አማርኛ: Open Bible Stories

Updated ? hours ago # views See on DCS

30. ኢየሱስ አምስት ሺህ ሰዎችን መገበ

Image

ኢየሱስ በተለያዩ ብዙ መንደሮች እንዲሰብኩና ሰዎችን እንዲያስተምሩ ሐዋርያቱን ላከ፡፡ እነርሱም ኢየሱስ ወደ ነበረበት በተመለሱ ጊዜ፣ ያደረጉትን ነገር ነገሩት፡፡ ከዚያ በኋላ ኢየሱስ ከሐይቁ ማዶ ጸጥታ ወዳለበት ቦታ አብረውት እንዲሄዱና ጥቂት እንዲያርፉ ጋበዛቸው፡፡ ስለዚህ ጀልባ ውስጥ ገቡና ወደ ሐይቁ ማዶ ሄዱ፡፡

Image

ነገር ግን በጀልባው ሲሄዱ ኢየሱስንና ደቀ መዛሙርቱን ያዩአቸው ብዙ ሰዎች ነበሩ፡፡ እነዚህ ሰዎች ሊቀድሙአቸው በሐይቁ ዳርቻ ሮጡ፡፡ ስለዚህ ኢየሱስና ደቀ መዛሙርቱ ወደ ማዶ በደረሱ ጊዜ፣ በጣም ብዙ ሰዎች አስቀድመው እዚያ ደርሰው ይጠባበቁአቸው ነበር፡፡

Image

ሕዝቡ ሴቶችና ልጆች ሳይቈጠሩ ከ5000 በላይ ወንዶች ነበሩ፡፡ ኢየሱስ ለሕዝቡ እጅግ አዘነላቸው፡፡ ለኢየሱስ እነዚህ ሕዝብ እረኛ እንደሌላቸው በጎች ነበሩ፡፡ ስለዚህ አስተማራቸውና በመካከላቸው የነበሩትን በሽተኞች ፈወሳቸው፡፡

Image

ቀኑ ሊመሽ ሲሆን ደቀ መዛሙርቱ እንዲህ ብለው ለኢየሱስ ነገሩት፣ ‹‹ጊዜው መሽቶአል፤ በአቅራቢያውም ከተሞች የሉም፡፡ ስለዚህ የሚበሉትን ነገር ይገዙ ዘንድ ሕዝቡን አሰናብታቸው፡፡››

Image

ኢየሱስ ግን ደቀ መዛሙርቱን፣ ‹‹የሚበሉትን እናንተ ስጡአቸው!›› አላቸው፡፡ እነርሱም፣ ‹‹ይህን ማድረግ እንዴት እንችላለን? ያለን አምስት እንጀራና ሁለት ትንንሽ ዓሣ ብቻ ነው›› ብለው መለሱለት፡፡

Image

ሃምሳ ሃምሳ ሆነው ሣሩ ላይ እንዲቀመጡ ለሕዝቡ ይነግሩ ዘንድ ኢየሱስ ለደቀ መዛሙርቱ ነገራቸው፡፡

Image

ከዚያም ኢየሱስ አምስቱን እንጀራና ሁለቱን ዓሣ ይዞ ወደ ሰማይ ተመለከተ፣ ስለ ምግቡም እግዚአብሔርን አመሰገነ፡፡

Image

ከዚያም ኢየሱስ እንጀራውንና ዓሣውን ቈረሰ፡፡ የቈረሰውን ለሕዝቡ እንዲያቀርቡም ለደቀ መዛሙርቱ ሰጣቸው፡፡ ደቀ መዛሙርቱ ምግቡን ማደላቸውን ቀጠሉ፣ በፍጹም አያልቅም ነበር! ሕዝቡ ሁሉ በልተው ጠገቡ፡፡

Image

ከዚያ በኋላ ደቀ መዛሙርቱ ቊርስራሹን ምግብ ሰበሰቡ፣ እርሱም ዐሥራ ሁለት መሶብ ሙሉ ነበር! ምግቡ ሁሉ የመጣው ከአምስቱ እንጀራና ከሁለቱ ዓሣ ነበር፡፡

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከማቴዎስ 14፡13-21፤ ማርቆስ 6፡31-44፤ ሉቃስ 9፡10-17፤ ዮሐንስ 6፡5-15፡፡