30. ኢየሱስ አምስት ሺህ ሰዎችን መገበ

ኢየሱስ በተለያዩ ብዙ መንደሮች እንዲሰብኩና ሰዎችን እንዲያስተምሩ ሐዋርያቱን ላከ፡፡ እነርሱም ኢየሱስ ወደ ነበረበት በተመለሱ ጊዜ፣ ያደረጉትን ነገር ነገሩት፡፡ ከዚያ በኋላ ኢየሱስ ከሐይቁ ማዶ ጸጥታ ወዳለበት ቦታ አብረውት እንዲሄዱና ጥቂት እንዲያርፉ ጋበዛቸው፡፡ ስለዚህ ጀልባ ውስጥ ገቡና ወደ ሐይቁ ማዶ ሄዱ፡፡

ነገር ግን በጀልባው ሲሄዱ ኢየሱስንና ደቀ መዛሙርቱን ያዩአቸው ብዙ ሰዎች ነበሩ፡፡ እነዚህ ሰዎች ሊቀድሙአቸው በሐይቁ ዳርቻ ሮጡ፡፡ ስለዚህ ኢየሱስና ደቀ መዛሙርቱ ወደ ማዶ በደረሱ ጊዜ፣ በጣም ብዙ ሰዎች አስቀድመው እዚያ ደርሰው ይጠባበቁአቸው ነበር፡፡

ሕዝቡ ሴቶችና ልጆች ሳይቈጠሩ ከ5000 በላይ ወንዶች ነበሩ፡፡ ኢየሱስ ለሕዝቡ እጅግ አዘነላቸው፡፡ ለኢየሱስ እነዚህ ሕዝብ እረኛ እንደሌላቸው በጎች ነበሩ፡፡ ስለዚህ አስተማራቸውና በመካከላቸው የነበሩትን በሽተኞች ፈወሳቸው፡፡

ቀኑ ሊመሽ ሲሆን ደቀ መዛሙርቱ እንዲህ ብለው ለኢየሱስ ነገሩት፣ ‹‹ጊዜው መሽቶአል፤ በአቅራቢያውም ከተሞች የሉም፡፡ ስለዚህ የሚበሉትን ነገር ይገዙ ዘንድ ሕዝቡን አሰናብታቸው፡፡››

ኢየሱስ ግን ደቀ መዛሙርቱን፣ ‹‹የሚበሉትን እናንተ ስጡአቸው!›› አላቸው፡፡ እነርሱም፣ ‹‹ይህን ማድረግ እንዴት እንችላለን? ያለን አምስት እንጀራና ሁለት ትንንሽ ዓሣ ብቻ ነው›› ብለው መለሱለት፡፡

ሃምሳ ሃምሳ ሆነው ሣሩ ላይ እንዲቀመጡ ለሕዝቡ ይነግሩ ዘንድ ኢየሱስ ለደቀ መዛሙርቱ ነገራቸው፡፡

ከዚያም ኢየሱስ አምስቱን እንጀራና ሁለቱን ዓሣ ይዞ ወደ ሰማይ ተመለከተ፣ ስለ ምግቡም እግዚአብሔርን አመሰገነ፡፡

ከዚያም ኢየሱስ እንጀራውንና ዓሣውን ቈረሰ፡፡ የቈረሰውን ለሕዝቡ እንዲያቀርቡም ለደቀ መዛሙርቱ ሰጣቸው፡፡ ደቀ መዛሙርቱ ምግቡን ማደላቸውን ቀጠሉ፣ በፍጹም አያልቅም ነበር! ሕዝቡ ሁሉ በልተው ጠገቡ፡፡

ከዚያ በኋላ ደቀ መዛሙርቱ ቊርስራሹን ምግብ ሰበሰቡ፣ እርሱም ዐሥራ ሁለት መሶብ ሙሉ ነበር! ምግቡ ሁሉ የመጣው ከአምስቱ እንጀራና ከሁለቱ ዓሣ ነበር፡፡
የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከማቴዎስ 14፡13-21፤ ማርቆስ 6፡31-44፤ ሉቃስ 9፡10-17፤ ዮሐንስ 6፡5-15፡፡