራ ስላገኘች ተመልሳ አልመጣችም። ውሃው እየደረቀ ነበር።

Image

ከሁለት ወራት በኋላ እግዚአብሔር ኖኅን “አንተ ቤተሰብህና እንስሳቱ በሙሉ ከመርከቧ ውጡ። ብዙ ልጆችና የልጅ ልጆችን ወለዱ፤ ምድርንም ሞሉአት” አለ።

Image

ስለዚህ ኖህና ቤተሰቡ ከመርከብ ወጡ ።ኖኅም ከመርከቢቱ ከወጣ በኋላ መሠዊያ ሠራና ከእያንዳንዱ እንስሳ ለመሥዋዕት ሊቀርቡ የሚችሉትን ለእግዚአብሔር መሥዋዕትአቀረበ። እግዚአብሔርም በመሥዋዕቱ ተደሰተ፤ ኖኅንና ቤተ ሰቡን ባረካቸው።

Image

እግዚአብሔርም ‹‹ሰዎች ስለሚያደርጉት ክፉ ነገር ዳግም በጥፋት ውሃ አይጠፉም። ምንም እንኳ ሰዎች ከልጅነታቸው ጀምሮ ክፉዎች ቢሆኑም ዓለምን ዳግመኛ በጥፋት ውሃ አላጠፋም›› አለ።

Image

እግዚአብሔር ለቃል ኪዳኑ ምልክት ይሆን ዘንድ የመጀመሪያውን ቀስተ ደመና ሠራ። ሁልጊዜ ቀስተ ደመናው በሰማይ ላይ ይታያል። እግዚአብሔር በዚህ ቀስተ ደመና አማካይነት ለሕዝቡ የገባውን ኪዳን ያሳታውሳል፤የርሱ ሕዝብም እንዲሁ ያስታውሳል።

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከዘፍጥረት 6-8