2. ኃጢአት ወደ ዓለም ገባ

አዳምና ሚስቱ እግዚአብሔር በሠራላቸው ውብ የአትክልት ስፍራ ሲኖሩ በጣም ደስተኞች ነበሩ። ሁለቱም ራቁታቸውን ነበሩ፤ ይሁን እንጂ ራቁታቸውን በመሆናቸው አይተፋፈሩም ነበረ፤ ምክንያቱም ኃጢአት በዓለም አልነበረም። እነርሱም በአትክልቱ ስፍራ እየተመላለሱ ከእግዚአብሔር ጋር ይነጋገሩ ነበር።

ነገር ግን ተንኮለኛ እባብ በአትክልቱ ውስጥ ነበር። እባቡም ሴትየዋን ‹‹እግዚአብሔር በእርግጥ በአትክልቱ ውስጥ ካለው ከማንኛውም ዛፍ ፍሬ እንዳትበሉ አዞዋችኋልን?›› ብሎ ጠየቃት።

ሴቲቱም፣ ‹‹እግዚአብሔር ክፉንና መልካሙን ከሚያሳውቀው የእውቀት ዛፍ በስተቀር ከማንኛውም የዛፍ ፍሬ መብላት እንደምንችል ተናግሮናል። ነገር ግን ‹ያንን ዛፍ ፍሬ ብትበሉ ወይም ብትነኩት እንኳ ትሞታላችሁ› አለን።

እባቡም ለሴቲቱ መልሶ፣ “ይህ እውነት አይደለም፤ አትሞቱም። ከፍሬው በበላችሁ ጊዜ ወዲያውኑ ዓይናችሁ እንደሚከፈትና መልካምንና ክፉን በማወቅ እንደ እግዚአብሔር እንደምትሆኑ እግዚአብሔር ስለሚያውቅ ነው አትብሉት ያላችሁ›› አለ።

ሴቲቱም የዛፉ ፍሬ ለመብል መልካም፣ ለዓይንም የሚያስደስትና የሚያስጎመጅ እንደሆነ አየች። ጥበብንም ለማግኘት ስለጓጓች ከፍሬው ወስዳ በላች። ከእርሷም ጋር ለነበረው ለባሏም ሰጠችው። እርሱም ከዛፉ ፍሬ በላ።

ወዲያውም የሁለቱም ዐይኖች ተከፈቱ። ራቁታቸውን መሆናቸውንም ተገነዘቡ፤ ቅጠልም እንደ ልብስ ሰፍተው ራቁትነታቸውን ለመሸፈን ሞከሩ።

ከዚያም አዳምና ሚስቱ የእግዚአብሔር ድምፅ በአትክልቱ መካከል ሲመላለስ ሰምተው ሁለቱም ከእግዚአብሔር ፊት ተሸሸጉ። እግዚአብሔርም አዳምን ጠርቶ ‹‹የት ነህ?›› አለው። አዳምም ‹‹በአትክልቱ ስፍራ ስትመላለስ ሰማሁ፤ ራቁቴን ስለ ሆንኩ ፈራሁ ተሸሸግሁም›› ብሎ መለሰ።

እግዚአብሔርም ‹‹ራቁትህን መሆንህን ማን ነገረህ? ከርሱ እንዳትበላ ብዬ ካዘዝሁህ ዛፍ በላህን?›› አለው።አዳምም፣ ‹‹ይህች ከእኔ ጋር እንድትኖር የሰጠኸኝ ሴት እርሷ ከዛፉ ፍሬ ሰጠችኝና በላሁ›› አለው። እግዚአብሔርም ሴቲቱን ‹‹ይህ ያደረግሽው ምንድን ነው?›› አላት። እርሷም፣ ‹‹እባብ አሳሳተኝና በላሁ›› አለች።

እግዚአብሔር እባቡን እንዲህ አለው፤ ‹‹አንተ የተረገምህ ነህ፣ በደረትህ ትሳባለህ፤ አፈርም ትበላለህ፤ በአንተና በሴቲቱ፣ በዘርህና በዘርዋ መካከል ጠላትነትን አደርጋለሁ፤የሴቷ ዘር እርሱ ራስህን ይቀጠቅጣል አንተም ተረከዙን ታቆስላለህ።››

እግዚአብሔር ሴቲቱንም አላት ‹‹በምጥ ጊዜ ጭንቅሽን አበዛለሁ፣ ፍላጎትሽ ወደ ባልሽ ይሆናል እርሱም ይገዛሻል።››

እግዚአብሔርም አዳምን እንዲህ አለው። ‹‹የሚስትህን ቃል ሰምተህ አትብላ ብዬ ካዘዝሁህ ዛፍ ፍሬ በልተሃልና ምድር ካንተ የተነሣ የተረግመች ትሁን። በሕይወትህ ዘመን ሁሉ ምግብህን ጥረህ ግረህ ከእርሷ ታገኛለህ። ከዚያም ትሞታለህ አፈር ነህና ወደ አፈር ትመለሳለህ።›› አዳምም ሚስቱን የሕያዋን ሁሉ እናት ስለሆነች ሔዋን ብሎ ጠራት፤ ትርጓሜውም ሕይወት ሰጪ ማለት ነው፤ እግዚአብሔርም ከእንስሳ ቆዳ አዘጋጅቶ አዳምንና ሔዋንን አለበሳቸው።

ለዘላለምም ሕያው ሆኖ እንዳይኖር መከልከል አለበት›› አለ። ስለዚህ አዳምንና ሔዋንን ከውቡ የአትክልት ስፍራ አስወጣቸው።ከዚያም ማንም የህይወት ዛፍ ፍሬ እንዳይበላ ወደ ሕይወት ዛፍ የሚወስደውን መንገድ እንዲጠብቁ ኃይለኞች መላእክትን በአትክልቱ ስፍራ መግቢያ ላይ አኖረ።
የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ዘፍጥረት 3