አማርኛ: Open Bible Stories

Updated ? hours ago # views See on DCS

2. ኃጢአት ወደ ዓለም ገባ

Image

አዳምና ሚስቱ እግዚአብሔር በሠራላቸው ውብ የአትክልት ስፍራ ሲኖሩ በጣም ደስተኞች ነበሩ። ሁለቱም ራቁታቸውን ነበሩ፤ ይሁን እንጂ ራቁታቸውን በመሆናቸው አይተፋፈሩም ነበረ፤ ምክንያቱም ኃጢአት በዓለም አልነበረም። እነርሱም በአትክልቱ ስፍራ እየተመላለሱ ከእግዚአብሔር ጋር ይነጋገሩ ነበር።

Image

ነገር ግን ተንኮለኛ እባብ በአትክልቱ ውስጥ ነበር። እባቡም ሴትየዋን ‹‹እግዚአብሔር በእርግጥ በአትክልቱ ውስጥ ካለው ከማንኛውም ዛፍ ፍሬ እንዳትበሉ አዞዋችኋልን?›› ብሎ ጠየቃት።

Image

ሴቲቱም፣ ‹‹እግዚአብሔር ክፉንና መልካሙን ከሚያሳውቀው የእውቀት ዛፍ በስተቀር ከማንኛውም የዛፍ ፍሬ መብላት እንደምንችል ተናግሮናል። ነገር ግን ‹ያንን ዛፍ ፍሬ ብትበሉ ወይም ብትነኩት እንኳ ትሞታላችሁ› አለን።

Image

እባቡም ለሴቲቱ መልሶ፣ “ይህ እውነት አይደለም፤ አትሞቱም። ከፍሬው በበላችሁ ጊዜ ወዲያውኑ ዓይናችሁ እንደሚከፈትና መልካምንና ክፉን በማወቅ እንደ እግዚአብሔር እንደምትሆኑ እግዚአብሔር ስለሚያውቅ ነው አትብሉት ያላችሁ›› አለ።

Image

ሴቲቱም የዛፉ ፍሬ ለመብል መልካም፣ ለዓይንም የሚያስደስትና የሚያስጎመጅ እንደሆነ አየች። ጥበብንም ለማግኘት ስለጓጓች ከፍሬው ወስዳ በላች። ከእርሷም ጋር ለነበረው ለባሏም ሰጠችው። እርሱም ከዛፉ ፍሬ በላ።

Image

ወዲያውም የሁለቱም ዐይኖች ተከፈቱ። ራቁታቸውን መሆናቸውንም ተገነዘቡ፤ ቅጠልም እንደ ልብስ ሰፍተው ራቁትነታቸውን ለመሸፈን ሞከሩ።

Image

ከዚያም አዳምና ሚስቱ የእግዚአብሔር ድምፅ በአትክልቱ መካከል ሲመላለስ ሰምተው ሁለቱም ከእግዚአብሔር ፊት ተሸሸጉ። እግዚአብሔርም አዳምን ጠርቶ ‹‹የት ነህ?›› አለው። አዳምም ‹‹በአትክልቱ ስፍራ ስትመላለስ ሰማሁ፤ ራቁቴን ስለ ሆንኩ ፈራሁ ተሸሸግሁም›› ብሎ መለሰ።

Image

እግዚአብሔርም ‹‹ራቁትህን መሆንህን ማን ነገረህ? ከርሱ እንዳትበላ ብዬ ካዘዝሁህ ዛፍ በላህን?›› አለው።አዳምም፣ ‹‹ይህች ከእኔ ጋር እንድትኖር የሰጠኸኝ ሴት እርሷ ከዛፉ ፍሬ ሰጠችኝና በላሁ›› አለው። እግዚአብሔርም ሴቲቱን ‹‹ይህ ያደረግሽው ምንድን ነው?›› አላት። እርሷም፣ ‹‹እባብ አሳሳተኝና በላሁ›› አለች።

Image

እግዚአብሔር እባቡን እንዲህ አለው፤ ‹‹አንተ የተረገምህ ነህ፣ በደረትህ ትሳባለህ፤ አፈርም ትበላለህ፤ በአንተና በሴቲቱ፣ በዘርህና በዘርዋ መካከል ጠላትነትን አደርጋለሁ፤የሴቷ ዘር እርሱ ራስህን ይቀጠቅጣል አንተም ተረከዙን ታቆስላለህ።››

Image

እግዚአብሔር ሴቲቱንም አላት ‹‹በምጥ ጊዜ ጭንቅሽን አበዛለሁ፣ ፍላጎትሽ ወደ ባልሽ ይሆናል እርሱም ይገዛሻል።››

Image

እግዚአብሔርም አዳምን እንዲህ አለው። ‹‹የሚስትህን ቃል ሰምተህ አትብላ ብዬ ካዘዝሁህ ዛፍ ፍሬ በልተሃልና ምድር ካንተ የተነሣ የተረግመች ትሁን። በሕይወትህ ዘመን ሁሉ ምግብህን ጥረህ ግረህ ከእርሷ ታገኛለህ። ከዚያም ትሞታለህ አፈር ነህና ወደ አፈር ትመለሳለህ።›› አዳምም ሚስቱን የሕያዋን ሁሉ እናት ስለሆነች ሔዋን ብሎ ጠራት፤ ትርጓሜውም ሕይወት ሰጪ ማለት ነው፤ እግዚአብሔርም ከእንስሳ ቆዳ አዘጋጅቶ አዳምንና ሔዋንን አለበሳቸው።

Image

ለዘላለምም ሕያው ሆኖ እንዳይኖር መከልከል አለበት›› አለ። ስለዚህ አዳምንና ሔዋንን ከውቡ የአትክልት ስፍራ አስወጣቸው።ከዚያም ማንም የህይወት ዛፍ ፍሬ እንዳይበላ ወደ ሕይወት ዛፍ የሚወስደውን መንገድ እንዲጠብቁ ኃይለኞች መላእክትን በአትክልቱ ስፍራ መግቢያ ላይ አኖረ።

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ዘፍጥረት 3