አማርኛ: Open Bible Stories

Updated ? hours ago # views See on DCS

5. የተስፋው ልጅ

Image

አብራምና ሦራ ከነዓን ከደረሱ ከዐሥር ዓመታት በኋላ እንኳ ልጅ አልነበራቸውም። ስለዚህም የአብራም ሚስት ሦራ እንዲህ አለችው ‹‹እግዚአብሔር ልጅ እንዳልወልድ ስለከለከለኝና እኔም ከእንግዲህ እንዳልወልድ ስላረጀሁ አገልጋዬ አጋር ይህችትልህ፤ አግባትና ለኔ ልጅ ትውለድለኝ›› አለችው።

Image

ስለዚህ አብራም አጋርን አገባት። አጋርም ወንድ ልጅ ወለደች። አብራምም ‹‹እስማኤል›› ሲል ስም አወጣለት። ይሁን እንጂ ሦራ በአጋር ቀናችባት። እስማኤል ዐሥራ ሦስት ዓመት ሲሆነው እግዚአብሔር ለአብራም እንደገና ተናገረው።

Image

እግዚአብሔርም አብራምን ‹‹እኔ ኤልሻዳይ አምላክ ነኝ፤ ካንተ ጋር ቃል ኪዳን እገባለሁ›› አለው። አብራምም በግምባሩ መሬት ላይ ተደፍቶ ለእግዚአብሔር ሰገደ፤ እግዚአብሔርም አብራምን አለው ‹‹አንተ የብዙ ሕዝቦች አባት ትሆናለህ። የከነዓንን ምድር ለአንተና ለዘርህ ርስት አድርጌ እሰጥሃለው። እኔም ለዘላለም አምላካቸው እሆናለሁ። አንተም በቤተ ሰብህ የሚገኘውን ወንድ ሁሉ መግረዝ አለብህ›› አለው።

Image

እግዚአብሔርም ‹‹ሚስትህ ሦራ ወንድ ልጅ ትወልዳለች። እርሱም የተስፋው ልጅ ይሆናል። ስሙን ይስሐቅ ብለህ ትጠራዋለህ። ኪዳኔንም ከእርሱ ጋር አደርጋለሁ። እርሱም ታላቅ ሕዝብ ይሆናል። እስማኤልንም ታላቅ ሕዝብ አደርገዋለሁ፤ ይሁን እንጂ ቃል ኪዳኔ ከይስሐቅ ጋር ይሆናል›› አለው። እግዚአብሔርም የአብራምን ስም ‹‹አብርሃም›› ሲል ለወጠለት፤ ትርጓሜውም ‹‹የብዙዎች አባት›› ማለት ነው። እግዚአብሔር የሦራንም ስም ‹‹ሣራ›› ሲል ለወጠላት፤ ትርጓሜውም ‹‹ልዕልት›› ማለት ነው።

Image

በዚያኑ ዕለት አብርሃም በቤተ ሰቡ የሚኙትን ወንዶች ሁሉ ገረዘ። ከዓመት በኋላ አብርሃም 100 ዓመት ሲሆነውና ሣራ 90 ዓመት በሆናት ጊዜ ለአብርሃም ወንድ ልጅ ወለደችለት። እግዚአብሔርም እንዳላቸው ‹‹ይስሐቅ›› ሲሉ ስም አወጡለት።

Image

ይስሐቅ ወጣት በሆነ ጊዜ እግዚአብሔር የአብርሃምን እምነት እንዲህ ሲል ፈተነው፤ ‹‹አንድዬ ልጅህን ይስሐቅን ውሰድና ለኔ መሥዋዕት አድርገህ አቅርብልኝ›› አለው። እንደ ገና አብርሃም እግዚአብሔርን ታዘዘና ልጁን ሊሠዋው ተዘጋጀ።

Image

አብርሃምና ይስሐቅ መሥዋዕት ወደሚደረግበት ስፍራ በመጓዝ ላይ ሳሉ ይስሐቅ አባቱን ‹‹አባቴ ሆይ ለመሥዋዕት ማቅረቢያ እንጨቱ ይኸውና፤ በጉ ግን የታለ?›› ሲል ጠየቀ። አብርሃምም ‹‹ልጄ ሆይ የመሥዋዕቱን በግ እግዚአብሔር ያዘጋጃል›› ሲል መለሰለት።

Image

ወደ መሥዋዕት ማቅረቢያ ቦታ በደረሱ ጊዜ አብርሃም ልጁን ይስሐቅን አስሮ በመሠዊያው ላይ አጋደመው። አብርሃምም ልጁን ለማረድ እጁን ዘርግቶ ቢላዋውን ባነሣ ጊዜ፤ እግዚአብሔር “ተው፤ በልጁ ላይ ምንም ጉዳት አታድርስበት። አንድዬ ልጅህን ሳትሳሳ ለእኔ በመስጠትህ እኔን እንደምትፈራኝ አሁን አውቄአለሁ” አለው።

Image

በአቅራቢያው አብርሃም በቊጥቋጦ ውስጥ የታሰረ በግ አየ። እግዚአብሔር በይስሐቅ ፋንታ ለመሥዋዕት የሚሆን በግ አዘጋጅቶ ነበር። አብርሃምም በደስታ በጉን መሥዋዕት አድርጎ ለእግዚአብሔር አቀረበ።

Image

እግዚአብሔርም አብርሃምን አለው፣ ‹‹አንድያ ልጅህን እንኳ ሳይቀር ያለህን ሁሉ ልትሰጠኝ ፍቃደኛ ነህና ልባርክህ ቃል እገባለሁ። ዘሮችህ ከሰማይ ክዋክብት ይልቅ ይበዛሉ፤ እኔን ስለ ታዘዝከኝ የዓለም ሕዝቦች ሁሉ በዘርህ ይባረካሉ።››

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከዘፍጥረት 16-22፡፡