3. የጥፋት ውሃ

ከረጅም ጊዜ በኋላ ብዙ ሕዝቦች በዓለም ይኖሩ ነበር። እነርሱም በጣም ክፉዎችና አመጸኞች ሆኑ። ክፋትም በጣም ስለበዛ እግዚአብሔር ዓለምን ሁሉ በከባድ የጥፋት ውሃ ለማጥፋት ወሰነ።

ኖኅ ግን በእግዚአብሔር ዘንድ ሞገስን አገኘ። ኖኅ በክፉ ሰዎች መካከል የሚኖር ጻድቅ ሰው ነበር። እግዚአብሔርም በምድር ላይ ሊያመጣ ስላቀደው የጥፋት ውሃ ለኖኅ ነገረው። ኖኅም ግዙፍ መርከብም እንዲሠራ እግዚአብሔር ነገረው።

የመርከቢቱም ርዝመት 140 ሜትር ወርዷ 23 ሜትር ከፍታዋ 13.5 ሜትር ይሁን አለው። ኖኅ የሚሠራት መርከብ ከእንጨት የተሠራች ሆና ባለ ሦስት ፎቅ፤ ብዙ ክፍሎች፤ ጣራና መስኮት ያሉአት ነበረች። መርከቢቱም ኖኅንና ቤተ ሰቡን፣ ሁሉንም ዓይነት የምድር ላይ እንስሳት ከጥፋት ውሃ እንድትጠብቅ ነገረው።

ኖኅም እግዚአብሔርን በመታዘዘ እግዚአብሔር እንደ ነገራው መርከቢቱን ሠራ። መርከቧ በጣም ትልቅ ስለነበረች ለመጨረስ ብዙ ዓመታት ፈጀ። ኖኅ ስለሚመጣው የጥፋት ውሃ ለሕዝቡ እያስጠነቀቀ ወደ እግዚአብሔር እንዲመለሱ ይነግራቸው ነበር፤ ይሁን እንጂ አላመኑትም።

እግዚአብሔር ኖኅንና ቤተ ሰቡን በቂ ምግብ ለራሳቸውና ለእንስሳቱ እንዲያከማቹ አዘዘ። ሁሉም ነገር ዝግጁ በሆነ ጊዜ ለኖኅ፣ ለሚስቱ፣ ለሦስቱ ወንዶች ልጆቹና ለሚስቶቻቸው ወደ መርከቢቱ ለመግባት ጊዜው መድረሱን ነገረው። ስምንት ሰዎችም ወደ መርከቢቱ ገቡ።

እግዚአብሔር ከጥፋት ውሃው እንዲድኑ የሁሉንም ተባእትና እንስት እንስሳት ወፎችንም ጨምሮ ወደ ኖኅ ላከ። ለመሥዋዕት የሚያገለግሉ ሰባት ተባእትና ሰባት እንስት ከሁሉም ዓይነት እንስሳ ወደ ኖኅ መርከብ ላካቸው። ሁሉም ወደ መርከቡ እንደ ገቡ እግዚአብሔር ራሱ የመርከቡን በር ዘጋ።

ከዚያም ዝናቡ መዝነብ ጀመረ፣ ዘነበ፣ ዘነበ፣ ዘነበ ያለማቋረጥ ለ40 ቀንና ሌሊት ዘነበ፣ ከምድርም ምንጭ ይፈልቅ ነበር። በመላው ዓለም ያለው ሁሉም ነገር በውሃ ተሸፈነ፤ ረጃጅም ተራሮች እንኳ ሳይቀሩ በውሃ ተሸፈኑ።

በመርከቡ ከነበሩት ሰዎችና እንስሳት በቀር በምድር ይኖር የነበረ ነገር ሁሉ ሞተ፤ መርከቢቱም በውሃው ላይ ተንሳፍፋ በውስጧ የሚገኙትን ነፍሳት ሁሉ ከሞት አዳነች።

ዝናቡ መዝነቡን ካቆመ በኋላ መርከቢቱ ለአምስት ወራት ያህል በውሃው ላይ ተንሳፈፈች። በዚህም ጊዜ ውሃው መቀነስ ጀመረ። ከዕለታት አንድ ቀን መርከቢቱ በተራራው አናት ላይ አረፈች፤ ይሁን እንጂ ዓለም አሁንም በውሃ ተሸፍና ነበር። ከሦስት ወራት በኋላ የተራሮች ጫፎች መታየት ጀመሩ።

ከአርባ ቀናት በኋላ ኖኅ ውሃው ከምድር ላይ ደርቆ እንደ ሆነ እንዲያይ ቁራ የተባለን ወፍ/አሞራ ላከ። ቁራው እዚህም እዚያም እየበረረ ደረቅ መሬት ቢፈልግም ሊያገኝ አልቻለም።

በኋላም ኖኅ ርግብ የተባለች ወፍ ላከ። ይሁን እንጂ የምታርፍበት መሬት ማግኘት ስላልቻለች ወደ ኖኅ ተመልሳ መጣች። ከሳምንት በኋላ ኖኅ እንደ ገና ርግቧን ላካት። እርሷም የወይራ ቅጠል በአፏ ይዛ ተመለሰች። ውሃው ይቀንስ ስለ ነበር ተክሎችም ደግሞ መብቀል ጀመሩ።

ኖኅ ሌላ አንድ ሳምንት ጠብቆ ርግቢቷን ለሦስተኛ ጊዜ ሰደዳት፤ በዚህ ጊዜ የምታርፍበት ስፍራ ስላገኘች ተመልሳ አልመጣችም። ውሃው እየደረቀ ነበር።

ከሁለት ወራት በኋላ እግዚአብሔር ኖኅን “አንተ ቤተሰብህና እንስሳቱ በሙሉ ከመርከቧ ውጡ። ብዙ ልጆችና የልጅ ልጆችን ወለዱ፤ ምድርንም ሞሉአት” አለ።

ስለዚህ ኖህና ቤተሰቡ ከመርከብ ወጡ ።ኖኅም ከመርከቢቱ ከወጣ በኋላ መሠዊያ ሠራና ከእያንዳንዱ እንስሳ ለመሥዋዕት ሊቀርቡ የሚችሉትን ለእግዚአብሔር መሥዋዕትአቀረበ። እግዚአብሔርም በመሥዋዕቱ ተደሰተ፤ ኖኅንና ቤተ ሰቡን ባረካቸው።

እግዚአብሔርም ‹‹ሰዎች ስለሚያደርጉት ክፉ ነገር ዳግም በጥፋት ውሃ አይጠፉም። ምንም እንኳ ሰዎች ከልጅነታቸው ጀምሮ ክፉዎች ቢሆኑም ዓለምን ዳግመኛ በጥፋት ውሃ አላጠፋም›› አለ።

እግዚአብሔር ለቃል ኪዳኑ ምልክት ይሆን ዘንድ የመጀመሪያውን ቀስተ ደመና ሠራ። ሁልጊዜ ቀስተ ደመናው በሰማይ ላይ ይታያል። እግዚአብሔር በዚህ ቀስተ ደመና አማካይነት ለሕዝቡ የገባውን ኪዳን ያሳታውሳል፤የርሱ ሕዝብም እንዲሁ ያስታውሳል።
የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከዘፍጥረት 6-8