አማርኛ: Open Bible Stories

Updated ? hours ago # views See on DCS

1. ፍጥረት

Image

እግዚአብሔር ሁሉንም ነገር የፈጠረው እንደሚከተለው ነው፡፡እግዚአብሔር ዓለምንንና በውስጧ የሚገኙትን ነገሮች ሁሉ በስድስት ቀናት ፈጠረ፡፡ እግዚአብሔር ምድርን ከፈጠረ በኋላ ምድር ጨለማና ባዶ ነበረች፤ በውስጧ ምንም ነገር ገና አልተፈጠረም ነበር፡፡ ይሁን እንጂ የእግዚአብሔር መንፈስ በውሆች ላይ ነበር፡፡

Image

ከዚያም እግዚአብሔር ‹‹ብርሃን ይሁን›› አለ ፤ ብርሃንም ሆነ፡፡ እግዚአብሔርም ብርሃኑ መልካም እንደሆነ አይቶ ‹‹ቀን›› ብሎ ጠራው፡፡ እግዚአብሔርም ቀኑን ከጨለማ ለይቶ ጨለማውን ሌሊት ብሎ ጠራው፡፡ እግዚአብሔርም በመጀመሪያው ቀን ብርሃንን ፈጠረ፡፡

Image

በሁለተኛው የፍጥረት ቀን እግዚአብሔር ከምድር በላይ ያለውን ጠፈር በቃሉ ፈጠረ፡፡ በዚህ መንገድ እግዚአብሔር ከጠፈር በለይ ያለውን ውሃ ከጠፈር በታች ካለው ውሃ የሚለይ ሰማይን ፈጠረ።

Image

በሦስተኛው ቀን እግዚአብሔር በቃሉ ውሃውን ከየብሱ መሬት እንዲለይ አደረገ፡፡ እግዚአብሔርም የብሱን መሬት ‹‹ምድር›› ውሃውንም ‹‹ባሕር›› ብሎ ጠራው፡፡ እግዚአብሔርም የፈጠረው ነገር መልካም እንደ ሆነ አየ፡፡

Image

ከዚያም እግዚአብሔር ምድር ሁሉንም ዓይነት ዛፎችንና ተክሎችን ታብቅል አለ፣ እንዲሁም ሆነ፡፡ እግዚአብሔርም የፈጠረው ነገር መልካም እንደ ሆነ አየ፡፡

Image

በአራተኛው የፍጥረት ቀን እግዚአብሔር ፀሐይን፣ ጨረቃንና ክዋክብትን በቃሉ ፈጠረ፡፡ እግዚአብሔርም እነዚህ ለመሬት ብርሃን እንዲሰጡ ቀንና ሌሊትንም ወቅቶችንና ዓመታትንም እንዲለዩ አደረገ፡፡ እግዚአብሔርም የፈጠረው ነገር መልካም እንደ ሆነ አየ፡፡

Image

በአምስተኛው ቀን እግዚአብሔር በውሃ ውስጥ የሚኖሩትንና ወፎችን ሁሉ በቃሉ ፈጠረ፡፡ እግዚአብሔር ያ መልካም እንደ ሆነ አየ፤የተፈጠሩትንም ባረካቸው፡፡

Image

በስድስተኛው ቀን፣ እግዚአብሔር ‹‹ምድር ሁሉንም ዓይነት እንስሳት ታውጣ›› አለ፡፡እነሱም ልክ እግዚአብሔር እንዳለውም ሆኑ፡፡ አንዳንዶቹ የቤት እንስሳት፣ አንዳንዶቹ በምድር የሚሳቡ፣ አንዳንዶቹ ደግሞ የዱር እንስሳት ነበሩ፡፡ እግዚአብሔርም ያ መልካም እንደ ሆነ አየ፡፡

Image

እግዚአብሔር ‹‹ሰዎችን በመልካችን እንደ ምሳሌአችን እንፍጠር እነርሱም በምድርና በእንስሳት ሁሉ ላይ ሥልጣን ይኑራቸው›› አለ፡፡

Image

ስለዚህ እግዚአብሔር ከምድር አፈር ወስዶ ሰው አድርጐ አበጀና የሕይወትን እስትንፋስ በአፍንጫው እፍ አለበት፡፡ የዚህም ሰው ስም አዳም ተባለ፡፡ እግዚአብሔር አዳም የሚኖርበትን የኤደን ገነት አበጀውና ስፍራውን እንዲያለማው እዚያ አስቀመጠው፡፡

Image

በገነትም መካከል እግዚአብሔር ሁለት የተለዩ ዛፎችን ተከለ፤እነርሱም የሕይወት ዛፍና መልካምና ክፉን እንዲያውቁ የሚያስችል የእውቀት ዛፍ ነበሩ፡፡ እግዚአብሔርም አዳምን መልካምንና ክፉን መለየት ከሚያስችለው የእውቀት ዛፍ በቀር በገነት ውስጥ ካለው ከየትኛውም ዛፍ መብላት እንደሚችል ነገረው፡፡ ነገር ግን ክፉውንና መልካሙን እንዲያውቁ ከሚያስችለው ዛፍ ቢበላ እንደሚሞትም ነገረው፡፡

Image

ከዚያም እግዚአብሔር ሰው ብቻውን ይሆን ዘንድ መልካም አይደለም አለ፡፡ ከእንስሳቱ አንዳቸውም የአዳም ረዳት ሊሆኑ አልቻሉም፡፡

Image

ስለዚህ እግዚአብሔር በአዳም ላይ ከባድ እንቅልፍ ጣለበት። አንቀላፍቶም ሳለ ከጐድኑ አንዲት አጥንት ወስዶ ሴት አድርጎ ሠራትና ወደ አዳም አመጣት፡፡

Image

አዳምም ባያት ጊዜ እንዲህ አለ፤ ‹‹ይህችስ እኔኑ ትመስላለች! ስለዚህ ከወንድ ተገኝታለችና ስሟ ሴት ትባል አለ፡፡” (በእብራይስጥ ከኢሽ ተገኝታለችና ስሟ ኢሻህ ትባል ይላል)፡፡ ስለዚህ ሰው አባቱንና እናቱን ይተዋል ከሚስቱም ጋር አንድ ይሆናል፡፡

Image

እግዚአብሔር ወንድና ሴትን በራሱ መልክ ፈጠረ፡፡ እግዚአብሔርም ባረካቸው፤ አላቸውም ‹‹ብዙ ተባዙ፤ ልጆችና የልጅ ልጆችንም ውለዱ ምድርንም ሙሉአት፡፡›› እግዚአብሔርም የሠራው ነገር ሁሉ እጅግ በጣም ጥሩ እንደ ሆነ አየ፡፡ በፈጠረው ነገር ሁሉ ደስ አለው። ይህ ሁሉ በስድስት የፍጥረት ቀናት ሆኑ።

Image

በሰባተኛውም ቀን እግዚአብሔር የመፍጠር ሥራውን ፈጸመ፡፡ ስለዚህ እግዚአብሔር ሲሠራው ከነበረው ሥራ ሁሉ አረፈ፤ ስለዚህ ሰባተኛውን ቀን ባረከው ቀደሰውም፡፡ ምክንያቱም በዚህ ቀን ከሥራው ሥራ ሁሉ አርፏልና፡፡ እግዚአብሔር ሰማይንና ምድርን በውስጣቸውም የሚገኙትን ሁሉ የፈጠረው በዚህ ሁኔታ ነበር፡፡

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከዘፍጥረት 1-2፡፡

2. ኃጢአት ወደ ዓለም ገባ

Image

አዳምና ሚስቱ እግዚአብሔር በሠራላቸው ውብ የአትክልት ስፍራ ሲኖሩ በጣም ደስተኞች ነበሩ። ሁለቱም ራቁታቸውን ነበሩ፤ ይሁን እንጂ ራቁታቸውን በመሆናቸው አይተፋፈሩም ነበረ፤ ምክንያቱም ኃጢአት በዓለም አልነበረም። እነርሱም በአትክልቱ ስፍራ እየተመላለሱ ከእግዚአብሔር ጋር ይነጋገሩ ነበር።

Image

ነገር ግን ተንኮለኛ እባብ በአትክልቱ ውስጥ ነበር። እባቡም ሴትየዋን ‹‹እግዚአብሔር በእርግጥ በአትክልቱ ውስጥ ካለው ከማንኛውም ዛፍ ፍሬ እንዳትበሉ አዞዋችኋልን?›› ብሎ ጠየቃት።

Image

ሴቲቱም፣ ‹‹እግዚአብሔር ክፉንና መልካሙን ከሚያሳውቀው የእውቀት ዛፍ በስተቀር ከማንኛውም የዛፍ ፍሬ መብላት እንደምንችል ተናግሮናል። ነገር ግን ‹ያንን ዛፍ ፍሬ ብትበሉ ወይም ብትነኩት እንኳ ትሞታላችሁ› አለን።

Image

እባቡም ለሴቲቱ መልሶ፣ “ይህ እውነት አይደለም፤ አትሞቱም። ከፍሬው በበላችሁ ጊዜ ወዲያውኑ ዓይናችሁ እንደሚከፈትና መልካምንና ክፉን በማወቅ እንደ እግዚአብሔር እንደምትሆኑ እግዚአብሔር ስለሚያውቅ ነው አትብሉት ያላችሁ›› አለ።

Image

ሴቲቱም የዛፉ ፍሬ ለመብል መልካም፣ ለዓይንም የሚያስደስትና የሚያስጎመጅ እንደሆነ አየች። ጥበብንም ለማግኘት ስለጓጓች ከፍሬው ወስዳ በላች። ከእርሷም ጋር ለነበረው ለባሏም ሰጠችው። እርሱም ከዛፉ ፍሬ በላ።

Image

ወዲያውም የሁለቱም ዐይኖች ተከፈቱ። ራቁታቸውን መሆናቸውንም ተገነዘቡ፤ ቅጠልም እንደ ልብስ ሰፍተው ራቁትነታቸውን ለመሸፈን ሞከሩ።

Image

ከዚያም አዳምና ሚስቱ የእግዚአብሔር ድምፅ በአትክልቱ መካከል ሲመላለስ ሰምተው ሁለቱም ከእግዚአብሔር ፊት ተሸሸጉ። እግዚአብሔርም አዳምን ጠርቶ ‹‹የት ነህ?›› አለው። አዳምም ‹‹በአትክልቱ ስፍራ ስትመላለስ ሰማሁ፤ ራቁቴን ስለ ሆንኩ ፈራሁ ተሸሸግሁም›› ብሎ መለሰ።

Image

እግዚአብሔርም ‹‹ራቁትህን መሆንህን ማን ነገረህ? ከርሱ እንዳትበላ ብዬ ካዘዝሁህ ዛፍ በላህን?›› አለው።አዳምም፣ ‹‹ይህች ከእኔ ጋር እንድትኖር የሰጠኸኝ ሴት እርሷ ከዛፉ ፍሬ ሰጠችኝና በላሁ›› አለው። እግዚአብሔርም ሴቲቱን ‹‹ይህ ያደረግሽው ምንድን ነው?›› አላት። እርሷም፣ ‹‹እባብ አሳሳተኝና በላሁ›› አለች።

Image

እግዚአብሔር እባቡን እንዲህ አለው፤ ‹‹አንተ የተረገምህ ነህ፣ በደረትህ ትሳባለህ፤ አፈርም ትበላለህ፤ በአንተና በሴቲቱ፣ በዘርህና በዘርዋ መካከል ጠላትነትን አደርጋለሁ፤የሴቷ ዘር እርሱ ራስህን ይቀጠቅጣል አንተም ተረከዙን ታቆስላለህ።››

Image

እግዚአብሔር ሴቲቱንም አላት ‹‹በምጥ ጊዜ ጭንቅሽን አበዛለሁ፣ ፍላጎትሽ ወደ ባልሽ ይሆናል እርሱም ይገዛሻል።››

Image

እግዚአብሔርም አዳምን እንዲህ አለው። ‹‹የሚስትህን ቃል ሰምተህ አትብላ ብዬ ካዘዝሁህ ዛፍ ፍሬ በልተሃልና ምድር ካንተ የተነሣ የተረግመች ትሁን። በሕይወትህ ዘመን ሁሉ ምግብህን ጥረህ ግረህ ከእርሷ ታገኛለህ። ከዚያም ትሞታለህ አፈር ነህና ወደ አፈር ትመለሳለህ።›› አዳምም ሚስቱን የሕያዋን ሁሉ እናት ስለሆነች ሔዋን ብሎ ጠራት፤ ትርጓሜውም ሕይወት ሰጪ ማለት ነው፤ እግዚአብሔርም ከእንስሳ ቆዳ አዘጋጅቶ አዳምንና ሔዋንን አለበሳቸው።

Image

ለዘላለምም ሕያው ሆኖ እንዳይኖር መከልከል አለበት›› አለ። ስለዚህ አዳምንና ሔዋንን ከውቡ የአትክልት ስፍራ አስወጣቸው።ከዚያም ማንም የህይወት ዛፍ ፍሬ እንዳይበላ ወደ ሕይወት ዛፍ የሚወስደውን መንገድ እንዲጠብቁ ኃይለኞች መላእክትን በአትክልቱ ስፍራ መግቢያ ላይ አኖረ።

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ዘፍጥረት 3

3. የጥፋት ውሃ

Image

ከረጅም ጊዜ በኋላ ብዙ ሕዝቦች በዓለም ይኖሩ ነበር። እነርሱም በጣም ክፉዎችና አመጸኞች ሆኑ። ክፋትም በጣም ስለበዛ እግዚአብሔር ዓለምን ሁሉ በከባድ የጥፋት ውሃ ለማጥፋት ወሰነ።

Image

ኖኅ ግን በእግዚአብሔር ዘንድ ሞገስን አገኘ። ኖኅ በክፉ ሰዎች መካከል የሚኖር ጻድቅ ሰው ነበር። እግዚአብሔርም በምድር ላይ ሊያመጣ ስላቀደው የጥፋት ውሃ ለኖኅ ነገረው። ኖኅም ግዙፍ መርከብም እንዲሠራ እግዚአብሔር ነገረው።

Image

የመርከቢቱም ርዝመት 140 ሜትር ወርዷ 23 ሜትር ከፍታዋ 13.5 ሜትር ይሁን አለው። ኖኅ የሚሠራት መርከብ ከእንጨት የተሠራች ሆና ባለ ሦስት ፎቅ፤ ብዙ ክፍሎች፤ ጣራና መስኮት ያሉአት ነበረች። መርከቢቱም ኖኅንና ቤተ ሰቡን፣ ሁሉንም ዓይነት የምድር ላይ እንስሳት ከጥፋት ውሃ እንድትጠብቅ ነገረው።

Image

ኖኅም እግዚአብሔርን በመታዘዘ እግዚአብሔር እንደ ነገራው መርከቢቱን ሠራ። መርከቧ በጣም ትልቅ ስለነበረች ለመጨረስ ብዙ ዓመታት ፈጀ። ኖኅ ስለሚመጣው የጥፋት ውሃ ለሕዝቡ እያስጠነቀቀ ወደ እግዚአብሔር እንዲመለሱ ይነግራቸው ነበር፤ ይሁን እንጂ አላመኑትም።

Image

እግዚአብሔር ኖኅንና ቤተ ሰቡን በቂ ምግብ ለራሳቸውና ለእንስሳቱ እንዲያከማቹ አዘዘ። ሁሉም ነገር ዝግጁ በሆነ ጊዜ ለኖኅ፣ ለሚስቱ፣ ለሦስቱ ወንዶች ልጆቹና ለሚስቶቻቸው ወደ መርከቢቱ ለመግባት ጊዜው መድረሱን ነገረው። ስምንት ሰዎችም ወደ መርከቢቱ ገቡ።

Image

እግዚአብሔር ከጥፋት ውሃው እንዲድኑ የሁሉንም ተባእትና እንስት እንስሳት ወፎችንም ጨምሮ ወደ ኖኅ ላከ። ለመሥዋዕት የሚያገለግሉ ሰባት ተባእትና ሰባት እንስት ከሁሉም ዓይነት እንስሳ ወደ ኖኅ መርከብ ላካቸው። ሁሉም ወደ መርከቡ እንደ ገቡ እግዚአብሔር ራሱ የመርከቡን በር ዘጋ።

Image

ከዚያም ዝናቡ መዝነብ ጀመረ፣ ዘነበ፣ ዘነበ፣ ዘነበ ያለማቋረጥ ለ40 ቀንና ሌሊት ዘነበ፣ ከምድርም ምንጭ ይፈልቅ ነበር። በመላው ዓለም ያለው ሁሉም ነገር በውሃ ተሸፈነ፤ ረጃጅም ተራሮች እንኳ ሳይቀሩ በውሃ ተሸፈኑ።

Image

በመርከቡ ከነበሩት ሰዎችና እንስሳት በቀር በምድር ይኖር የነበረ ነገር ሁሉ ሞተ፤ መርከቢቱም በውሃው ላይ ተንሳፍፋ በውስጧ የሚገኙትን ነፍሳት ሁሉ ከሞት አዳነች።

Image

ዝናቡ መዝነቡን ካቆመ በኋላ መርከቢቱ ለአምስት ወራት ያህል በውሃው ላይ ተንሳፈፈች። በዚህም ጊዜ ውሃው መቀነስ ጀመረ። ከዕለታት አንድ ቀን መርከቢቱ በተራራው አናት ላይ አረፈች፤ ይሁን እንጂ ዓለም አሁንም በውሃ ተሸፍና ነበር። ከሦስት ወራት በኋላ የተራሮች ጫፎች መታየት ጀመሩ።

Image

ከአርባ ቀናት በኋላ ኖኅ ውሃው ከምድር ላይ ደርቆ እንደ ሆነ እንዲያይ ቁራ የተባለን ወፍ/አሞራ ላከ። ቁራው እዚህም እዚያም እየበረረ ደረቅ መሬት ቢፈልግም ሊያገኝ አልቻለም።

Image

በኋላም ኖኅ ርግብ የተባለች ወፍ ላከ። ይሁን እንጂ የምታርፍበት መሬት ማግኘት ስላልቻለች ወደ ኖኅ ተመልሳ መጣች። ከሳምንት በኋላ ኖኅ እንደ ገና ርግቧን ላካት። እርሷም የወይራ ቅጠል በአፏ ይዛ ተመለሰች። ውሃው ይቀንስ ስለ ነበር ተክሎችም ደግሞ መብቀል ጀመሩ።

Image

ኖኅ ሌላ አንድ ሳምንት ጠብቆ ርግቢቷን ለሦስተኛ ጊዜ ሰደዳት፤ በዚህ ጊዜ የምታርፍበት ስፍራ ስላገኘች ተመልሳ አልመጣችም። ውሃው እየደረቀ ነበር።

Image

ከሁለት ወራት በኋላ እግዚአብሔር ኖኅን “አንተ ቤተሰብህና እንስሳቱ በሙሉ ከመርከቧ ውጡ። ብዙ ልጆችና የልጅ ልጆችን ወለዱ፤ ምድርንም ሞሉአት” አለ።

Image

ስለዚህ ኖህና ቤተሰቡ ከመርከብ ወጡ ።ኖኅም ከመርከቢቱ ከወጣ በኋላ መሠዊያ ሠራና ከእያንዳንዱ እንስሳ ለመሥዋዕት ሊቀርቡ የሚችሉትን ለእግዚአብሔር መሥዋዕትአቀረበ። እግዚአብሔርም በመሥዋዕቱ ተደሰተ፤ ኖኅንና ቤተ ሰቡን ባረካቸው።

Image

እግዚአብሔርም ‹‹ሰዎች ስለሚያደርጉት ክፉ ነገር ዳግም በጥፋት ውሃ አይጠፉም። ምንም እንኳ ሰዎች ከልጅነታቸው ጀምሮ ክፉዎች ቢሆኑም ዓለምን ዳግመኛ በጥፋት ውሃ አላጠፋም›› አለ።

Image

እግዚአብሔር ለቃል ኪዳኑ ምልክት ይሆን ዘንድ የመጀመሪያውን ቀስተ ደመና ሠራ። ሁልጊዜ ቀስተ ደመናው በሰማይ ላይ ይታያል። እግዚአብሔር በዚህ ቀስተ ደመና አማካይነት ለሕዝቡ የገባውን ኪዳን ያሳታውሳል፤የርሱ ሕዝብም እንዲሁ ያስታውሳል።

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከዘፍጥረት 6-8

4. የእግዚአብሔር ቃል ኪዳን ከአብርሃም ጋር

Image

ከጥፋት ውሃው ከብዙ ዓመታት በኋላ ሕዝቦች በዓለም ላይ እንደገና በዙ። ሁሉም አንድ አይነት ቋንቋ ይናገሩ ነበር። እግዚአብሔር እንዳዘዛቸው ምድርን በመሙላት ፋንታ በአንድነት ተሰብስበው ከተማ ሠሩ።

Image

እነርሱም በጣም ትምክህተኞችና እግዚአብሔር የተናገራቸውን ነገር የማይሰሙ ነበሩ። እንዲያውም ወደ ሰማይ ሊደርሱ ረጅም ሕንጻ መገንባት ጀመሩ። እግዚአብሔርም እነዚህ ሰዎች በአንድ ላይ ሆነው ክፉ መሥራታቸውን ከቀጠሉ ከዚህም የከፋ ብዙ ኃጢአት ማድረግ እንደሚችሉ አየ።

Image

ስለዚህም እግዚአብሔር ቋንቋቸውን ወደ ብዙ የተለያዩ ቋንቋዎች ደበላለቀና ሕዝቡን በዓለም ሁሉ በተናቸው። ሊሠሩት የጀመሩት ከተማ ስም ባቤል ይባላል። የስሙም ትርጓሜ የተደባለቀ ወይም ግራ የተጋባ ማለት ነው።

Image

ከመቶ ዓመታት በኋላ እግዚአብሔር አብራም የተባለውን ሰው ተናገረው። እግዚአብሔርም እንዲህ አለው “አገርህንና ቤተ ሰብህን ትተህ እኔ ወደማሳይህ ምድር ሂድ። በዚያም እባርክሃለሁ፣ ታላቅ ሕዝብም አደርግሃለሁ፤ ስምህንም ታላቅ አደርገዋለሁ፣ የሚባርኩህን እባርካለሁ፣ የሚረግሙህንም እረግማለሁ፤ የምድር ሰዎች ሁሉ ባንተ ይባረካሉ።”

Image

አብራምም እግዚአብሔርን ታዘዘ፤ ሚስቱን ሦራንና አገልጋዮቹን ሁሉና ንብረቱንም ሁሉ ይዞ እግዚአብሔር ወዳሳየው የከነዓን ምድር ሄደ።

Image

አብራም ከነዓን በደረሰ ጊዜ እግዚአብሔር ‹‹በዙሪያህ ያለውን ሁሉ ተመልከት፤ይህን የምታየውን ምድር ሁሉ ለአንተና ለዘሮችህ ውርስ አድርጌ እሰጣችኋለሁ›› አለው። አብራምም በምድሪቱ ተቀመጠ።

Image

ከዕለታት አንድ ቀን አብራም መልከ ጼዴቅ የተባለውን የልዑል እግዚአብሔር ሊቀ ካህን ተገናኘው። መልከ ጻዴቅም አብራምን ባረከው፤ እንዲህም አለው ‹‹የሰማይና የምድር ጌታ ልዑል እግዚአብሔር አብራምን ይባርክ››። አብራምም ለመልከ ጼዴቅ ካለው ሁሉ አሥራት ሰጠው።

Image

አብራምና ሦራ አሁንም ያለ ልጅ ብዙ ዓመታት ኖሩ። እግዚአብሔር ለአብራም እንደ ገና ተናገረውና ልጅ እንደሚወልድና ዘሮቹ እንደ ሰማይ ክዋክብት እንደሚበዙ ተስፋ ሰጠው። አብራምም በእግዚአብሔር ተስፋ አመነ። አብራምም በእግዚአብሔር ተስፋ በማመኑ ምክንያት ጻድቅ ሆኖ ተቈጠረ።

Image

እግዚአብሔርም ከአብራም ጋር ቃል ኪዳን ገባ። ቃል ኪዳን በሁለት ወገኖች መካከል የሚደረግ ስምምነት ነው። እግዚአብሔርም አብራምን ‹‹ከገዛ አብራክህ ልጅ እሰጥሃለሁ። የከነዓንንም ምድር ለዘሮችህ እሰጣለሁ›› አለው። አብራም ግን በዚያን ጊዜ ልጅ አልነበረውም።

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከዘፍጥረት 11-15

5. የተስፋው ልጅ

Image

አብራምና ሦራ ከነዓን ከደረሱ ከዐሥር ዓመታት በኋላ እንኳ ልጅ አልነበራቸውም። ስለዚህም የአብራም ሚስት ሦራ እንዲህ አለችው ‹‹እግዚአብሔር ልጅ እንዳልወልድ ስለከለከለኝና እኔም ከእንግዲህ እንዳልወልድ ስላረጀሁ አገልጋዬ አጋር ይህችትልህ፤ አግባትና ለኔ ልጅ ትውለድለኝ›› አለችው።

Image

ስለዚህ አብራም አጋርን አገባት። አጋርም ወንድ ልጅ ወለደች። አብራምም ‹‹እስማኤል›› ሲል ስም አወጣለት። ይሁን እንጂ ሦራ በአጋር ቀናችባት። እስማኤል ዐሥራ ሦስት ዓመት ሲሆነው እግዚአብሔር ለአብራም እንደገና ተናገረው።

Image

እግዚአብሔርም አብራምን ‹‹እኔ ኤልሻዳይ አምላክ ነኝ፤ ካንተ ጋር ቃል ኪዳን እገባለሁ›› አለው። አብራምም በግምባሩ መሬት ላይ ተደፍቶ ለእግዚአብሔር ሰገደ፤ እግዚአብሔርም አብራምን አለው ‹‹አንተ የብዙ ሕዝቦች አባት ትሆናለህ። የከነዓንን ምድር ለአንተና ለዘርህ ርስት አድርጌ እሰጥሃለው። እኔም ለዘላለም አምላካቸው እሆናለሁ። አንተም በቤተ ሰብህ የሚገኘውን ወንድ ሁሉ መግረዝ አለብህ›› አለው።

Image

እግዚአብሔርም ‹‹ሚስትህ ሦራ ወንድ ልጅ ትወልዳለች። እርሱም የተስፋው ልጅ ይሆናል። ስሙን ይስሐቅ ብለህ ትጠራዋለህ። ኪዳኔንም ከእርሱ ጋር አደርጋለሁ። እርሱም ታላቅ ሕዝብ ይሆናል። እስማኤልንም ታላቅ ሕዝብ አደርገዋለሁ፤ ይሁን እንጂ ቃል ኪዳኔ ከይስሐቅ ጋር ይሆናል›› አለው። እግዚአብሔርም የአብራምን ስም ‹‹አብርሃም›› ሲል ለወጠለት፤ ትርጓሜውም ‹‹የብዙዎች አባት›› ማለት ነው። እግዚአብሔር የሦራንም ስም ‹‹ሣራ›› ሲል ለወጠላት፤ ትርጓሜውም ‹‹ልዕልት›› ማለት ነው።

Image

በዚያኑ ዕለት አብርሃም በቤተ ሰቡ የሚኙትን ወንዶች ሁሉ ገረዘ። ከዓመት በኋላ አብርሃም 100 ዓመት ሲሆነውና ሣራ 90 ዓመት በሆናት ጊዜ ለአብርሃም ወንድ ልጅ ወለደችለት። እግዚአብሔርም እንዳላቸው ‹‹ይስሐቅ›› ሲሉ ስም አወጡለት።

Image

ይስሐቅ ወጣት በሆነ ጊዜ እግዚአብሔር የአብርሃምን እምነት እንዲህ ሲል ፈተነው፤ ‹‹አንድዬ ልጅህን ይስሐቅን ውሰድና ለኔ መሥዋዕት አድርገህ አቅርብልኝ›› አለው። እንደ ገና አብርሃም እግዚአብሔርን ታዘዘና ልጁን ሊሠዋው ተዘጋጀ።

Image

አብርሃምና ይስሐቅ መሥዋዕት ወደሚደረግበት ስፍራ በመጓዝ ላይ ሳሉ ይስሐቅ አባቱን ‹‹አባቴ ሆይ ለመሥዋዕት ማቅረቢያ እንጨቱ ይኸውና፤ በጉ ግን የታለ?›› ሲል ጠየቀ። አብርሃምም ‹‹ልጄ ሆይ የመሥዋዕቱን በግ እግዚአብሔር ያዘጋጃል›› ሲል መለሰለት።

Image

ወደ መሥዋዕት ማቅረቢያ ቦታ በደረሱ ጊዜ አብርሃም ልጁን ይስሐቅን አስሮ በመሠዊያው ላይ አጋደመው። አብርሃምም ልጁን ለማረድ እጁን ዘርግቶ ቢላዋውን ባነሣ ጊዜ፤ እግዚአብሔር “ተው፤ በልጁ ላይ ምንም ጉዳት አታድርስበት። አንድዬ ልጅህን ሳትሳሳ ለእኔ በመስጠትህ እኔን እንደምትፈራኝ አሁን አውቄአለሁ” አለው።

Image

በአቅራቢያው አብርሃም በቊጥቋጦ ውስጥ የታሰረ በግ አየ። እግዚአብሔር በይስሐቅ ፋንታ ለመሥዋዕት የሚሆን በግ አዘጋጅቶ ነበር። አብርሃምም በደስታ በጉን መሥዋዕት አድርጎ ለእግዚአብሔር አቀረበ።

Image

እግዚአብሔርም አብርሃምን አለው፣ ‹‹አንድያ ልጅህን እንኳ ሳይቀር ያለህን ሁሉ ልትሰጠኝ ፍቃደኛ ነህና ልባርክህ ቃል እገባለሁ። ዘሮችህ ከሰማይ ክዋክብት ይልቅ ይበዛሉ፤ እኔን ስለ ታዘዝከኝ የዓለም ሕዝቦች ሁሉ በዘርህ ይባረካሉ።››

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከዘፍጥረት 16-22፡፡

6. እግዚአብሔር ለይስሐቅ ሚስት አዘጋጀለት

Image

አብርሃም በጣም ባረጀ ጊዜ ይስሐቅ ዕድሜው ለአቅመ አዳም ደረሰ። ስለዚህ አብርሃም ከአገልጋዮቹ አንዱን ወደ ዘመዶቹ ምድር ሄዶ ለልጁ ለይስሐቅ ሚስት እንዲያመጣለት ላከው።

Image

አገልጋዩም የአብርሃም ዘመዶች ወደሚኖሩበት ምድር ከረጅም ጒዞ በኋላ ደረሰ። እግዚአብሔርም የተላከውን የአብርሃምን አገልጋይ ወደ ርብቃ መራው። ርብቃ የአብርሃም ወንድም የልጅ ልጅ ነበረች።

Image

ርብቃ ቤተ ሰቦቿን ትታ ከአገልጋዩ ጋር ወደ ይስሐቅ ቤት ለመሄድ ተስማማች። እንደ ደረሰችም ይስሐቅ አገባት።

Image

ከረጅም ጊዜ በኋላ አብርሃም ሲሞት እግዚአብሔር ከአብርሃም ጋር የገባው የተስፋ ቃል ኪዳን ሁሉም ወደ ይስሐቅ ተላለፈ። እግዚአብሔር ለአብርሃም ማንም ሊቆጥር የማይችል ዘር እንደሚኖረው ተስፋ ሰጥቶት ነበር። ይሁን እንጂ የይስሐቅ ሚስት ርብቃ ልጅ ልትወልድ አልቻለችም።

Image

ይስሐቅ እግዚአብሔርን ለመነ፣ እግዚአብሔርም ርብቃ መንታ ልጆችን እንድታረግዝ ፈቀደ። ሁለቱ ልጆች በርብቃ ማኅፀን ሳሉ እርስ በርሳቸው ይታገሉ ነበር። ርብቃም በማኅፀንዋ እየሆነ ያለው ምን እንደሆነ እግዚአብሔርን ጠየቀች።

Image

እግዚአብሔርም ርብቃን አላት፣ ‹‹በማኅፀንሽ ካሉት ከሁለቱ ልጆችሽ ሁለት ሕዝቦች ይወጣሉ። እነርሱም እርስ በርሳቸው ይታገላሉ። ታላቁም ታናሹን ያገለግላል›› አላት።

Image

የርብቃ ልጆች በተወለዱ ጊዜ ታላቁ ልጅ ቀይና ፀጉራም ሆኖ ወጣ፤ ‹ኤሳው› ሲሉትም ስም አወጡለት፤ ታናሹም ልጅ የኤሳውን ተረከዝ ይዞ ወጣ፤ ስሙንም ‹ያዕቆብ› ሲሉ አወጡለት።

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከዘፍጥረት 24፡1-25፤ 26፡፡

7. እግዚአብሔር ያዕቆብን ባረከ

Image

ልጆቹም እያደጉ ሲሄዱ ያዕቆብ በቤት መቆየትን ይወድ ነበር። ኤሳው ግን አደን ማደን ይወድ ነበር። ርብቃ ያዕቆብን ትወድደው ነበር፣ ይስሐቅ ግን ኤሳውን ይወድደው ነበር።

Image

ከዕለታት አንድ ቀን ኤሳው ከአደን ተመልሶ ሲመጣ በጣም ተርቦ ነበር። ኤሳው ያዕቆብን ‹‹እባክህ ካዘጋጀኸው ምግብ ትንሽ ስጠኝ›› አለው። ያዕቆብም “በመጀመሪያ የብኩርናህን መብት ስጠኝ” ሲል መለሰለት። ስለዚህም ኤሳው የብኩርናውን መብት ለያዕቆብ ሰጠው። ከዚያም ያዕቆብ ከሠራው ምግብ ሰጠው።

Image

ይስሐቅ ኤሳውን ሊባርከው ፈለገ። ነገር ግን ይህን ከማድረጉ በፊት ርብቃና ያዕቆብ ይስሐቅን አታለሉት። ያዕቆብ ኤሳውን መስሎ ወደ ይስሐቅ ቀረበ።በዚያ ጊዜ ይስሐቅ አርጅቶ ነበር፤ ማየትም አይችልም ነበር። ስለዚህም ያዕቆብ የኤሳውን ልብሶች ለብሶ የፍየል ለምድ በአንገቱና በእጆቹ አድርጎ ወደ ይስሐቅ በመቅረብ ይስሐቅን አታለለው።

Image

ያዕቆብ ወደ ይስሐቅ መጣና እንዲህ አለው፣ ‹‹እኔ ኤሳው ነኝ፤ መጥቻለውና ባርከኝ››አለው። ይስሐቅ የፍየሉን ፀጉር ዳሰሰና የልብሱንም ጠረን አሽትቶ ኤሳው እንደ ሆነ አሰበና ባረከው።

Image

ያዕቆብ የብኵርና መብቱንና በረከቱን አታልሎ ስለ ወሰደበት ኤሳው ያዕቆብን ጠላው። አባታቸው ሲሞት ሊገድለውም አቀደ።

Image

ነገር ግን ርብቃ የኤሳውን እቅድ ሰማች። ስለዚህም እሷና ይስሐቅ ከዘመዶቹ ጋር እንዲኖር ወደ ሩቅ አገር ያዕቆብን ሰደዱት።

Image

ያዕቆብ ለረዥም ዓመታት ከርብቃ ዘመዶች ጋር ኖረ። በዚያም ጊዜ ትዳር መስርቶ 12 ወንዶች ልጆችና 1 ሴት ልጅ ወለደ። እግዚአብሔርም በጣም አበለጸገው።

Image

በከነዓን ከኖረበት ከሃያ (20) ዓመታት በኋላ ያዕቆብ ከቤተ ሰቡ፣ ከአገልጋዮቹና ከመንጋው ሁሉ ጋር ወደ ከነዓን ምድር ተመለሰ።

Image

ኤሳው አሁንም ሊገድለኝ ያስብ ይሆናል ብሎ በልቡ ስላሰበ ያዕቆብ እጅግ በጣም ፈራ። ስለዚህም የእጅ መንሻ እንዲሆነው የብዙ ከብቶች መንጋ ስጦታ አድርጎ ለኤሳው ላከለት። ከብቶቹን ያመጡለት የያዕቆብ አገልጋዮች ኤሳውን ‹‹አገልጋይህ ያዕቆብ እነዚህን ከብቶች ልኮልሃል። እርሱም በቅርቡ ይመጣል›› አሉት።

Image

ኤሳው ግን ቀድሞውኑ ያዕቆብን ይቅር ብሎት ስለ ነበር ዳግም ለመገናኘት በመብቃታቸው ደስ አለው። ያዕቆብ በከነዓን ምድር በሰላም ኖረ፤ ከዚያም ይስሐቅ ሞተ። ያዕቆብና ኤሳውም ቀበሩት። እግዚአብሔር ለአብርሃም የገባለት የቃል ኪዳኑ ተስፋ አሁን ከይስሐቅ ወደ ያዕቆብ ተላለፈ።

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከዘፍጥረት 25፡27-33፡20፡፡

8. እግዚአብሔር ዮሴፍንና ቤተ ሰቡን አዳነ

Image

ከብዙ ዓመታት በኋላ ያዕቆብ ባረጀ ጊዜ የከብቶቹን መንጋ የሚጠብቁት ልጆቹ እንዴት እንዳሉ እንዲያያቸው የሚወደው ልጁን ዮሴፍን ወደ ወንድሞቹ ላከው።

Image

አባታቸው ያዕቆብ ዮሴፍን ከወንድሞቹ ሁሉ አብዝቶ ይወድደው ስለ ነበረና አለቃቸው እንደሚሆንም ሕልም አልሞ ስለ ነበር ዮሴፍን ወንድሞቹ ጠሉት። ዮሴፍ ወደ ወንድሞቹ በመጣ ጊዜ ጠልፈው ለባሪያ ነጋዴዎች ሸጡት።

Image

የዮሴፍ ወንድሞች ወደ ቤት ከመመለሳቸው በፊት የዮሴፍን ልብስ ቀድደው በፍየል ደም ነከሩት። ከዚያም ዮሴፍን አውሬ በልቶታል ብለው በደም የተነከረውን የዮሴፍን ልብስ ለአባታቸው አሳዩት። ያዕቆብም በጣም አዘነ።

Image

የባሪያ ነጋዴዎቹ ዮሴፍን ወደ ግብፅ ወሰዱት። በዚያን ጊዜ ግብፅ በአባይ ወንዝ አጠገብ የምትገኝ ታላቅና ኃያል አገር ነበረች። የባሪያ ነጋዴዎቹ ዮሴፍን ባርያ አድርገው ለሀብታም የመንግሥት ባለ ሥልጣን ሸጡት። ዮሴፍ ጌታውን በደንብ አድርጎ አገለገለው። እግዚአብሔርም ዮሴፍን ባረከው።

Image

ነገር ግን የጌታው ሚስት ከዮሴፍ ጋር ለመተኛት ፈልጋ ሞከረች። ዮሴፍ ግን በእግዚአብሔር ፊት ኃጢአት አልሠራም ሲል እምቢ አላት። እሷም ስለ ተናደደችበት በሐሰት ከስሳው ተይዞ ወደ እሥር ቤት ተወሰደ። በእሥር ቤትም ቢሆን ለእግዚአብሔር ታማኝ ሆኖ ስለ ተገኘ እግዚአብሔር ባረከው።

Image

ምንም እንኳ ዮሴፍ ንጹሕ ሰው ቢሆንም ከሁለት ዓመት በኋላ አሁንም በእሥር ቤት ነበር። አንድ ሌሊት ግብፃውያን ‹ፈርዖን› የሚሉት ንጉሣቸው በጣም የታወከባቸውን ሁለት ሕልሞች አለመ። ከአማካሪዎቹ አንዳቸውም የሕልሙን ትርጕም ሊነግሩት አልቻሉም።

Image

እግዚአብሔር ለዮሴፍ ሕልም የመተርጐም ችሎታ ሰጥቶት ነበር። ስለዚህ ፈርዖን ዮሴፍን ከእሥር ቤት ወደ ራሱ አስመጣው። ዮሴፍ ሕልሞቹን ተረጐመለትና እንዲህ አለው። ‹‹እግዚአብሔር ሰባት የጥጋብ ዓመታትን ይልካል፣ ቀጥሎም ሰባት የረሀብ ዓመታት ይሆናሉ›› አለ።

Image

ፈርዖንም በዮሴፍ በጣም ስለተደሰተ በግብፅ ምድር ሁሉ ላይ ከእርሱ ቀጥሎ ሁለተኛ ባለ ሥልጣን አድርጎ ሾመው።

Image

ዮሴፍም ሕዝቡን በሰባቱ የመልካም ምርት ዓመታት በርካታ እህል በጎተራው እንዲያከማቹ ነገራቸው። የሰባቱ የረሀብ ዓመታት በመጡ ጊዜ ዮሴፍ ከጎተራው ለሕዝቡ እህል በመሸጡ በቂ የሚበላ ምግብ አገኙ።

Image

የረሀቡ አስከፊነት በግብፅ ብቻ ሳይሆን ያዕቆብና ቤተ ሰቡ በሚኖሩበት በከነዓን ምድርም ደግሞ ነበር።

Image

ስለዚህ ያዕቆብ ልጆቹ እህል እንዲሸምቱ ወደ ግብፅ ላካቸው። የዮሴፍ ወንድሞች ለእህል ሸመታ ሄደው በፊቱ በቆሙ ጊዜ ዮሴፍ መሆኑን አላስተዋሉትም። ዮሴፍ ግን አወቃቸው።

Image

ዮሴፍ ወንድሞቹን ተለውጠው እንደ ሆነ ለማየት ከፈተናቸው በኋላ እንዲህ አላቸው፣ ‹‹አትፍሩ እኔ ወንድማችሁ ዮሴፍ ነኝ። ለባርነት ስትሸጡኝ ክፉ ልታደርጉብኝ ሞከራችሁ፤ ነገር ግን እግዚአብሔር ክፉውን ለመልካም አደረገው። መጥታችሁ በግብፅ ኑሩ፤ እኔም ለእናንተና ለቤተ ሰቦቻችሁ የሚያስፈልጋችሁን አቀርብላችኋለሁ።››

Image

የዮሴፍ ወንድሞች ወደ አገራቸው ተመልሰው ዮሴፍ በሕይወት መኖሩን ለአባታቸው ለያዕቆብ በነገሩት ጊዜ ያዕቆብ በጣም ደስ አለው።

Image

ምንም እንኳ ያዕቆብ ሽማግሌ ቢሆንም ከመላው ቤተ ሰቡ ጋር ወደ ግብፅ ሄዶ በዚያ ኖሩ። ያዕቆብ ከመሞቱ በፊት ልጆቹን እያንዳንዳቸውን ባረካቸው።

Image

እግዚአብሔር ለአብርሃም የገባቸው የቃል ኪዳን ተስፋዎች ከአብርሃም ወደ ይስሐቅ ተላለፉ፤ ከዚያም ወደ ያዕቆብ፣ ቀጥሎም ወደ ዐሥራ ሁለቱ የያዕቆብ ልጆቹና ቤተ ሰቦቻቸው ተላለፈ። የዐሥራ ሁለቱ የያዕቆብ ልጆች ዘሮቻቸው ዐሥራ ሁለቱ የእስራኤል ነገዶች ሆኑ።

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከዘፍጥረት 37-50፡፡

9. እግዚአብሔር ሙሴን ጠራው

Image

ዮሴፍ ከሞተ በኋላ ዘመዶቹ በሙሉ በግብፅ ኖሩ። እነርሱና ዘሮቻቸው ለብዙ ዓመታት እዚያ መኖራቸውን ቀጠሉ፤ ብዙ ልጆችንም አፈሩ፤ እስራኤላውያንም ተብለው ተጠሩ።

Image

ከመቶዎች ዓመታት በኋላ የእስራኤላውያን ቊጥር እየበዛ መጣ። ግብፃውያንም ዮሴፍንና እነርሱን ለመርዳት ዮሴፍ ያደረገውን ሁሉ ረሱ። እስራኤላውያን እየበዙ በመምጣታቸው ግብፃውያን ፈሯቸው። ስለዚህ በዚያን ጊዜ ግብፅን ያስተዳድር የነበረው ፈርዖን እስራኤሎችን ለግብፃውያን ባሪያዎች እንዲሆኑ አደረጋቸው።

Image

ግብፃውያን እስራኤላውያንን የግንብ ሥራ እንዲሠሩና፣ ከተማዎችን ሁሉ እንዲገነቡ በኃይል ያስገድዷቸው ነበር። ከባዱ ሥራም ሕይወታቸውን አስቸጋሪ አደረገው። እግዚአብሔር ግን ባረካቸው፤ ብዙ ልጆችም ነበሯቸው።

Image

ፈርዖን እስራኤላውያን ብዙ ሕፃናት እንዳሏቸው አየ፤ ስለዚህ ፈርዖን ከእስራኤላውያን ወንዶች ልጆች ሲወለዱ አባይ ወንዝ ውስጥ በመወርወር እንዲገድሉ ሕዝቡን አዘዘ።

Image

በዚያን ጊዜ አንዲት እስራኤላዊት ሴት ወንድ ልጅ ወለደች። እርሷና ባለቤቷ የቻሉትን ያህል ልጁን ለመደበቅ ሞከሩ።

Image

የልጁ ወላጆች ልጁን ከዚያ በላይ ሊደብቁት እንደማይችሉ በተረዱ ጊዜ ልጁ እንዳይሞት በሚንሳፈፍ ቅርጫት ውስጥ አድርገው በአባይ ወንዝ ዳር ባለው ቄጤማ ውስጥ ወንዙ ላይ እንዲንሳፈፍ ለቀቁት። ታላቅ እህቱም በልጁ ላይ የሚደርስበትን ለማየት በቅርብ ትከታተለው ነበር።

Image

የፈርዖን ሴት ልጅ ቅርጫቱን አየችና በውስጡ ያለውን ተመለከተች። ሕፃኑን ባየች ጊዜ እንደ ልጇ አድርጋ ወሰደችው። እርሷም ልጁን ጡት የምታጠባ እስራኤላዊት ሴት ቀጠረች። የቀጠረቻትም ሴትዮ የልጁ እናት መሆኗን አላወቀችም ነበር። ልጁም አድጎ የናቱን ጡት መጥባት ባቆመ ጊዜ ሴትዮዋ ወደ ፈርዖን ልጅ መለሰችው። የፈርዖ ልጅም ስሙን ‹‹ሙሴ›› ብላው ጠራች።

Image

ሙሴም ባደገ ጊዜ አንድ ቀን አንድ ግብፃዊ እስራኤላዊ የሆነውን ባሪያ ሲመታው አየ። ሙሴም እስራኤላዊ ወገኑን ሊያድነው ፈለገ።

Image

ሙሴ ማንም ሰው ያላየ መስሎት ግብፃዊውን ገድሎ ቀበረው። ነገር ግን ሙሴ ያደረገውን አንድ ሰው አይቶት ነበር።

Image

ሙሴ ያደረገውን ፈርዖን በሰማ ጊዜ ሊገድለው ፈለገ። ሙሴ ግን ከፈርዖን ወታደሮች ነፍሱን ለማዳን ወደ ምድረ በዳ ሸሸ።

Image

ሙሴ ከግብፅ ምድር ርቆ ወደሚገኝ ምድረ በዳ በመሄድ የበጐች እረኛ ሆነ። ከዚያም አገር ሚስት አግብቶ ሁለት ወንዶች ልጆችን ወለደ።

Image

አንድ ቀን ሙሴ በጐቹን እየጠበቀ ሳለ እሳት የሚነድበት ቊጥቋጦ ተመለከተ፤ ይሁን እንጂ ቊጥቋጦው አይቃጠልም ነበር። ሙሴም በደንብ ለማየት ወደ ቊጥቋጦው ጠጋ አለ። ወደሚቃጠለው ቊጥቋጦ ጠጋ ሲል የእግዚአብሔር ድምፅ ‹‹ሙሴ፤ በቅዱስ ስፍራ ቆመሃልና ከእግርህ ጫማህን አውልቅ›› አለው።

Image

እግዚአብሔርም ‹‹የሕዝቤን ሥቃይ አይቻለሁና እስራኤልንም ከግብፅ ባርነት ነጻ እንድታወጣቸው ወደ ፈርዖን እልክሃለው። ለአብርሃም፣ለይስሐቅና ለያዕቆብ ተስፋ የሰጠኋቸውን የከነዓንን ምድር እሰጣቸዋለሁ አለ።››

Image

ሙሴም ሕዝቡ ‹‹ማን ላከህ›› ብለው ቢጠይቁኝ ምን እላቸዋለሁ ሲል እግዚአብሔርን ጠየቀ። እግዚአብሔርም ሙሴን “እኔ ያለሁና የሚኖር ንኝ፤ ስለዝህ ‹ያለና የሚኖር ልኮኛል› ብለህ ንገራቸው›› አለው። ደግሞሜ ‹‹እኔ የአብርሃም፣ የይስሐቅና የያዕቆብ አምላክ ያህዌህ ነኝ። ስሜም ለዘላለም ይህ ነው” አለው።

Image

ሙሴ ስለ ፈራ ወደ ፈርዖን መሄድ አልፈለገም። ምክንያቱም የንግግር ችሎታ የለኝም ብሎ በማሰቡ ነበር። ስለዚህም እግዚአብሔር የሙሴን ወንድም አሮንን አብሮት እንዲሄድና ሙሴን እንዲረዳው ላከው። እግዚአብሔርም ፈርዖን ሕዝቡን አለቅም በሚል ልቡን ሊያደነድን እንደሚችል ሙሴንና አሮንን አስጠነ ቃቸው።

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከዘጸአት 1-4፡፡

10. ዐሥሩ መቅሠፍቶች

Image

ሙሴና አሮን ወደ ፈርዖን ሄደው “የእስራኤል አምላክ “ሕዝቤን ልቀቅ! ይልሃል” አሉት። ፈርዖን ግን አልሰማቸውም። እስራኤላውያን ነጻ ሆነው እንዲሄዱ በመልቀቅ ፈንታ ከበፊቱ የከበደ ሥራ እንዲሠሩ አስገደዳቸው!

Image

ፈርዖን ሕዝቡን አልለቅም ማለቱን ቀጠለ፤ ስለዚህ እግዚአብሔር በግብፅ ላይ ዐሥር መቅሠፍቶችን ላከ። እግዚአብሔር በእነዚህ መቅሠፍቶች አማካይነት ከፈርዖንና ከግብፅ አማልክት ሁሉ ይልቅ ኃያል መሆኑን ለፈርዖን ዐሳየው።

Image

እግዚአብሔር የዓባይን ውሃ ወደ ደም ለወጠው፣ ነገር ግን ፈርዖን አሁንም እስራኤላውያንን እንዲሄዱ አልለቀቃቸውም።

Image

እግዚአብሔር በግብፅ ሁሉ ላይ እንቁራሪቶችን ላከ። ፈርዖን እንቁራሪቶቹን እንዲያርቅ ሙሴን ለመነው። እንቁራሪቶቹ ሁሉ ከሞቱ በኋላ ግን ፈርዖን ልቡን እንደገና አደነደነና እስራኤላውያንን ከግብፅ እንዲወጡ አልለቀቃቸውም።

Image

ስለዚህ እግዚአብሔር የቅማል መቅሰፍት ላከ። ከዚያም የዝንብ መቅሰፍት ላከ። ፈርዖን ሙሴንና አሮንን ጠራና መቅሠፍቱን ካቆሙ እስራኤላውያን ከግብፅ መሄድ እንደሚችሉ ነገራቸው። ሙሴ በጸለየ ጊዜ እግዚአብሔር የዝንብ መቅሰፍቶችን ሁሉ ከግብፅ አስወገደ። ነገር ግን ፈርዖን ልቡን አደነደነና ሕዝቡን ነፃ እንዲወጡ አልለቀቃቸውም።

Image

ቀጥሎ እግዚአብሔር የግብፃውያን ከብቶች ሁሉ ታመው እንዲሞቱ አደረገ። ነገር ግን የፈርዖን ልብ ስለደነደነ እስራኤላውያንን አልለቀቀም።

Image

ከዚያም እግዚአብሔር በፈርዖን ፊት ዐመድ ወደ ሰማይ እንዲበትን ለሙሴ ነገረው። ዐመዱን በበተነ ጊዜ በግብፃውያን ላይ የሚያም ቊስል ሆነባቸው፣ በእስራኤላውያን ላይ ግን ቊስሉ አልሆነባቸውም። እግዚአብሔር የፈርዖንን ልብ ስላደነደነ ፈርዖን እስራኤላውያንን አልለቀቀም።

Image

ከዚያ በኋላ እግዚአብሔር በግብፅ ያለውን አብዛኛውን ቡቃያ ያሚያጠፋና ከቤት ውጪ የነበረውን ማንኛውንም ሰው የሚገድል በረዶ ላከ። ፈርዖን ሙሴንና አሮንን ጠርቶ፣ ‹‹በድዬአለሁ። መሄድ ትችላላችሁ›› ብሎ ነገራቸው። ስለዚህ ሙሴ ጸለየ፣ በረዶውም ከሰማይ መዝነቡን አቆመ።

Image

ነገር ግን ፈርዖን እንደ ገና ኃጢአት ሠራ፤ ልቡንም አደነደነ። እስራኤላውያንን አልለቀቀም።

Image

ስለዚህ እግዚአብሔር በግብፅ ላይ የአንበጣዎችን መንጋ አመጣ። እነዚህ አንበጣዎች ከበረዶው የተረፈውን ሰብል ሁሉ አወደሙት።

Image

ከዚያም እግዚአብሔር ለሦስት ቀን የቆየ ጨለማ ላከ። ጭለማው በጣም ከባድ ስለነበር ግብፃውያን ከቤታቸው ሊወጡ አቻሉም ነበር። እስራኤላውያን በሚኖሩበት ስፍራ ግን ብርሃን ነበረ።

Image

ከእነዚህ ዘጠኝ መቅሠፍቶች በኋላ እንኳ ፈርዖን አሁንም እስራኤላውያንን አልለቅም አለ። ፈርዖን መስማት እንቢ ስላለ፣ እግዚአብሔር አንድ የመጨረሻ መቅሠፍት ለመላከ ወሰነ። ይህ መቅሰፍት ፈርዖን ዐሳቡን እንዲቀይር ያደርጋል።

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከዘጸአት 5-10፡፡

11. ፋሲካ

Image

ፈርዖን እስራኤላውያንን ካልለቀቀ የግብፃውያን ሰዎችና የእንስሳቶቻቸውን መጀመሪያ የተወለዱትን ወንዶች ሁሉ እንደሚገድል እግዚአብሔር ፈርዖንን አስጠነቀቀው። ፈርዖን ይህን ቢሰማም እንኳ፣ አሁንም ማመንና ለእግዚአብሔር መታዘዝ እምቢ አለ።

Image

እግዚአብሔር በእርሱ ያመነ የማንኛውንም ሰው የመጀመሪያ ወንድ ልጅን ለማዳን መንገድ አዘጋጀ። እያንዳንዱ ቤተ ሰብ ፍጹም የሆነ የበግ ጠቦት መርጦ እንዲያርድ አዘዘ።

Image

እግዚአብሔር ለእስራኤላውያን የጠቦቱን ደም በቤታቸው በር ላይ እንዲቀቡት፣ ሥጋውንም ጠብሰው ያለ እርሾ ከተጋገረው ቂጣ ጋር በፍጥነት እንዲበሉት ነገራቸው። ደግሞ በበሉት ጊዜ ከግብፅ ለመውጣት እንዲዘጋጁ ነገራቸው።

Image

እስራኤላውያን ልክ እግዚአብሔር እንዲያደርጉ እንዳዘዛቸው ሁሉንም ነገር አደረጉ። እኩለ ሌሊት ላይ እግዚአብሔር በመላው ግብፅ አልፎ መጀመሪያ የተወለደውን ወንድ ሁሉ ገደለ።

Image

የእስራኤላውያን ቤቶች ሁሉ በሮቻቸው ደም ተቀብተው ነበር፣ ስለዚህ እግዚአብሔር በቤቶቹ አለፈ። በቤቶቹ ውስጥ የነበረው ሁሉ ከሞት ተረፈ። እስራኤላውያን በጠቦቱ ደም ምክንያት ዳኑ።

Image

ግብፃውያን ግን በእግዚአብሔር አላመኑም፣ ትእዛዛቱንም አልፈጸሙም። ስለዚህ እግዚአብሔር በቤቶቻቸው አላለፈም። እግዚአብሔር የግብፃውያንን በመጀመሪያ የተወለዱ ወንዶችን በሙሉ ገደለ።

Image

በእስር ቤት ካለው በኵር ልጅ ጀምሮ እስከ ፈርዖን በኩር ልጅ ድረስ የግብፃዊያን የመጀመሪያ ወንድ ልጅ በሙሉ ሞተ። ከጥልቅ ሐዘናቸው የተነሣ በግብፅ የነበሩ ሰዎች ሁሉ ያለቅሱና ይጮኹ ነበር።

Image

በዚያው ሌሊት ፈርዖን ሙሴንና አሮንን ጠርቶ፣ “እስራኤላውያንን ይዛችሁ አሁኑኑ ከግብፅ ውጡ” አላቸው። ግብፃውያንም እስራኤላውያን በፍጥነት ከግብፅ እንዲወጡ አስቸኰሉአቸው።

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከዘጸአት 11፡1-12፡32፡፡

12. የእስራኤላውያን ከግብፅ መውጣት

Image

እስራኤላውያን ከግብፅ በመውጣታቸው በጣም ደስ አላቸው። ከእንግዲህ ባሪያዎች አይደሉም፣ ወደ ተስፋዪቱ ምድርም በመጓዝ ላይ ናቸው። ግብፃውያን ለእስራኤላውያን ወርቅና ብር ሌሎችም የከበሩ ነገሮች ሳይቀሩ የጠየቁትን ማንኛውንም ነገር ሰጡአቸው። እስሬላውያን ከግብፅ ሲወጡ ከሌሎች ብሔሮች የሆኑ አንዳንድ ሰዎች በእግዚአብሔር አምነው ከእስራኤላውያን ጋር ከግብፅ ወጡ።

Image

እግዚአብሔርም ቀን ረጅም በሆነ የደመና ዓምድ፣ ማታ ደግሞ ረጅም የሆነ የእሳት ዓምድ ከፊት ከፊታቸው እንዲሄድ እያደረገ መራቸው። እግዚአብሔር ሁልጊዜ ከእነርሱ ጋር በመሆን ሲጓዙ መራቸው።እነርሱ ማድረግ ያለባቸው ነገር ቢኖር እርሱን መከተል ብቻ ነበር።

Image

ከጥቂት ጊዜ በኋላ፣ ፈርዖንና ሕዝቡ ዐሳባቸውን ቀይረው እስራኤላውያን እንደ ገና የእነርሱ ባሪያዎች እንዲሆኑ ፈለጉ። እግዚአብሔር ብቸኛው እውነተኛ አምላክ መሆኑን ሕዝቡ እንዲያዩ፣ እንዲሁም እርሱ፣ ያሕዌ፣ ከፈርዖንና ከአማልክቱ የበለጠ ኃያል እንደ ሆነ ይረዱ ዘንድ የፈርዖንን ልብ አደነደነው።

Image

ስለዚህ ፈርዖንና ጦር ሠራዊቱ እንደ ገና ባሪያዎቻቸው ሊያደርጉአቸው እስራኤላውያንን አሳደዱአቸው። እስራኤላውያን የግብፅ ጦር ሠራዊት ሲመጣ ባዩ ጊዜ፣ በፈርዖን ጦር ሠራዊትና በቀይ ባሕር መካከል እንደ ተጠመዱ ዐወቁ። በጣም ፈርተው ስለ ነበር፣ ‹‹ከግብፅ ለምን ወጣን? መሞታችን ነው!›› ብለው ጮኹ።

Image

ሙሴ እስራኤላውያንን፣ ‹‹አትፍሩ! ዛሬ እግዚአብሔር ስለ እናንተ ተዋግቶ ያድናችኋል›› ብሎ ነገራቸው። ከዚያም እግዚአብሔር፣ለሙሴ ‹‹ሕዝቡ ወደ ቀይ ባሕር እንዲንቀሳቀሱ ንገራቸው››አለ።

Image

ከዚያም ግብፃውያን እስራኤላውያንን ማየት እንዳይችሉ እግዚአብሔር የደመናውን ዓምድ በእስራኤላውያንና በግብፃውያን መካከል አደረገው።

Image

እግዚአብሔርም ለሙሴ በባሕሩ ላይ እጁን እንዲዘረጋና ውሃውን እንዲከፍለው ነገረው። ከዚያም እግዚአብሔር በባሕሩ መካከል መተላለፊያ መንገድ ይኖር ዘንድ ነፋስ ውሃውን ወደ ግራና ወደ ቀኝ እንዲገፋ አደረገ።

Image

እስራኤላውያንም ውሃው በግራና በቀኛቸው እንደ ግድግዳ ሆኖላቸው በባሕሩ መካከል በደረቅ መሬት ላይ ተጓዙ።

Image

ከዚያም እግዚአብሔር እስራኤላውያን እያመለጡ መሆናቸውን ግብፃውያኑ ያዩ ዘንድ የደመናውን አምድ ከመንገዱ ወደ ላይ አነሳው። ግብፃውያንም ከኋላቸው ሊያሳድዱአቸው ወሰኑ።

Image

ስለዚህ በባሕሩ መካከል ውስጥ ባለው መንገድ እስራኤላውያንን ተከተሉአቸው፣ ነገር ግን እግዚአብሔር ግብፃውያን እንዲርበተበቱና ሰረገሎቻቸውም እንዳይንቀሳቀሱ አደረገ።ግብፃውያንም “ለነፍሳቸው ሽሹ! እግዚአብሔር ለእስራኤላውያን እየተዋጋላቸው ነው!” ብለው ጮኹ።

Image

እስራኤላውያን ሁሉ ባሕሩን በደኅና ከተሻገሩ በኋላ፣ እግዚአብሔር እንደ ገና እጁን እንዲዘረጋ ለሙሴ ነገረው። እርሱም እግዚአብሔር እንዳዘዘ ባደረገ ጊዜ፣ ውሃው በግብፃውያን ሠራዊት ላይ ተገለበጠና ወደ ድሮው ቦታ ተመለሰ።የግብፃውያን ጦር ሠራዊት በሙሉ ሰጠመ።

Image

እስራኤላውያን ግብፃውያን እንደ ሞቱ ባዩ ጊዜ በእግዚአብሔር አመኑ፤ ሙሴም የእግዚአብሔር ነቢይ መሆኑን አመኑ።

Image

ደግሞም እስራኤላውያን እግዚአብሔር ከሞትና ከባርነት ስለ አዳናቸው እጅግ በጣም ደስ አላቸው! አሁን እግዚአብሔርን ለማገልገል ነጻ ሆኑ። እስራኤላውያንም እግዚአብሔር ከግብፃውያን ጦር ሠራዊት ስለ አዳናቸው ዐዲሱን ነጻነታቸውን ለማክበርና እግዚአብሔርን ለማመስገን ብዙ መዝሙሮችን ዘመሩ።

Image

እግዚአብሔር እንዴት በግብፃውያን ላይ ድልን እንደ ሰጣቸውና ከባርነት እንዳዳናቸው ያስታውሱ ዘንድ በያመቱ ፋሲካን እንዲያከብሩ እስራኤላውያንን አዘዛቸው። እንከን በፍጹም የሌለበትን ጠቦት አርደው ካልቦካ ቂጣ ጋር በመብላት ተደሰቱ።፡፡

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከዘጸአት 12፡33-15፡21፡፡

13. እግዚአብሔር ከእስራኤል ጋር ያደረገው ቃል ኪዳን

Image

እግዚአብሔር እስራኤላውያንን በቀይ ባሕር ውስጥ ካሳለፋቸው በኋላ በምድረ በዳ ውስጥ ሲና ተብሎ ወደሚጠራ ተራራ ወሰዳቸው። ይህም ሙሴ የሚቃጠለውን ቊጥቋጦ ያየበት ተራራ ነው። ሕዝቡ በተራራው ሥር ድንኳኖቻቸውን ተከሉ።

Image

እግዚአብሔርም፣ ‹‹ለእኔ ብትታዘዙና ቃል ኪዳኔን ብትጠብቁ፣ የከበረ ርስት፣ የካህናት መንግስት፣ እንዲሁም ቅዱስ ሕዝብ ትሆኑኛላችሁ›› ብሎ ለሙሴና ለእስራኤል ሕዝብ ተናገረ።

Image

ሕዝቡ በመንፈሳዊነት ራሳቸውን ካዘጋጁ ከሦስት ቀን በኋላ፣ እግዚአብሔር በነጐድጓድ፣ በመብረቅ፣ በጢስ እንዲሁም ከፍ ባለ የመለከት ድምፅ በሲና ተራራ ላይ ወረደ። ወደ ተራራው እንዲወጣ የተፈቀደለት ሙሴ ብቻ ነበር።

Image

ከዚያም እግዚአብሔር ቃል ኪዳን ገባላቸውና እንዲህ አለ፣ ‹‹እኔ ከግብፅ ባርነት ያዳንኳችሁ፣ አምላካችሁ፣ ያህዌ ነኝ። ሌሎችን አማልክት አታምልኩ።››

Image

‹‹ጣዖታትን አትሥሩ አታምልኳቸውም፣ ምክንያቱም እኔ፣ ያህዌ ቀናተኛ አምላከ ነኝ። ስሜንም በከንቱ አትጥሩ፣ የሰንበትን ቀን ትቀድሰው ዘንድ ዐስብ። ይኸውም ሥራህን ሁሉ በስድስት ቀን ሥራ፣ ሰባተኛው ቀን ግን የምታርፍበትና እኔን የምታስታውስበት ዕለት ነው።››

Image

‹‹አባትህንና እናትህን አክብር። አትግደል። አታመንዝር። አትስረቅ። አትዋሽ። የባልንጀራህን ሚስት፣ ቤቱን፣ ወይም የእርሱ የሆነውን ማንኛውም ነገር አትመኝ።››

Image

ከዚያም እግዚአብሔር እነዚህን ዐሥር ትእዛዛት በሁለት ጠፍጣፋ ድንጋዮች ላይ ጽፎ ለሙሴ ሰጠው። ደግሞ እግዚአብሔር የሚከተሉአቸውን ሌሎች ብዙ ሕግጋትንና ደንቦችን ሰጣቸው። ሕዝቡ እነዚህን ሕግጋት ከታዘዙ እግዚአብሔር እንደሚባርካቸውና እንደሚጠብቃቸው ተስፋ ሰጣቸው። ሕግጋቱን ካልታዘዙ ግን እግዚአብሔር ይቀጣቸዋል።

Image

ደግሞም እግዚአብሔር ለእስራኤላውያን እንዲሠሩለት ስለሚፈልገው ድንኳን ዝርዝር መግለጫ ሰጣቸው። እርሱ የመገናኛው ድንኳ ተብሎ ይጠራ ነበር፣ በትልቅ መጋረጃ የተከፈሉ ሁለት ክፍሎችም ነበሩት። እግዚአብሔር በዚያ ይኖር ስለ ነበረ፣ ከመጋረጃ በስተጀርባ ወዳለው ክፍል እንዲገባ የተፈቀደለት ሊቀ ካህን ብቻ ነበር።

Image

የእግዚአብሔርን ሕግ ያልታዘዘ ማንኛውም ሰው በመገናኛው ድንኳ ፊት ለፊት ወዳለው መሠዊያ ለእግዚአብሔር መሥዋዕት የሚሆን እንስሳ ያመጣ ነበር። ካህኑ እንስሳውን ያርድና በመሠዊያው ላይ ያቃጥለው ነበር። የተሠዋው እንስሳ ደም የሰውዬውን ኃጢአት ይሸፍንና ሰውዬውን በእግዚአብሔር ፊት ያነጻው ነበር። እግዚአብሔር ካህናቱ ይሆኑ ዘንድ የሙሴን ወንድም አሮንንና፣የአሮንን ዝርያዎች መረጠ።

Image

ሕዝቡ ሁላቸውም እግዚአብሔር የሰጣቸውን ትእዛዛት ለመፈጸም፣ እግዚአብሔርን ብቻ ለማምለክ፣ እንዲሁም የተለዩ ሕዝቡ ለመሆን ተስማሙ። ነገር ግን ለእግዚአብሔር ለመታዘዝ ቃል ከገቡ ከጥቂት ጊዜ በኋላ ክፉኛ ኃጢአት ሠሩ።

Image

ሙሴ ለብዙ ቀናት በሲና ተራራ ጫፍ ላይ ሆኖ ከእግዚአብሔር ጋር ይነጋገር ነበር። ሕዝቡ እርሱ እስኪመለስ ድረስ መጠበቅ ሰለቻቸው። ስለዚህ ወደ አሮን ወርቅ አመጡና ጣዖት እንዲሠራላቸው ጠየቁት!

Image

አሮንም በጥጃ ቅርፅ የወርቅ ጣዖት ሠራ። ሕዝቡም ልቅ በሆነ ሁኔታ ጣዖቱን ማምለክ ጀመሩ፣ መሥዋዕትም ሠዉለት! በኃጢአታቸው ምክንያት እግዚአብሔር በጣም ተቈጣቸው፣ ሊያጠፋቸውም ፈለገ። ነገር ግን ሙሴ ጸለየላቸው፣ እግዚአብሔርም ጸሎቱን ሰማና አላጠፋቸውም።

Image

ሙሴ ከተራራው ወርዶ ጣዖቱን ስያምልኩ ባየ ጊዜ በጣም ተቈጥቶ እግዚአብሔር ዐሥሩን ትእዛዛት የጻፈባቸውን ድንጋዮች ሰባበረ።

Image

ከዚያም ሙሴ ጣዖቱን ፈጨው፣ በውሃውም ላይ በተነው፣ ለሕዝቡም አጠጣቸው። እግዚአብሔር በሕዝቡ ላይ መቅሠፍት ላከና ብዙዎቻቸው ሞቱ።

Image

ሙሴ እንደ ገና ተራራው ላይ ወጣና እግዚአብሔር ሕዝቡን ይቅር እንዲላቸው ጸለየ። እግዚአብሔር ሙሴን ሰማውና ይቅር አላቸው። ሙሴ የሰባበራቸውን ለመተካት በዐዲስ ጠፍጣፋ ድንጋዮች ላይ የተጻፉትን ዐሥሩን ትእዛዛት ይዞ ከተራራ ወረደ። ከዚያ በኋላ እግዚአብሔር እስራኤላውያንን ከሲና ተራራ ወደ ተስፋዪቱ ምድር መራቸው።

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከዘጸአት 19-34፡፡

14. በምድረ በዳ መቅበዝበዝ

Image

እግዚአብሔር ከእነርሱ ጋር ያደረገው ቃል ኪዳን ክፍል ለሆኑት ሕግጋት እንዲታዘዙ ለእስራኤላውያን ከነገራቸው በኋላ የሲና ተራራን ለቀው ሄዱ። እግዚአብሔርም ሕዝቡን ከሲና ተራራ ከነዓን ተብላ ትጠራ ወደ ነበረችው ወደ ተስፋዪቱ ምድር ይመራቸው ጀመር። የደመናው ዓምድ ከፊት ለፊታቸው ወደ ከነዓን ሄደ፣ እነርሱም ተከተሉት።

Image

እግዚአብሔር የተስፋዪቱን ምድር ለዘሮቻቸው እንደሚሰጣቸው ለአብርሃም፣ ለይስሐቅና ለያዕቆብ ተስፋ ሰጥቶአቸው ነበር፣ ነገር ግን በዚያች ምድር ብዙ የሕዝብ ወገኖች ይኖሩ ነበር። እነርሱም ከነዓናውያን ተብለው ይጠሩ ነበር። ከነዓናውያን እግዚአብሔርን አያመልኩትም ወይም አይታዘዙትም ነበር።ነገር ግን ሐሰተኞች አማልክትን ያመልኩ ነበር፤ ብዙ ክፉ ነገሮችንም ያደርጉ ነበር።

Image

እግዚአብሔር ለእስራኤላውያን እንዲህ ብሎ ነገራቸው፣ ‹‹በተስፋዪቱ ምድር ያሉትን ከነዓናውያንን ሁሉ አጥፉአቸው። ከእነርሱ ጋር ሰላምን አታድርጉ፤ አታግቡአቸውም። ጣዖቶቻቸውን ሁሉ ፈጽማችሁ አጥፉአቸው። ለእኔ ባትታዘዙ፣ በእኔ ፈንታ የእነርሱን ጣዖታት ታመልካላችሁ።››

Image

እስራኤላውያን ወደ ከነዓን ድንበር በደረሱ ጊዜ፣ ሙሴ ከእያንዳንዱ የእስራኤል ነገድ አንድ አንድ ሰው፣ ዐሥራ ሁለት ሰዎችን መረጠ። ሄደው ምድሪቱ ምን እንደምትመስል እንዲሰልሉ መመሪያ ሰጣቸው።ደግሞም ከነዓናውያን ብርቱዎች ወይም ደካሞች መሆናቸውን ለማየት ከነዓናውያንን መሰለል ነበረባቸው።

Image

ዐሥራ ሁለቱ ሰዎች በከነዓን ውስጥ ለአርባ ቀን ተጓዙና ተመልሰው መጡ።መጥተውም ‹‹ምድሪቱ በጣም ለም ነች፤ ሰብሉም የተትረፈረፈ ነው!›› ብለው ለሕዝቡ ነገሩአቸው። ከስችላዮቹ ዐሥሩ ግን፣ ‹‹ከተሞቹ በጣም ብርቱዎች፤ ሰዎቹም ግዙፍ ናቸው! እነርሱን ብንወጋቸው በእርግጥ ያሸንፉናል፤ ይገድሉናልም!›› አሉ።

Image

ወዲያውኑ ሌሎቹ ሁለት ሰላዮች፣ ካሌብና ኢያሱ፣ ‹‹የከነዓን ሰዎች ረጃጅሞችና ብርቱዎች መሆናቸው እውነት ነው፣ ነገር ግን እኛ በእርግጥ እናሸንፋቸዋለን! እግዚአብሔር ስለ እኛ ይዋጋል!›› አሉ።፡

Image

ሕዝቡ ግን ካሌብንና ኢያሱን አልሰሙአቸውም። ሙሴንና አሮንን ተቈጡአቸውና፣ ‹‹ወደዚህ አስከፊ ቦታ ለምን አመጣችሁን? እኛ በጦርነት ከምንሞትና ሚስቶቻችንና ልጆቻችን ባሮች ከሚሆኑ ይልቅ በግብፅ ብንኖር ይሻለን ነበር›› አሉ። ሕዝቡ ወደ ግብፅ መልሶ የሚወስዳቸውን ሌላ መሪ ለመምረጥ ፈለጉ።

Image

እግዚአብሔር በጣም ተቈጣና ወደ መገናኛው ድንኳ መጣ። እንዲህም አለ፣ ‹‹እናንተ በእኔ ላይ ስላመፃችሁ፣ ሕዝቡ ሁሉ በምድረ በዳ ይቅበዘበዛሉ። ከኢያሱና ከካሌብ በቀር ሃያ ዓመትና ከዚያ በላይ የሆናቸው ሁሉ በዚያ ይሞታሉ እንጂ ከቶ ወደ ተስፋዪቱ ምድር አይገቡም›› አላቸው።

Image

ሕዝቡ ይህን በሰሙ ጊዜ፣ ኃጢአት በመሥራታቸው ዐዘኑ። የጦር መሣሪያዎቻቸውን ይዘው የከነዓንን ሰዎች ለመውጋት ሄዱ። ሙሴ ግን እግዚአብሔር ከእነርሱ ጋር ስላልነበረ እንዳይሄዱ አስጠነቀቃቸው፣ ነገር ግን እርሱን አልሰሙትም።

Image

እግዚአብሔር አብሮአቸው ወደ ጦርነቱ አልሄደም፣ ስለዚህ ተሸነፉ፤ ብዙዎቻቸውም ተገደሉ። ከዚያም እስራኤላውያን ከከነዓን ተመለሱና በምድረ በዳ ለአርባ ዓመት ተቅበዘበዙ።

Image

የእስራኤል ሕዝብ በምድረ በዳ በተቅበዘበዙባቸው አርባ ዓመታት እግዚአብሔር የሚያስፈልጋቸውን ሰጣቸው። ከሰማይ ‹‹መና›› ተብሎ የሚጠራ ምግብ ሰጣቸው። ደግሞም ሥጋ ይበሉ ዘንድ ወደ ሰፈራቸው ድርጭቶችን ላከላቸው። በዚያን ጊዜ ሁሉ እግዚአብሔር ልብሳቸውና ጫማቸው እንዳያልቅ አደረገ።

Image

እግዚአብሔር ተአምራዊ በሆነ መንገድ ውሃ እንኳ ከአለት ሰጣቸው። ይህም ሁሉ ሆኖ ግን የእስራኤል ሕዝብ በእግዚአብሔርና በሙሴ ላይ አማረሩ፤ አጕረመረሙም። ቢሆንም፣ እግዚአብሔር ለአብርሃም፣ ለይስሐቅና ለያዕቆብ ለሰጠው ተስፋ አሁንም ታማኝ ነበር።

Image

ሕዝቡ ምንም ውሃ ባልነበራቸው በሌላ ጊዜ እግዚአብሔር ለሙሴ፣ ‹‹አለቱን ተናገረው፣ ከእርሱም ውሃ ይወጣል›› አለው። ነገር ግን ሙሴ ለአለቱ በመናገር ፈንታ በበትር ሁለት ጊዜ ስለ መታው በሕዝቡ ሁሉ ፊት እግዚአብሔርን አላከበረም። ሁለም ሰው እንዲጠጣ ከአለቱ ውሃ ወጣ፣ ነገር ግን እግዚአብሔር በሙሴ ላይ ተቈጣና፣ ‹‹ወደ ተስፋዪቱ ምድር አትገባም›› አለው።

Image

እስራኤላውያን ለአርባ ዓመት በምድረ በዳ ከተቅበዘበዙ በኋላ በእግዚአብሔር ላይ ያመፁት ሁሉ ሞቱ። ከዚያም እግዚአብሔር ሕዝቡን እንደ ገና ወደ ተስፋዪቱ ምድር ዳርቻ መራቸው። አሁን ሙሴ በጣም አርጅቶ ነበር፣ ስለዚህ ሕዝቡን በመምራት እንዲያግዘው እግዚአብሔር ኢያሱን መረጠ። ደግሞም እግዚአብሔር አንድ ቀን እንደ ሙሴ ያለ ሌላ ነቢይ እንደሚልክ ለሙሴ ተስፋ ሰጠው።

Image

ከዚያም እግዚአብሔር የተስፋዪቱን ምድር ለማየት ይችል ዘንድ ወደ ተራራ ራስ ላይ እንዲወጣ ለሙሴ ነገረው። ሙሴ የተስፋዪቱን ምድር ዐየ፣ ነገር ግን እግዚአብሔር ወደ እርስዋ እንዲገባ አልፈቀደለትም። ከዚያም ሙሴ ሞተ፣ እስራኤላውያንም ለሠላሳ ቀናት አለቀሱለት። ኢያሱም ዐዲሱ መሪአቸው ሆነ። ኢያሱ በእግዚአብሔር ያመነና ለእግዚአብሔር የሚታዘዝ ስለ ነበር ጥሩ መሪ ነበር።

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከዘጸአት 16-17፤ ዘኍልቁ 10-14፤ 20፤ 27፤ ዘዳግም 34፡፡

15. የተስፋይቱ ምድር

Image

በመጨረሻ እስራኤላውያን ወደ ተስፋዪቱ ምድር፣ ወደ ከነዓን የሚገቡበት ጊዜ ደረሰ። ኢያሱ በብርቱ ግንብ ተጠብቃ ወደ ነበረችው የከነዓናውያን ከተማ ወደ ኢያሪኮ ሁለት ሰላዮችን ላከ። በዚያች ከተማ ሰላዮቹን የሸሸገችና ኋላ ላይ እንዲያመልጡ የረዳቻቸው ረዓብ የተባለች ጋለሞታ ትኖር ነበር። እርስዋ ይህን ያደረገችው በእግዚአብሔር ስላመነች ነው። ሰላዮቹ፤ እስራኤላውያን ኢያሪኮን በሚያጠፉበት ጊዜ ረዓብንና ቤተ ሰብዋን እንደሚያድኑአቸው ቃል ገቡላት።

Image

እስራኤላውያን ወደ ተስፋዪቱ ምድር ለመግባት የዮርዳኖስን ወንዝ መሻገር ነበረባቸው። እግዚአብሔር፣ ‹‹መጀመሪያ ካህናቱ እንዲሻገሩ አድርግ›› ብሎ ለኢያሱ ነገረው። ካህናቱ ወደ ዮርዳኖስ ወንዝ መግባት በጀመሩ ጊዜ፣ እስራኤላውያን በደረቅ መሬት መሻገር ይችሉ ዘንድ ከላይ በኩል ይፈስ የነበረ ውሃ መፍሰሱን አቆመ።

Image

ሕዝቡ የዮርዳኖስን ወንዝ ከተሻገሩ በኋላ፣ እግዚአብሔር ኃይለኛውን የኢያሪኮ ከተማ እንዴት እንደሚያጠፋት ለኢያሱ ነገረው። ሕዝቡ ለእግዚአብሔር ታዘዙ። ወታደሮቹና ካህናቱ ልክ እግዚአብሔር እንደ ነገራቸው በቀን አንዴ ለስድስት ቀናት የኢያሪኮን ከተማ ዞሩ።

Image

ከዚያም በሰባተኛው ቀን፣ እስራኤላውያን ሰባት ጊዜ ከተማይቱን ዞሩ። ለመጨረሻ ጊዜ ከተማዪቱን እየዞሩ እያሉ ወታደሮቹ ጮኹ፣ ካህናቱም መለከቶቻቸውን ነፉ።

Image

ከዚያም በኢያሪኮ ዙሪያ የነበረው ግንብ ወደቀ! እግዚአብሔር እንዳዘዘው እስራኤላውያን በከተማይቱ የነበረውን ነገር ሁሉ አጠፉ። የእስራኤላውያን ወገን የሆኑትን ረዓብንና ቤተ ሰብዋን ብቻ አዳኑአቸው። በከነዓን የሚኖሩ ሌሎች ሕዝቦች እስራኤላውያን ኢያሪኮን እንዳጠፉአት በሰሙ ጊዜ፣ እስራኤላውያን እነርሱንም ደግሞ እንደሚያጥቋቸው በማሰብ ፈሩ።

Image

እግዚአብሔር በከነዓን ካሉ ከማናቸውም የሕዝብ ወገኖች ጋር የሰላም ስምምነት እንዳያደርጉ እስራኤላውያንን አዞአቸው ነበር። ነገር ግን ገባዖናውያን የተባሉት ከከነዓናውያን ሕዝብ ወገኖች አንዱ የሆኑት፣ ከከነዓን ራቅ ብሎ ከሚገኝ ቦታ የመጡ መሆናቸውን ለኢያሱ ዋሽተው ነገሩት። ከእነርሱ ጋር የሰላም ስምምነት እንዲያደርግ ኢያሱን ጠየቁት። ገባዖናውያን ከየት እንደ ሆኑ ኢያሱና እስራኤላውያን እግዚአብሔርን አልጠየቁም። ስለዚህ ኢያሱ ከእነርሱ ጋር የሰላም ስምምነት አደረገ።

Image

ገባዖናውያን እንዳታለሉአቸው ባወቁ ጊዜ እስራኤላውያን ተናደዱ፣ ነገር ግን በእግዚአብሔር ፊት የገቡት ቃል ስለ ነበር ከእነርሱ ጋር ያደረጉትን የሰላም ስምምነት ጠበቁ። ቆየት ብሎ በሌላ ጊዜ፣ በከነዓን የነበሩ አሞራውያን የሚባሉ የሌላ ሕዝብ ወገን ነገሥታት፣ የገባዖን ሰዎች ከእስራኤላውያን ጋር የሰላም ስምምነት እንዳደረጉ ሰሙ፣ ስለዚህ ጦር ሠራዊታቸውን አንድ ላይ አስተባበሩና ገባዖናውያንን ወጉ። ገባዖናውያንም እርዳታ ጥየቃ ወደ ኢያሱ መልእክት ላኩ።

Image

ስለዚህ ኢያሱ የእስራኤልን ጦር ሠራዊት ሰበሰበና ወደ ገባዖናውያን ለመድረስ ሌሊቱን ሙሉ ተጓዙ። በማለዳ ሳያስቡት የአሞራውያንን ጦር ሠራዊት መቱ።

Image

በዚያን ቀን እግዚአብሔር ለእስራኤላውያን ተዋጋ። አሞራውያንን አደናገራቸውና ትልልቅ የበረዶ ድንጋይ ልኮ ከአሞራውያን ብዙዎችን ገደለ።

Image

ደግሞ እግዚአብሔር እስራኤላውያን አሞራውያንን ፈጽመው ለማጥፋት በቂ ጊዜ ይኖራቸው ዘንድ ፀሐይ በሰማይ በአንድ ቦታ እንድትቆም አደረገ። በዚያን ቀን እግዚአብሔር ለእስራኤል ታላቅ ድል አጐናጸፋቸው።

Image

እግዚአብሔር እነዚያን ጦር ሠራዊት ካጠፉ በኋላ፣ ብዙዎቹ የከነዓናውያን ሕዝብ ወገኖች እስራኤልን ለመውጋት በአንድነት ተሰበሰቡ። ነገር ግን ኢያሱና እስራኤላውያን ወጉና አጠፉአቸው።

Image

ከዚህ ጦርነት በኋላ እግዚአብሔር ለእያንዳንዱ ለእስራኤል ነገድ ከተስፋዪቱ ምድር የሚደርሰውን ክፍል ሰጠው። ከዚያም እግዚአብሔር ለእስራኤል በድንበሮችዋ ሁሉ ሰላምን ሰጣት።

Image

ኢያሱ ባረጀ ጊዜ፣ የእስራኤልን ሕዝብ ሁሉ አንድ ላይ ጠራ። ከዚያም ኢያሱ እግዚአብሔር በሲና ከእስራኤላውያን ጋር ላደረገው ቃል ኪዳን ሕዝቡ የመታዘዝ ግዴታ እንዳለበቸው አስታወሳቸው። ሕዝቡ ለእግዚአብሔር ታማኞች ሆነው ለመኖርና ሕግጋቱን ለመከተል ቃል ገቡ።

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከኢያሱ 1-24፡፡

16. ነፃ አውጪዎቹ

Image

ኢያሱ ከሞተ በኋላ፣ እስራኤላውያን እግዚአብሔርን አልታዘዙም፤ የቀሩትንም ከነዓናውያን ከመካከላቸው አላስወጡም፤ ወይም የእግዚአብሔርን ሕግ አልታዘዙም። እስራኤላውያን እውነተኛ አምላክ የሆነውን ያህዌን ከማምለክ ይልቅ የከነዓናውያንን አማልክት ማምለክ ጀመሩ። እስራኤላውያን ንጉሥ አልነበራቸውም፣ ስለዚህ እያንዳንዱ ትክክል መስሎ የሚታየውን ሁሉ ያደርግ ነበር።

Image

እስራኤላውያን እግዚአብሔርን አለመታዘዛቸውን በመቀጠላቸው፣ እግዚአብሔር ጠላቶቻቸው እንዲያሸንፏቸው አደረገ። እነዚህ ጠላቶቻቸው የእስራኤላውያንን ሀብት ሁሉ ዘረፉ፣ንብረታቸውንም አወደሙ፣ አብዛኞቻቸውንም ገደሉ። እስራኤላውያን እግዚአብሔርን ባለመታዘዝና በጠላቶቻቸው በመጨቆን ብዙ ዘመናትን ካሳለፉ በኋላ፣ ንስሐ ገቡ፤ እግዚአብሔርንም ከጠላቶቻቸው እንዲያድናቸው ጠየቁ።

Image

ከዚያም እግዚአብሔር ከጠላቶቻቸው የሚያድናቸውን ነፃ አውጪ ላከላቸው፤ ለምድሪቱም ሰላምን አመጣ። ነገር ግን ሰዎቹ እግዚአብሔርን እንደገና ረሱ። ጣዖትንም ማምለክ ጀመሩ፤ ስለ ሆነም እግዚአብሔር በአቅራቢያቸው የሚገኙትን ጠላቶቻቸውን ምድያማውያንን አስንሣባቸው፣ አሸነፉአቸውም።

Image

ምድያማውያን የእስራኤላውያንን ሰብል ሁሉ ለሰባት ዓመታት ወሰዱ። እስራኤላውያን በጣም ፈርተው ስለ ነበር ምድማውያን እንዳያገኙአቸው፣ በየሸለቆውና በየዋሻው ይሸሽጉ ነበር። በመጨረሻም እንዲያድናቸው ወደ እግዚአብሔር ጮኹ።፡

Image

አንድ ቀን፣ ጌዴዎን የሚባል እስራኤላዊ ምድያማውያን ሰብሉን እንዳይወስዱበት ተደብቆ እህል ይወቃ ነበር። የእግዚአብሔርም መልአክ ወደ ጌዴዎን መጥቶ እንዲህ አለው ‹‹አንተ ብርቱ ተዋጊ ሰው እግዚአብሔር ከአንተ ጋር ነው። ሂድና እስራኤልን ከምድያማውያን አድን።››

Image

የጌዴዎን አባት ለጣዖት አምልኮ የተዘጋጀ መሠዊያ ነበረው። እግዚአብሔርም ጌዴዎንን ያንን መሠዊያ እንዲያፈርስ ተናገረው። ነገር ግን ጌዴዎን ሕዝቡን ስለ ፈራ እስኪመሽ ድረስ ጠበቀ። ከዚያም መሠዊያውን አፈራረሰው፤ እስኪደቅቅ ድረስም ሰባበረው። በአጠገቡም ለእግዚአብሔር ዐዲስ መሠዊያን አዘጋጀ። ለእግዚአብሔርም መሥዋዕትን ሠዋበት።

Image

በማግስቱ ጠዋት ሕዝቡ አንድ ሰው መሠዊያቸውን እንዳፈራረሰው ተመልክተው እጅግ ተበሳጩ። ጌዴዎንን ለመግደል ወደ ጌዴዎን ቤት ሄዱ። ነገር ግን የጌዴዎን አባት ‹‹ለምን አምላካችሁን ለማገዝ ትሞክራላችሁ? እርሱ አምላክ ከሆነ ራሱን ይከላከል!›› አላቸው። ይህንንም ስላለ ሕዝቡ ጌዴዎንን አልገደሉትም።

Image

ምድያማውያን አስራኤላውያንን ለመዝረፍ እንደ ገና መጡ። ቊጥራቸው እጅግ ብዙ ስለ ነበር ማንም ሊቈጥራቸው አይችልም ነበር። ጌዴዎንም ምድያማውያንን ለመውጋት እስራኤላውያንን ጠራ። እግዚአብሔር እርሱን ተጠቅሞ እስራኤልን ያድን እንደ ሆነ ለማረጋገጥ ጌዴዎን ሁለት ምልክቶችን ከእግዚአብሔር ጠየቀ።

Image

የመጀመሪያው ምልክት፦የበግ ፀጉር በምድር ላይ አድርጎ የጠዋቱ ጤዛ በበግ ፀጉር ላይ ብቻ እንጂ በምድር ላይ እንዳይሆን ጠየቀ። እግዚአብሔርም እንደዚያው አደረገ። በሚቀጥለው ምሽት ጌዴዎን እግዚአብሔርን ፤ መሬቱ በጠዋቱ ጤዛ እንዲረጥብ ጨርቁ ግን ደረቅ እንዲሆን ጠየቀ። እግዚአብሔርም እንደዚያው አደረገ። እነዚህ ሁለቱ ምልክቶች እግዚአብሔር እርሱን ተጠቅሞ እስራኤልን ከምድያም እንደሚያድን ለጌዴዎን ማስረጃ ሆኑለት።

Image

32,000 እስራኤላውያን ወታደሮች ወደ ጌዴዎን መጡ፣ ነገር ግን እግዚአብሔር ቊጥራቸው ብዙ ነው አለው። ስለዚህ ጌዴዎን መዋጋት የፈሩትን 22,000 ወታደሮችን ወደ ቤታቸው መለሳቸው። እግዚአብሔር ጌዴዎንን አሁንም የወታደሩ ቊጥር ብዙ ነው አለው። ስለሆነም ጌዴዎን 300 ወታደሮችን አስቀርቶ ሌሎቹን ወደ ቤታቸው መለሳቸው።

Image

በዚያን ሌሊት እግዚአብሔር ጌዴዎንን ‹‹ወደ ምድያማውያን ጦር ሠፈር ውረድ፣ የሚሉትንም ስትሰማ ከዚያ በኋላ ፈጽሞ አትፈራቸውም›› አለው። ስለ ሆነም ጌዴዎን ወደ ምድያማውያን ጦር ሠፈር በዚያው ሌሊት ወርዶ አንድ የምድያም ወታደር ለጓደኛው በሕልሙ ያየውን ነገር ሲነገረው ሰማ፤ ጓደኛውም መልሶ “ይህ ሕልም የሚለው የጌድዎን ጦር ምድያማውያንን እንደሚያሸንፍ ነው” አለ። ጌዴዎን ይህን በሰማ ጊዜ ለእግዚአብሔር ሰገደ።

Image

ከዚያም ጌዴዎን ወደ ወታደሮቹ ተመልሶ ለእያንዳንዳቸው ቀንደ መለከት፣ ማሰሮ እና ችቦ ሰጣቸው።እነሱም የምድያም ሠራዊት ተኝቶ እያለ ሰፍሮ የነበረበትን የጦር ሠፈር ከበቡ። የጌድዎን 300 ወታደሮች ችቦ በማሰሮው ውስጥ ይዘው ስለነበር የምድያም ወታደሮች የችቦውን ብርሃን ማየት አልቻሉም።

Image

ከዚያም የጌዴዎን ወታሮች በሙሉ በተመሳሳይ ጊዜ ማሰሮዎቻቸውን ሰበሩ፤ ወዲያው የችቦው ብርሃን በድንገት አበራ። ቀንደ መለከታቸውን እየነፉ ‹‹የእግዚአብሔርና የጌዴዎን ሰይፍ›› እያሉ ጮኹ።

Image

እግዚአብሔርም ምድያማውያንን ግራ አጋባቸው፣ እርስ በርሳቸውም ተገዳደሉ። ወዲያው በየቤታቸው ያሉ እስራኤላውያን ምድያማውያንን ለማባረር እንዲረዱ ተጠሩ። ብዙዎችን ምድማውያንን ገደሉ የተቀሩቱንም ከእስራኤል ምድር አባረሩ። በዚያን ቀን 120,000 የምድያም ሰዎች ሞቱ። እግዚአብሔርም እስራኤልን አዳነ።

Image

ሕዝቡም ጌዴዎንን ንጉሣቸው እንዲሆን ፈለጉ። ጌዴዎን ግን ይህን እንዲያደርጉ አልፈቀደላቸውም፤ ነገር ግን እያንዳንዳቸው ከምድያማውያን የወሰዱአቸውን የወርቅ ቀለበት እንዲያመጡ ጠየቃቸው። ሕዝቡም ለጌዴዎን እጅግ ብዙ ወርቅ ሰጡት።

Image

ጌዴዎንም ወርቁን አቅልጦ ሊቀ ካህኑ እንደሚለብሰው ልዩ ልብስ አድርጎ አሠራው። ነገር ግን ሕዝቡ ያንን ልብስ እንደ ጣዖት ሊያመልኩት ጀመሩ። ከዚያም የተነሣ እግዚአብሔር ጠላቶቻቸው እንዲያሸንፉአቸው አድርጎ ቀጣቸው። በመጨረሻም ሕዝቡ አሁንም እግዚአብሔር እንዲያድናቸው ጠየቁ፣ እግዚአብሔርም ሌላ አዳኝ ላከላቸው።

Image

እንዲህ ያለው ሁኔታ ብዙ ጊዜ ተደጋገመ። እስራኤላውያን ኃጢአትን ያደርጋሉ፣ እግዚአብሔር ይቀጣቸዋል፣ እንደ ገና ንስሐ ይገባሉ፣ እግዚአብሔርም ያድናቸው ዘንድ አዳኝን ይልክላቸዋል። ለብዙ ዓመታት እግዚአብሔር እስራኤልን ከጠላቶቻቸው ለማዳን ብዙ ነፃ አውጪዎችን ልኮላቸዋል።

Image

በመጨረሻም፣ ሕዝቡ እንደሌሎቹ ሁሉ አሕዛብ ንጉሥን እንዲሰጣቸው እግዚአብሔርን ጠየቁ። በጦርነት የሚመራቸው፣ ረጅምና ጠንካራ የሆነ ንጉሥ እንዲኖራቸው ፈለጉ። እግዚአብሔር ግን ይህንን ጥያቄአቸውን አልወደደም፣ ሆኖም እንደ ፈለጉት ንጉሥን ሰጣቸው።

__የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- መሳፍንት 1-5፣ 6-8፡፡

17. እግዚአብሔር ከዳዊት ጋር ያደረገው ቃል ኪዳን

Image

ሳኦል የመጀመሪያው የእስራኤል ንጉሥ ነበር፡፡ እርሱ ልክ ሕዝቡ እንደ ፈለጉት ረጅምና መልከ መልካም ነበር፡፡ ሳኦል እስራኤልን በገዛባቸው በመጀመሪያዎቹ ጥቂት ዓመታት ጥሩ ንጉሥ ነበር፡፡ ከዚያ በኋላ ግን ለእግዚአብሔር ያልታዘዘ ክፉ ሰው ሆነ፣ ስለዚህ እግዚአብሔር አንድ ቀን በሳኦል ቦታ ንጉሥ የሚሆን የተለየ ሰው መረጠ፡፡

Image

እግዚአብሔር ከሳኦል በኋላ ንጉሥ እንዲሆን ዳዊት የተባለውን እስራኤላዊ ወጣት መረጠ፡፡ ዳዊት ከቤተ ልሔም ከተማ የሆነ የበጎች እረኛ ነበር፡፡ ዳዊት በተለያዩ ጊዜያት የአባቱን በጎች ሲጠብቅ፣ በጎቹን ለማጥቃት የመጡትን አንበሳና ድብ ገድሎ ነበር፡፡ ዳዊት በእግዚአብሔር የሚያምንና ለእርሱም የሚታዘዝ ትሑትና ጻድቅ ሰው ነበር፡፡

Image

ዳዊት ታላቅ ወታደርና መሪ ሆነ፡፡ ዳዊት ገና ወጣት በነበረ ጊዜ ጎልያድ ተብሎ ከሚጠራ ግዙፍ ሰው ጋር ተዋጋ፡፡ ጎልያድ የሠለጠነ ወታደር፣ በጣም ብርቱ፣ እንዲሁም ቁመቱ ከሞላ ጎደል ሦስት ሜትር ነበር፡፡ ነገር ግን እግዚአብሔር ጎልያድን ገድሎ እስራኤልን እንዲያድን ዳዊትን ረዳው፡፡ ከዚያ በኋላ ዳዊት በሕዝቡ የተመሰገነባቸውን፣ በእስራኤል ጠላቶች ላይ ብዙ ድሎችን አገኘ፡፡

Image

ሳኦል ሕዝቡ ለዳዊት በነበራቸው ፍቅር ቀና፡፡ ሳኦል ብዙ ጊዜ ዳዊትን ሊገድለው ሞከረ፣ ስለዚህ ዳዊት ከሳኦል ተሸሸገ፡፡ አንድ ቀን ሳኦል ይገድለው ዘንድ ዳዊትን እየፈለገው ነበር፡፡ ሳኦል ዳዊት ከእርሱ ተሸሽጎበት ወደ ነበረው ዋሻ ሄደ፣ ነገር ግን ሳኦል አላየውም ነበር፡፡ ዳዊትም ወደ ሳኦል በጣም ተጠግቶ ነበርና ሊገድለው ይችል ነበር፣ ነገር ግን አልገደለውም፡፡ በዚህ ፈንታ ዳዊት ንጉሥ ለመሆን እንዳልገደለው ለሳኦል ለማረጋገጥ የሳኦልን ልብስ ዘርፍ ቈረጠ፡፡

Image

በመጨረሻ፣ ሳኦል በጦርነት ሞተ፣ ዳዊትም የእስራኤል ንጉሥ ሆነ፡፡ ዳዊት ጥሩ ንጉሥ ነበረ፣ ሕዝቡም ወደዱት፡፡ እግዚአብሔር ዳዊትን ባረከው፣ ስኬታማም አደረገው፡፡ ዳዊት ብዙ ጦርነቶችን ተዋጋ፣ የእስራኤልን ጠላቶች እንዲያሸንፍም እግዚአብሔር ረዳው፡፡ ዳዊት ኢየሩሳሌምን አሸንፎ ያዘና ዋና ከተማው አደረጋት፡፡ በዳዊት ንግሥና ጊዜ፣ እስራኤል ኃያልና ባለ ጠጋ ሆነች፡፡

Image

ዳዊት እስራኤላውያን ሁሉ እግዚአብሔርን የሚያመልኩበትና ለእርሱ መሥዋዕቶችን የሚያቀርቡበት ቤተ መቅደስ ለመሥራት ፈለገ፡፡ ሕዝቡ ለ400 ዓመት ገደማ ሙሴ በሠራው የመገናኛ ድንኳን እግዚአብሔርን ያመልኩና መሥዋዕቶችን ያቀርቡለት ነበር፡፡

Image

ነገር ግን እግዚአብሔር እንዲህ የሚል መልዕክት በነቢዩ ናታን በኩል ወደ ዳዊት ላከው፣ ‹‹አንተ የጦርነት ሰው ስለ ሆንክ ይህን ቤተ መቅደስ ለእኔ አትሠራልኝም፡፡ ልጅህ ይሠራዋል፡፡ ነገር ግን አንተን በእጅጉ እባርክሃለሁ፡፡ ከዝርያዎችህ አንዱ በሕዝቤ ላይ ንጉሥ ሆኖ ለዘላለም ይገዛል!›› ለዘላለም የሚገዛው ብቸኛው የዳዊት ዝርያ፣ መሲሑ ነው፡፡ መሲሑ የዓለምን ሕዝቦች ከኃጢአታቸው የሚያድናቸው የእግዚአብሔር ምርጥ ነው፡፡

Image

ዳዊት እነዚህን ቃሎች በሰማ ጊዜ፣ ይህንን ታላቅ ክብርና ብዙ በረከቶችን ሊሰጠው ቃል ስለ ገባለት ወዲያውኑ እግዚአብሔርን አመሰገነ አወደሰም፡፡ ዳዊት እግዚአብሔር እነዚህን ነገሮች መቼ እንደሚያደርግ ግን አላወቀም፡፡ ነገር ግን እስራኤላውያን መሲሑ እስከሚመጣ ረዘም ላለ ጊዜ፣ ከሞላ ጐደል 1000 ዓመታት መጠበቅ ነበረባቸው፡፡

Image

ዳዊት በፍትሕና በታማኝነት ለብዙ ዓመታት ገዛ፣ እግዚአብሔርም ባረከው። ይሁን እንጂ፣ ወደ ሕይወቱ መጨረሻ በእግዚአብሔር ላይ ክፉኛ ኃጢአት ሠራ።

Image

አንድ ቀን የዳዊት ወታደሮች በሙሉ ከቤታቸው ርቀው ጦርነት በሚዋጉበት ጊዜ፣ እርሱ ከቤተ መንግሥቱ ውጪ ሆኖ አንዲት ቆንጆ ሴት ገላዋን ስትታጠብ ዐየ። ስምዋ ቤርሳቤህ ነበር።

Image

ዳዊት ፊቱን ከሷ በማዞር ፈንታ፣ ወደ እርሱ እንዲያመጣት ሰው ላከ፡፡ ከእርስዋ ጋር ተኛና ወደ ቤቷ መልሶ ላካት፡፡ ከጥቂት ጊዜ በኋላ ቤርሳቤህ አርግዣለሁ ብላ ወደ ዳዊት መልእክት ላከች፡፡

Image

ኦርዮ ተብሎ የሚጠራው የቤርሳቤህ ባል ከዳዊት ምርጥ ወታደሮች አንዱ ነበር፡፡ ዳዊት ኦርዮን ከጦርነቱ ቦታ ጠራውና ከሚስቱ ጋር እንዲሆን ነገረው፡፡ ነገር ግን ኦርዮ የቀሩት ወታደሮች በጦርነት ላይ እያሉ ወደ ቤት አልሄድም አለ፡፡ ስለዚህ ዳዊት ኦርዮንን ወደ ጦርነቱ መልሶ ላከውና ይገደል ዘንድ ጠላት እጅግ በበረታበት ቦታ እንዲያሰልፈው ለሠራዊቱ ዋና አዛዥ ነገረው፡፡

Image

ኦርዮ ከተገደለ በኋላ ዳዊት ቤርሳቤህን አገባት፡፡ በኋላ እርስዋ ለዳዊት ወንድ ልጅን ወለደችለት፡፡ እግዚአብሔር ዳዊት ስላደረገው ነገር በጣም ተቈጣ፣ ኃጢአቱ እንዴት ክፉ እንደ ነበረ ለዳዊት እንዲነግረውም እግዚአብሔር ነቢዩን ናታንን ላከው፡፡ ዳዊት ኃጢአቱን ተናዘዘና እግዚአብሔር ይቅር አለው፡፡ ዳዊት በቀረው የሕይወቱ ዘመን በአስቸጋሪ ጊዜያት እንኳ፣ እግዚአብሔርን ተከተለ፤ ታዘዘውም፡፡

Image

ነገር ግን ዳዊት ለሠራው ኃጢአት ቅጣት እንዲሆን ሆኖ የተወለደው ልጁ ሞተበት፡፡ ደግሞም በቀረው የሕይወቱ ዘመን በዳዊት ቤተ ሰብ ውጊያ ነበረ፣ የዳዊት ኃይልም በእጅጉ ተዳከመ፡፡ ዳዊት ለእግዚአብሔር ያልታመነ ቢሆንም እንኳ፣ እግዚአብሔር አሁንም ለተስፋዎቹ የታመነ ነበረ፡፡ በኋላ ዳዊትና ቤርሳቤህ ሌላ ወንድ ልጅ ወለዱ፣ ስሙንም ሰሎሞን አሉት፡፡

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከ1ኛ ሳሙኤል 10፡15-19፤ 24፤ 31፤ 2ኛ ሳሙኤል 5፤ 7፤ 11-12፡፡

18. ለሁለት የተከፈለው መንግሥት

Image

ከብዙ ዓመታት በኋላ፣ ዳዊት ሞተ፣ ልጁ ሰሎሞንም እስራኤልን ይገዛ ጀመር፡፡ እግዚአብሔር ሰሎሞንን ተናገረውና ከሁሉ በላይ ምን እንደሚፈልግ ጠየቀው፡፡ ሰሎሞን ጥበብን እንዲሰጠው በለመነ ጊዜ፣እግዚዘብሔር ደስ አለውና በዓለም ላይ ካሉ ሰዎች ሁሉ በላይ እጅግ በጣም ጠቢብ ሰው አደረገው፡፡ ሰሎሞን ብዙ ነገሮችን የሚያውቅ በጣም ጠቢብ ፈራጅ ሆነ፡፡ ደግሞም እግዚአብሔር በጣም ባለ ጠጋ አደረገው፡፡

Image

ሰሎሞን በኢየሩሳሌም አባቱ ዳዊት ሊሠራ ያቀደውንና ለግንባታው የሚያስፈልጉ ነገሮች የሰበሰበለትን ቤተ መቅደስ ሠራ፡፡ አሁን ሕዝቡ በመገናኛው ድንኳ ፈንታ በቤተ መቅደስ እግዚአብሔርን አመለኩ መሥዋዕትንም አቀረቡለት፡፡ እግዚአብሔር መጥቶ በቤተ መቅደሱ ሆነ፣ በዚያም ከሕዝቡ ጋር ኖረ፡፡

Image

ነገር ግን ሰሎሞን የሌሎች አገሮች ዜጎች የሆኑ ሴቶችን ወደደ። ከሞላ ጐደል 1000 የሚሆኑ ብዙ ሴቶችን በማግባት ለእግዚአብሔር አልታዘዘም! ከእነዚህ ሴቶች ብዙዎቹ ከሌላ አገሮች የመጡ ነበሩ፣ እነርሱም ጣዖቶቻቸውን አምጥተው ማምለካቸውን ቀጠሉ። ሰሎሞንም በሸመገለ ጊዜ፣ እርሱም ደግሞ የእነርሱን አማልክት አመለከ።

Image

እግዚአብሔር በሰሎሞን ላይ ተቈጣ፣ ሰሎሞን ባለመታመኑ እንደ መቀጣጫ እንዲሆን ከእርሱ ሞት በኋላ የእስራኤልን ሕዝብ ወደ ሁለት መንግሥታት እንደሚከፍል ተናገረ።

Image

ሰሎሞን ከሞተ በኋላ ልጁ ሮብዓም ነገሠ፡፡ ሮብዓም ሞኝ ነበረ፡፡ የእስራኤል ሕዝብ በሙሉ ንጉሥነቱን ሊያጸድቁለት ተሰብስበው መጡ፡፡ ሰሎሞን ብዙ ከባድ ሥራ እንዳሠራቸውና ብዙ ግብር እንዳስከፈላቸው ለሮብዓም ቅሬታቸውን ተናገሩ፡፡

Image

ሮብዓም በሞኝነት እንዲህ ብሎ መለሰላቸው፣ ‹‹አባቴ ሰሎሞን ከባድ ሥራ አሠርቶናል ብላችሁ ዐስባችኋል፣ ነገር ግን እኔ ከእርሱ የባሰ ከባድ ሥራ አሠራችኋለሁ፣ ከእርሱ የባሰም በኃይል እቀጣችኋለሁ፡፡››

Image

ስለዚህ ዐሥሩ የእስራኤል ሕዝብ ነገዶች በሮብዓም ላይ ዓመፁ፡፡ ሁለት ነገዶች ብቻ ለእርሱ ባላቸው ታማኝነት ቀጠሉ፡፡ እነዚህ ሁለት ነገዶች የይሁዳ መንግሥት ሆኑ፡፡

Image

በሮብዓም ላይ ያመፁት ሌሎቹ ዐሥር የእስራኤል ሕዝብ ነገዶች ኢዮርብዓም የተባለውን ሰው ንጉሣቸው አድርገው ሾሙት፡፡ በምድሪቱ ሰሜናዊ ክፍል መንግሥታቸውን አቋቋሙ፤ የእስራኤል መንግሥት ተብለውም ተጠሩ፡፡

Image

ኢዮርብዓም በእግዚአብሔር ላይ ዓመፀና ሕዝቡ ኃጢአት እንዲሠሩ አደረገ፡፡ በይሁዳ መንግሥት ባለው ቤተ መቅደስ እግዚአብሔርን በማምለክ ፈንታ ሕዝቡ ያመልኩአቸው ዘንድ ሁለት ጣዖታትን ሠራላቸው፡፡

Image

የይሁዳና የእስራኤል መንግሥታት ጠላቶች ሆኑና ብዙ ጊዜ እርስ በርስ ተዋጉ።

Image

በዐዲሲቱ የእስራኤል መንግሥት የነገሡት ነገሥታቱ ሁሉ ክፉዎች ነበሩ። ከእነዚህ ነገሥታት አብዛኞቹ፣ በእነርሱ ቦታ መንገሥ በፈለጉ ሌሎች እስራኤላውያን ተገደሉ።

Image

ነገሥታቱ ሁሉና አብዛኞቹ የእስራኤል መንግሥት ሕዝብ ጣዖትን አመለኩ፡፡ የጣዖት አምልኮአቸው ብዙውን ጊዜ ግብረ ገብነት የጐደለው የግብረ ሥጋ ግንኙነትና አንዳንድ ጊዜ እንደውም ልጆችን መሠዋትንም ያካተተ ነበር፡፡

Image

የይሁዳ ነገሥታት የዳዊት ዝርያዎች ነበሩ፡፡ ከእነዚህ ነገሥታት አንዳንዶቹ በቅንነት የገዙና እግዚአብሔርን ያመለኩ ጥሩ ሰዎች ነበሩ፡፡ ነገር ግን አብዛኞቹ የይሁዳ ነገሥታት ክፉዎችና ብልሹዎች ነበሩ፣ ጣዖታትንም ያመልኩ ነበር፡፡ አንዳንዶቹ ነገሥታት ልጆቻቸውን እንኳ ለሐሰት አማልክት ሠውተዋል፡፡ ደግሞም አብዛኞቹ የይሁዳ ሕዝብ በእግዚአብሔር ላይ ዓመፁ፤ ሌሎች አማልክትንም አመለኩ፡፡

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከ1ኛ ነገሥት 1-6፤ 11-12፡፡

19. ነቢያቱ

Image

እግዚአብሔር በእስራኤላውያን ታሪክ በሙሉ ነቢያትን ይልክላቸው ነበር፡፡ ነቢያቱም መልእክትን ከእግዚአብሔር ሰምተው ለሕዝቡ ይነግሩ ነበር፡፡

Image

አክአብ በእስራኤል መንግሥት ላይ በነገሠ ጊዜ ኤልያስ ነቢይ ነበረ፡፡ አክዓብ በኣል ተብሎ የሚጠራ የሐሰት አምላክ እንዲያመልኩ ሕዝቡን ያደፋፈረ ክፉ ሰው ነበር፡፡ ኤልያስ ለአክዓብ፣ ‹‹እኔ እንዲዘንብ እስከምናገር ድረስ በእስራኤል ዝናብ ወይም ጠል አይኖርም›› አለው፡፡ ይህ አክዓብን በጣም አስቈጣው፡፡

Image

አክዓብ ኤልያስን ሊገድለው ይፈልግ ስለ ነበር እግዚአብሔር ኤልያስን ይሸሸግ ዘንድ በምድረ በዳ ወዳለ ምንጭ እንዲሄድ ነገረው። በየጠዋቱና በየምሽቱ ወፎች እንጀራና ሥጋ ያመጡለት ነበር። አክዓብና ጦር ሠራዊቱ ኤልያስን ፈለጉት፣ ነገር ግን ሊያገኙት አልቻሉም። ድርቁ በጣም ከባድ ስለነበር በመጨረሻ ምንጩ ደረቀ።

Image

ስለዚህ ኤልያስ ወደ አንድ ጐረቤት አገር ሄደ። በዚያችም አገር በድርቁ ምክንያት ረሃብ ስለነበር አንዲት መበለትና ወንድ ልጅዋ ምግብ ሊያልቅባቸው ተቃርበው ነበር። ነገር ግን ኤልያስን ተንከባከቡት፣ ስለሆነም እግዚአብሔር ዱቄቱ ከማድጋ ዘይቱም ከማሰሮ እንዳይጐድል አድርጎ መገባቸው። በረሀቡ ጊዜ ሁሉ ምግብ ነበራቸው። ኤልያስ በዚያ ለረዥም ጊዜ ተቀመጠ።

Image

ከሦስት ዓመት ተኩል በኋላ ኤልያስ ወደ እስራኤል መንግሥት ተመልሶ ዝናብ እንደሚዘንብ ለአክዓብ እንዲነግረው እግዚአብሔር ለኤልያስ ነገረው። አክዓብ ኤልያስን ባየው ጊዜ፣ ‹‹አንተ ችግር ፈጣሪ፣ አለህ እንዴ!›› አለው። ኤልያስ እንዲህ ብሎ መለሰት፣ ‹‹ችግር ፈጣሪ አንተ ነህ እንጂ እኔ አይደለሁም! እውነተኛውን አምላክ፣ ያህዌን ትተህ፣ በኣልን አምልከሃል፤ የእስራኤልን መንግሥት ሕዝብ ሁሉ በቀርሜሎስ ተራራ ላይ ሰብስብ።››

Image

450ዎቹ የበኣል ነቢያትን ጨምሮ የእስራኤል መንግሥት ሕዝብ ሁሉ ወደ ቀርሜሎስ ተራራ መጡ፡፡ ኤልያስም ለሕዝቡ፣ ‹‹ስንት ጊዜ ዐሳባችሁን ትለውጣላችሁ? እግዚአብሔር አምላክ ከሆን እርሱን አገልግሉ! በኣል አምላክ ከሆን እርሱን አገልግሉ!›› አላቸው፡፡

Image

ከዚያም ኤልያስ ለበኣል ነቢያት፣ ‹‹አንድ ወይፈን እረዱና መሥዋዕት አድርጋችሁ አቅርቡት፣ ነገር ግን እሳት አታንድዱ፡፡ እኔም እንደዚሁ አደርጋለሁ፡፡ በእሳት የሚመልስ አምላክ እርሱ እውነተኛ አምላክ ነው›› አላቸው፡፡ ስለዚህ የበኣል ካህናት መሥዋዕት አዘጋጁ፤ ነገር ግን እሳት አላነደዱም፡፡

Image

ከዚያ በኋላ የበኣል ነቢያት ‹‹በኣል ሆይ፣ ስማን!›› ብለው ወደ በኣል ጸለዩ። ቀኑን ሙሉ ጸለዩ፣ ጮኹ፣ እንዲሁም ሰውነታቸውን በቢላዋ ቈረጡ፣ ነገር ግን መልስ አልነበረም።

Image

በቀኑ መጨረሻ፣ ኤልያስ ለእግዚአብሔር መሥዋዕት አዘጋጀ፡፡ ከዚያም ሥጋው፣ እንጨቱ፣ እንዲሁም በመሠዊያው ዙሪያ ያለው መሬት እንኳ ሳይቀር ፍጹም እስኪረጥብ ድረስ ዐሥራ ሁለት ጋን ሙሉ ውሃ በመሥዋዕቱ ላይ እንዲያፈሱ ለሕዝብ ነገራቸው፡፡

Image

ከዚያም ኤልያስ እንዲህ ብሎ ጸለየ፣ ‹‹ያህዌ፣ የአብርሃም፣ የይስሐቅና የያዕቆብ አምላክ፣ አንተ የእስራኤል አምላክ እንደ ሆንክና እኔም አገልጋይህ እንደ ሆንኩ ዛሬ ዐሳየን። አንተ እውነተኛ አምላክ እንደ ሆንክ ይህ ሕዝብ ያውቅ ዘንድ መልስልኝ›› አለ።

Image

ወዲያውኑ፣ እሳት ከሰማይ ወደቀና ሥጋውን፣ እንጨቱን፣ ድንጋዩን፣ ቈሻሻውን፣ እንዲሁም በመሠዊያው ዙሪያ የነበረውን ውሃ እንኳ ሳይቀር አቃጠለ፡፡ ሕዝቡ ይህን ባዩ ጊዜ መሬት ላይ ወደቁና ‹‹ያህዌ አምላክ ነው! ያህዌ አምላክ ነው!›› አሉ፡፡

Image

ከዚያም ኤልያስ፣ ‹‹ከበኣል ነቢያት አንድም እንዳያመልጥ!›› አለ። ስለዚህ ሕዝቡ የበኣልን ነቢያት ያዙና ወስደው ገደሉአቸው።

Image

ከዚያ በኋላ ኤልያስ ለንጉሥ አክዓብ፣ ‹‹ዝናብ መጥቶአልና ፈጥነህ ወደ ከተማ ተመለስ›› አለው፡፡ ወዲያውኑ ሰማዩ ጠቈረ፣ ከባድ ዝናብም መዝነብ ጀመረ፡፡ ያህዌ ድርቁን አቆመው፤ እውተኛ አምላክ መሆኑንም አረጋገጠ፡፡

Image

ከኤልያስ ዘመን በኋላ፣ እግዚአብሔር ነቢይ እንዲሆን ኤልሳዕ የተባለ ሰውን መረጠ። እግዚአብሔር በኤልሳዕ በኩል ብዙ ተአምራትን አደረገ። ከተአምራቱ አንዱ አስከፊ የቆዳ በሽታ በያዘው የጠላት ጦር ሠራዊት አዛዥ በነበረው ንዕማን ላይ ተከሠተ። ስለ ኤልሳዕ ሰምቶ ነበርና ስለዚህ እንዲፈውሰው ኤልሳዕን ሄዶ ጠየቀው። ኤልሳዕ በዮርዳኖስ ወንዝ ሰባት ጊዜ ብቅ ጥልቅ እንዲል ለንዕማን ነገረው።

Image

በመጀመሪያ ንዕማን ተቈጣና ሞኝነት ስለ መሰለው ኤልሳዕ የነገረውን ነገር አላደረገውም። በኋላ ግን ዐሳቡን ለወጠና በዮርዳኖስ ወንዝ ሰባት ጊዜ ብቅ ጥልቅ አለ። በመጨረሻ ከውሃው በወጣ ጊዜ ቆዳው ፍጹም ተፈወሰ! እግዚአብሔር ፈወሰው።

Image

እግዚአብሔር ሌሎች ብዙ ነቢያትን ላከ፡፡ ሁላቸውም ለሕዝቡ ጣዖታትን ማምለክ እንዲያቆሙና ለሌሎች ፍትሕንና ምሕረትን ማሳየት እንዲጀምሩ ነገሩአቸው፡፡ ነቢያቱ ሕዝቡ ክፉ መሥራትን ባያቆሙና ለእግዚአብሔር መታዘዝ ባይጀምሩ፣ እግዚአብሔር በበደለኝነት እንደሚፈርድባቸውና፣ እንደሚቀጣቸውም አስጠነቀቁአቸው፡፡

Image

አብዛኛውን ጊዜ ሕዝቡ ለእግዚአብሔር አልታዘዙም። ብዙውን ጊዜ ለነቢያት የነበራቸው አያያዝ መጥፎ ነበረ፣ አንዳንድ ጊዜ እንዳውም ይገድሉአቸው ነበር። በአንድ ወቅት፣ ነቢዩ ኤርምያስ ደረቅ በሆነ የውሃ ጕድጓድ ውስጥ ተጥሎ በዚያ እንዲሞት ተትቶ ነበር። በጕድጓዱ መጨረሻ በነበረው ጭቃ ውስጥ እየሰመጠ ነበር፣ ነገር ግን ንጉሡ ራራለትና ከመሞቱ በፊት ከጕድጓዱ ጐትተው እንዲያወጡት አገልጋዮቹን አዘዛቸው።

Image

ነቢያቱ ሕዝቡ ቢጡሉአቸውም እንኳ ስለ እግዚአብሔር መናራቸውን ቀጠሉ፡፡ ንስሐ ባይገቡ እግዚአብሔር እንደሚያጠፋቸው ሕዝቡን አስጠነቀቁአቸው፡፡ ደግሞም የእግዚአብሔር መሲሕ እንደሚመጣ ስለተሰጠው ተስፋ ሕዝቡን አስታወቋቸው፡፡

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከ1ኛ ነገሥት 16-18፤ 2ኛ ነገሥት 5፤ ኤርምያስ 38፡፡

20. ምርኮና ከምርኮ መመለስ

Image

የእስራኤል መንግሥትና የይሁዳ መንግሥት ሁለቱም በእግዚአብሔር ላይ ኃጢአት ሠሩ፡፡ እግዚአብሔር ከእነርሱ ጋር በሲና ተራራ ያደረገውን ቃል ኪዳን አፈረሱ፡፡ እግዚአብሔርም ንስሐ እንዲገቡና እንደገና እንዲያመልኩት ሊያስጠነቅቃቸው ነቢያቱን ላከ፣ እነርሱ ግን አንታዘዝም አሉ፡፡

Image

ስለዚህ እግዚአብሔር ጠላቶቻቸው እንዲያጠፉአቸው በመፍቀድ ሁለቱንም መንግሥታት ቀጣቸው። ኃያልና ጨካኝ የሆነው የአሦር ንጉሠ ነገሥት ግዛት የእስራኤልን መንግሥት ደመሰሰው፣ ብዙ የእስራኤል መንግስት ሕዝብንም አዘርያውያን ገደሉ። ንብረቶቻቸውንም ሁሉ ወሰዱ፣ ከአገሪቱ አብዛኛውንም አቃጠሉ።

Image

አሦርያውያንም መሪዎችን፣ ሀብታሞችን፣ እንዲሁም ሙያ የነበራቸውን ሰዎች ሁሉ ሰበሰቡና ወደ አሦር ወሰዱአቸው፡፡ ያልተገደሉት በጣም ድሆች የነበሩት እስራኤላውያን ብቻ በእስራኤል መንግሥት ቀሩ፡፡

Image

ከዚያም አሦራውያን የእስራኤል መንግሥት በነበረባት ምድር እንዲኖሩ ባዕዳንን አመጡ፡፡ ባዕዳኑም የፈረሱትን ከተሞች እንደገና ሠሩና በዚያ ቀርተው የነበሩትን እስራኤላውያን አገቡ፡፡ ባዕዳንን ያገቡት የእስራኤላውያን ዝርያዎች ሳምራውያን ተብለው ይጠሩ ነበር፡፡

Image

የእስራኤል መንግሥት ሕዝብ እግዚአብሔርን ስላላመኑበትና ስላልታዘዙት እንዴት እንደ ቀጣቸው በይሁዳ መንግሥት የነበሩት ሕዝብ ዐዩ። እንደዚያም ሆኖ ግን የይሁዳ መንግሥት ሕዝብ የከነዓናውያንን አማልክት ጨምሮ ጣዖታትን አመለኩ። እግዚአብሔርም እንዲያስጠነቅቁአቸው ነቢያትን ላከ፣ እነርሱ ግን አንሰማም አሉ።

Image

አሦራውያን የእስራኤልን መንግሥት ካጠፉ ከ100 ዓመታት ገደማ በኋላ የይሁዳን መንግሥት እንዲወጉ እግዚአብሔር የባቢሎናውያንን ንጉሥ ናቡከደናፆርን ላከ፡፡ ባቢሎን ኃያል የንጉሠ ነገሥት ግዛት ነበረች፡፡ የይሁዳ ንጉሥም የናቡከደነፆር አገልጋይ ለመሆንና በያመቱ ብዙ ገንዘብ ሊከፍለው ተስማሙ፡፡

Image

ነገር ግን ከጥቂት ዓመታት በኋላ የይሁዳ ንጉሥ በባቢሎን ላይ ዓመፀ፡፡ ስለዚህ ባቢሎናውያን ተመልሰው መጥተው የይሁዳን መንግሥት ወጉ፡፡ የኢየሩሳሌምን ከተማ ያዙ፣ ቤተ መቅደሱን አጠፉ፣ እንዲሁም የከተማይቱንና የቤተ መቅደሱን ንብረት ሁሉ ወሰዱ፡፡

Image

የይሁዳ ንጉሥ ስላመፀበት ሊቀጡ የናቡከደነፆር ወታደሮች የይሁዳን ንጉሥ ወንድ ልጆች በፊቱ ገደሉ፤ እርሱንም ዓይኖቹን አሳወሩ፡፡ ከዚያ በኋላ በባቢሎን በእስር ቤት እንዲሞት ንጉሡን ወሰዱት፡፡

Image

ናቡከደነፆርና ሠራዊቱ በእርሻ እንዲሠሩ እጅግ በጣም ድሆች የሆኑትን ሰዎች ብቻ በመተው ከሞላ ጐደል የይሁዳን መንግሥት ሕዝብ ሁሉ ወደ ባቢሎን ማርከው ወሰዱ፡፡ የእግዚአብሔር ሕዝብ የተስፋዪቱን ምድር እንዲለቁ የተገደዱበት ይህ ወቅት የባቢሎን ምርኮ ተብሎ ይጠራል፡፡

Image

ምንም እንኳ እግዚአብሔር ወደ ምርኮ በመውሰድ ሕዝቡን ስለ ኃጢአታቸው ቢቀጣቸውም እነርሱንና ተስፋዎቹን አልረሳም። እግዚአብሔር ሕዝቡን መጠበቁንና በነቢያቱ በኩል እነርሱን ማነጋገሩን ቀጠለ። ከሰባ ዓመት በኋላ፣ ወደ ተስፋዪቱ ምድር እንደ ገና እንዲመለሱ ተስፋ ሰጠ።

Image

ከሰባ ዓመታት ገደማ በኋላ፣ የፋርስ ንጉሥ ቂሮስ ባቢሎንን አሸነፈ፣ ስለዚህ የፋርስ ንጉሠ ነገሥት ግዛት የባቢሎንን ንጉሠ ነገሥት ግዛት ተካ፡፡ በዚያን ጊዜ እስራኤላውያን አይሁዶች ተብለው ይጠሩ ነበር። አብዛኞቻቸውም ሕይወታቸውን በሙሉ በባቢሎን የኖሩ ነበሩ፡፡ በጣም ያረጁ ጥቂት አይሁዶች ብቻ የይሁዳን ምድር አስታወሱ፡፡

Image

የፋርስ ንጉሠ ነገሥት ኃይለኛ ቢሆንም ለማረካቸው ሕዝብ መሐሪ ነበር፡፡ ቂሮስ የፋርሳውያን ንጉሥ ከሆነ ከጥቂት ጊዜ በኋላ፣ ወደ ይሁዳ መመለስ የፈለገ ማንኛውም አይሁዳዊ ፋርስን ለቆ ወደ ይሁዳ መመለስ እንደሚችል ትእዛዝ ሰጠ፡፡ ቤተ መቅደሱን እንደገና እንዲሠሩም የገንዘብ ድጋፍ ሳይቀር አደረገላቸው! ስለዚህ በምርኮ ከቆዩባቸው ሰባ ዓመታት በኋላ፣ ጥቂት የአይሁዶች ቡድን በይሁዳ ወዳለችው ኢየሩሳሌም ከተማ ተመለሱ፡፡

Image

ሕዝቡ ወደ ኢየሩሳሌም በደረሱ ጊዜ፣ ቤተ መቅደሱንና በከተማዪቱ ዙሪያ ያለውን ቅጥር እንደገና ሠሩ። ምንም እንኳ እስካሁን ድረስ በሌሎች ሕዝቦች የተገዙ ቢሆኑም፣ ዳግመኛ በተስፋዪቱ ምድር ኖሩና በቤተ መቅደሱ እግዚአብሔርን አመለኩ።

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከ2ኛ ነገሥት 17፤ 24-25፤ 2ኛ ዜና 36፤ ዕዝራ 1-10፤ ነህምያ 1-13፡፡

21. እግዚአብሔር ስለ መሲሑ ተስፋ ሰጠ

Image

ገና ከመጀመሪያው፣ እግዚአብሔር መሲሑን ለመላክ ዐቀደ፡፡ የመጀመሪያው የመሲሑ ተስፋ ወደ አዳምና ሔዋን መጣ፡፡ እግዚአብሔር የእባቡን ራስ የሚቀጠቅጥ የሔዋን ዘር እንደሚወለድ ተስፋ ሰጠ፡፡ ሔዋንን ያታለለው እባብ ሰይጣን ነበር፡፡ ተስፋው መሲሑ ሰይጣንን ፍጹም ያሸንፈዋል የሚል ነው፡፡

Image

በእርሱ በኩል የዓለም ሕዝብ ወገኖች ሁሉ በረከት እንደሚቀበሉ እግዚአብሔር ለአብርሃም ተስፋ ሰጠው፡፡ ይህ በረከት ወደ ፊት መሲሑ ሲመጣ ይፈጸማል፡፡ እርሱ በዓለም ካሉ ከሁሉም የሕዝብ ወገኖች የሆኑ ሕዝቦች እንዲድኑ ያደርጋል፡፡

Image

ወደ ፊት እንደ ሙሴ ያለ ሌላ ነቢይ እንደሚያስነሣ እግዚአብሔር ለሙሴ ተስፋ ሰጠው፡፡ ይህ ቆይቶ ስለሚመጣው መሲሕ የተሰጠ ሌላ ተስፋ ነበር፡፡

Image

ከዝርያዎቹ አንዱ በእግዚአብሔር ሕዝብ ላይ ንጉሥ ሆኖ ለዘላለም እንደሚገዛ እግዚአብሔር ለንጉሥ ዳዊት ተስፋ ሰጠው፡፡ ይህም መሲሑ ከዳዊት ዝርያዎች አንዱ ይሆናል ማለት ነበር፡፡

Image

እግዚአብሔር ዐዲስ ቃል ኪዳን እንደሚያደርግ በነቢዩ ኤርምያስ በኩል ተስፋ ሰጠ፣ ይህ ቃል ኪዳን እግዚአብሔር በሲና ከእስራኤል ጋር እንዳደረገው ቃል ኪዳን ግን አይደለም፡፡ በዐዲሱ ቃል ኪዳን እግዚአብሔር ሕጉን በሕዝቡ ልብ ይጽፋል፣ ሕዝቡ እግዚአብሔርን በግል ያውቁታል፣ ሕዝቡም ይሆናሉ፣ እግዚአብሔርም ኃጢአታቸውን ይቅር ይላል፡፡ መሲሑ ዐዲሱን ኪዳን ይጀምራል፡፡

Image

ደግሞም የእግዚአብሔር ነቢያት መሲሑ ነቢይም፣ ካህንም እንዲሁም ንጉሥም ይሆናል አሉ፡፡ ነቢይ የእግዚአብሔርን ቃል የሚሰማ ከዚያም የእግዚአብሔርን ቃል ለሕዝቡ የሚያውጅ ሰው ነው፡፡ እግዚአብሔር ለመላክ ተስፋ የሰጠው መሲሕ እንከን የሌለው ነቢይ ይሆናል፡፡

Image

የእስራኤላውያን ካህናት ስለ ሕዝብ ኃጢአት ለሚደርስባቸው ቅጣት ምትክ እንዲሆን በሕዝብ ፈንታ ለእግዚአብሔር መሥዋዕቶችን ያቀርቡ ነበር፡፡ ደግሞም ካህናት ስለ ሕዝቡ ወደ እግዚአብሔር ይጸለዩ ነበር፡፡ መሲሑ ደግሞ ፍጹም መሥዋዕት አድርጎ ራሱን ለእግዚአብሔር የሚያቀርብ ፍጹም ሊቀ ካህናት ይሆናል፡፡

Image

ንጉሥ ማለት በመንግሥቱ ላይ የሚገዛና በሕዝቡ ላይ የሚፈርድ ሰው ነው። እንዲሁም መሲሑ በቅድመ አያቱ በዳዊት ዙፋን ላይ የሚቀመጥ ፍጹም ንጉሥ ይሆናል። በመላው ዓለም ላይ ለዘላለም ይገዛል፣ እንዲሁም ሁልጊዜ በቅንነት ይፈርዳል፤ ትክክለኛ ውሳኔም ይሰጣል።

Image

የእግዚአብሔር ነቢያት ስለ መሲሑ ሌሎች ብዙ ነገሮችን ተንብየዋል፡፡ ነቢዩ ሚልክያስ መሲሑ ከመምጣቱ በፊት ታላቅ ነቢይ እንደሚመጣ አስቀድሞ ተነበየ፡፡ መሲሑ ከአንዲት ድንግል እንደሚወለድ ነቢዩ ኢሳይያስ ተነበየ፡፡ ነቢዩ ሚክያስ መሲሑ በቤተልሔም ከተማ ይወለዳል አለ፡፡

Image

ነቢዩ ኢሳይያስ መሲሑ በገሊላ ይኖራል፣ ልባቸው የተሰበረ ሰዎችን ያጽናናል፣ እንዲሁም ለተማረኩት ነጻነትንና ለታሰሩት መፈታትን ያውጃል ብሎአል፡፡ ደግሞም ነቢዩ መሲሑ የታመሙና መስማት፣ ማየት፣ መናገር፣ ወይም መራመድ የማይችሉትን ሕዝብ እንደሚፈውስ ተነበየ፡፡

Image

ደግሞም ነቢዩ ኢሳይያስ ሰዎች ያለ ምክንያት መሲሑን እንደሚጠሉትና እንደማይቀበሉት ተነበየ። ሌሎች ነቢያት መሲሑን የገደሉት እነዚያ በልብሶቹ ላይ ዕጣ እንድሚጣጣሉና ወዳጁ አሳልፎ እንደሚሰጠው አስቀድመው ተነበዩ። ነቢዩ ዘካርያስ መሲሑን አሳልፎ የሚሰጠው ወዳጅ ሠላሳ ብር እንደሚከፈለው ተነበየ።

Image

ደግሞም ነቢያት ስለ መሲሑ አሟሟት ተናገሩ፡፡ ኢሳይያስ ሰዎች በመሲሑ እንደሚተፉበት፣ እንደሚያፌዙበትና እንደሚመቱት ተነበየ፡፡ ምንም ክፉ ነገር ያላደረገ ቢሆንም እንኳ ይወጉታል፤ በታላቅ መከራና ሥቃይ ይሞታል፡፡

Image

ደግሞም ነቢያት መሲሑ ምንም ኃጢአት የሌለበት ፍጹም ይሆናል ብለዋል፡፡ የሌሎች ሰዎችን የኃጢአት ቅጣት ለመቀበል እርሱ ይሞታል፡፡ የእርሱ መቀጣት በእግዚአብሔርና በሰዎች መካከል ሰላምን ያመጣል፡፡ በዚህ ምክንያት መሲሑን ማድቀቅ የእግዚአብሔር ፈቃድ ነበር፡፡

Image

መሲሑ እንደሚሞትና እግዚአብሔር ደግሞ ከሙታን እንደሚያስነሣው ነቢያት አስቀድመው ተነበዩ፡፡ እግዚአብሔር በመሲሑ ሞትና ትንሣኤ በኩል ኃጢአተኞችን ለማዳንና ዐዲሱን ኪዳን ለመጀመር የያዘውን ዕቅዱን ይፈጽማል፡፡

Image

እግዚአብሔር ለነቢያት ስለ መሲሑ ብዙ ነገሮችን ገለጠላቸው፣ ነገር ግን መሲሑ ከእነዚያ ነቢያት በአንዳቸውም ዘመን አልመጣም። ከእነዚህ ትንቢቶች የመጨረሻው ከተተነበየ ከ400 ዓመታት በኋላ፣ ልክ በትክክለኛው ጊዜ፣ እግዚአብሔር መሲሑን ወደ ዓለም ላከ።

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከዘፍጥረት 3፡15፤ 12፡1-3፤ ዘዳግም 18፡15፤ 2ኛ ሳሙኤል 7፤ ኤርምያስ 31፤ ኢሳይያስ 59፡16፤ ዳንኤል 7፤ ሚልክያስ 4፡5፤ ኢሳይያስ 7፡14፤ ሚክያስ 5፡2፤ ኢሳይያስ 9፡1-7፤ 35፡3-5፤ 61፡53፤ መዝሙር 22፡18፤ 35፡19፤ 69፡4፤ 41፡9፤ ዘካርያስ 11፡12-13፤ ኢሳይያስ 50፡6፤ መዝሙር 16፡10-11፡፡

22. የዮሐንስ መወለድ

Image

አስቀድሞ እግዚአብሔር በመላእክቱና በነቢያቱ በኩል ለሕዝቡ ተናግሮ ነበር፡፡ ነገር ግን ከዚያ በኃላ ለእነርሱ ሳይነገራቸው 400 ዓመታት አለፉ፡፡ አንድ ቀን በድንገት አንድ መልአክ ዘካርያስ ተብሎ ወደሚጠራ ሽማግሌ ካህን ከእግዚአብሔር ዘንድ መልእክት ይዞ መጣ፡፡ ዘካርያስና ሚስቱ ኤልሳቤጥ እግዚአብሔርን የሚፈሩ ሰዎች ነበሩ፣ ነገር ግን እርስዋ ልጆችን አልወለደችም ነበር፡፡

Image

መልአኩ ዘካርያስን አለው፣ ‹‹ሚስትህ ወንድ ልጅ ትወልዳለች።ስሙንም ዮሐንስ ብለህ ተጠራዋለህ፤ እርሱ በመንፈስ ቅዱስ ይሞላል፣ ሕዝቡንም ለመሲሑ ያዘጋጃል!›› ዘካርያስ፣ ‹‹ሚስቴና እኔ ልጆችን ለመውለድ በጣም አርጅተናል! ይህ እንደሚሆን እንዴት ዐውቃለሁ?›› ብሎ መለሰ።

Image

መልአኩ ለዘካርያስ እንዲህ ብሎ መለሰለት፣ “ይህን የምሥራች እንዳመጣላችሁ እግዚአብሔር ላከኝ፡፡ አንተ ስላላመንከኝ፣ ልጁ እስኪወለድ ድረስ መናገር አትችልም፡፡” ወዲያውኑ ዘካርያስ መናገር አልቻለም፡፡ ከዚያ በኋላ መልአኩ ከዘካርያስ ተለየ፡፡ ዘካርያስም ወደ ቤት ተመለሰ፤ ሚስቱም ፀነሰች፡፡

Image

ኤልሳቤጥ የስድስት ወር ነፍሰ ጡር በነበረች ጊዜ፣ ያው መልአክ በድንገት ስምዋ ማርያም ለተባለ ለኤልሳቤጥ ዘመድ ተገለጠ። እርስዋ ድንግል ነበረችና ልታገባ ዮሴፍ ለተባለ ሰው ታጭታ ነበር። መልአኩ፣ ‹‹ትፀንሻለሽ፤ ወንድ ልጅም ትወልጃለሽ። ስሙንም ኢየሱስ ትዪዋለሽ። እርሱም የልዑል እግዚአብሔር ልጅ ይባላል፤ ለዘላለምም ገዥ ይሆናል›› አለ።

Image

ማርያም‹‹እኔ ድንግል ስለ ሆንኩ፣ ይህ እንዴት ይሆናል?›› ብላ መለሰች። መልአኩ እንዲህ ብሎ አብራራ፣ ‹‹መንፈስ ቅዱስ ወደ አንቺ ይመጣል፣ የልዑል እግዚዘብሔር ኃይል ይጸልልሻል። ስለዚህ ልጁ ቅዱስ የእግዚአብሔር ልጅ ይሆናል።›› ማርያምም አመነች፤ መልአኩ ያለውንም ተቀበለች።

Image

መልአኩ ለማርያም ከተናገረ በኋላ ወዲያወኑ ሄደችና ኤልሳቤጥን ጐበኘቻት። ኤልሳቤጥ የማርያምን ሰላምታ እንደ ሰማች፣ የኤልሳቤጥ ልጅ በሆዷ ውስጥ ዘለለ። ሴቶቹ እግዚአብሔር ስላደረገላቸው ነገር አብረው ሐሤት አደረጉ። ማርያም ኤልሳቤጥን ለሦስት ወራት ከጐበኘቻት በኋላ፣ ወደ ቤትዋ ተመለሰች።

Image

ኤልሳቤጥ ወንድ ልጅዋን ከወለደች በኋላ፣ ዘካርያስና ኤልሳቤጥ መልአኩ እንዳዘዘው ሕፃኑን ዮሐንስ ብለው ሰየሙት፡፡ በዚያን ጊዜ እግዚአብሔር ዘካርያስ እንደ ገና እንዲናገር ፈቀደለት፡፡ ዘካርያስ እንዲህ አለ፣ ‹‹ሕዝቡን ዐስቦአልና እግዚአብሔር ይመስገን! አንተም ልጄ፣ ለኃጢአታቸው ይቅርታ መቀበል እንዴት እንደሚችሉ ለሕዝቡ የምትናገር የልዑል እግዚአብሔር ነቢይ ትባላለህ!››

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከሉቃስ 1፡፡

23. የኢየሱስ ልደት

Image

ማርያም ዮሴፍ ለተባለ ጻድቅ ሰው ታጭታ ነበር። እጮኛዋ ዮሴፍ ማርያም መፀነስዋን በሰማ ጊዜ፣ ሕፃኑ የእርሱ እንዳልሆነ ዐወቀ። ስለዚህ ማርያምን ለማሳፈር ስላልፈለገ፣ዝም ብሎ ሊተዋት ዐሰበ። ያንን ከማድረጉ በፊት የእግዚአብሔር መልአክ መጣና በሕልም ተናገረው።

Image

መልአኩ እንዲህ አለ፡- “ዮሴፍ፣ እጮኛህን ማርያምን ሚስትህ አድርገህ ለመውሰድ አትፍራ። በውስጥዋ ያለው ሕፃን ከመንፈስ ቅዱስ ነው። ወንድ ልጅ ትወልዳለች። ስሙን ኢየሱስ ብለህ ጥራው (ትርጕሙም፣ ያሕዌ ያድናል ማለት ነው)፣ ምክንያቱም ሕዝቡን ከኃጢአታቸው ያድናቸዋልና።”

Image

ስለዚህ ዮሴፍ ማርያምን ወሰዳት፣ ነገር ግን እስክትወልድ ድረስ ከእርስዋ ጋር አልተኛም፡፡

Image

ማርያም የምትወልድበት ጊዜ እንደ ደረሰ፣ የሮማ መንግሥት ሁሉም ሰው ለቈጠራ ቅድመ አያቶቹ ወደ ኖሩበት ከተማ እንዲሄድ ተናገረ። ዮሴፍና ማርያም ከሚኖሩበት ከናዝሬት ወደ ቤትልሔም ረጅም ጕዞ ተጓዙ፤ ምክንያቱም የቅድመ አያቶቻቸው የዳዊት ከተማ ቤትልሔም ነበር።

Image

ወደ ቤትልሔም በደረሱ ጊዜ ማረፊያ ስፍራ አልነበራቸውም። ሊያገኙ የቻሉት ብቸኛ ክፍል እንስሶች የሚያድሩበት ስፍራ ነበረ። ሕፃኑ በተወለደ ጊዜ የሚያስተኙበት አልጋ ስላልነበረ እናቱ በከብቶች መመገቢያ ገንዳ አስተኛችው። ስሙንም ኢየሱስ አሉት።

Image

በዚያ ሌሊት በአቅራቢያው ባለ ሜዳ ላይ መንጎቻቸውን የሚጠብቁ ጥቂት እረኞች ነበሩ። በድንገት የሚያበራ መልአክ ታያቸው፣ እነርሱም ፈሩ። መልአኩ፣ ‹‹አትፍሩ፣ ምክንያቱም ለእናንተ የምነግራችሁ የምሥራች አለኝ። መሲሑ ጌታ በቤተልሔም ተወልዶአል!››።

Image

“ሄዳችሁ ሕፃኑን ፈልጉ፣ በጨርቅ ተጠቅልሎና በእንስሶች መመገቢያ ገንዳ ተኝቶ ታገኙታላችሁ።” አለ። ድንገትም ሰማያት ‹‹ክብር ለእግዚአብሔር በሰማይ ይሁን! ሰላምም እግዚአብሔር ለሚወደው ሕዝብ በምድር ላይ ይሁን!›› እያሉ እግዚአብሔርን በሚያመሰግኑ መላእክት ተሞሉ።

Image

እረኞች ኢየሱስ ወደ ነበረበት ስፍራ ፈጥነው ደረሱና ልክ መልአኩ እንደ ነገራቸው በእንስሶች መመገቢያ ገንዳ ተኝቶ አገኙት፡፡ በጣም ደስ አላቸው፡፡ እረኞቹ ስለ ሰሙትና ስላዩት ሁሉ እግዚአብሔርን እያመሰገኑ፣ በጎቻቸው ወደ ነበሩባቸው ሜዳዎች ተመለሱ፡፡Image

ከጥቂት ጊዜ በኋላ ከሩቅ ምሥራቅ አገሮች የሆኑ ጠቢባን በሰማይ አንድ ያልተለመደ ኮከብ ዐዩ፡፡ ዐዲስ የአይሁድ ንጉሥ የተወለደ መሆኑን እንደሚያመለክትም ተገነዘቡ፡፡ ስለዚህ ይህንን ንጉሥ ለማየት በጣም ረጅም ርቀት ተጓዙ፡፡ ወደ ቤተ ልሔም መጡና ኢየሱስና ወላጆቹ የነበሩበትን ቤት አገኙት፡፡

Image

ጠቢባኑ ኢየሱስን ከእናቱ ጋር ባዩት ጊዜ ወድቀው ሰገዱለት፡፡ ለኢየሱስም ውድ ስጦታዎች ሰጡት፡፡ ከዚያም ወደ አገራቸው ተመለሱ፡፡

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከማቴዎስ 1፤ ሉቃስ 2፡፡

24. ዮሐንስ ኢየሱስን አጠመቀ

Image

የዘካርያስና የኤልሳቤጥ ልጅ ዮሐንስ አድጎ ነቢይ ሆነ፡፡ የሚኖረውም በምድረበዳ ነበር የሚበላውም፣ የበረሐ ማርና አንበጣ ነበር፣የሚለብሰውም ከግመል ፀጉር የተሠራ ልብስ ነበር፡፡

Image

ብዙ ሕዝብ ዮሐንስን ለመስማት ወደ ምድረ በዳ መጡ፡፡ እርሱም፣ ‹‹የእግዚአብሔር መንግሥት ቀርባለችና ንስሐ ግቡ›› እያለ ሰበከላቸው፡፡

Image

ሕዝቡ የዮሐንስን መልእክት በሰሙ ጊዜ፣ ብዙዎች ኃጢአታቸውን ተናዘዙ፣ ዮሐንስም አጠመቃቸው፡፡ ብዙ የሃይማኖት መሪዎችም ደግሞ በዮሐንስ ሊጠመቁ መጡ፣ ነገር ግን ንስሐ አልገቡም ወይም ኃጢአታቸውን አልተናዘዙም፡፡

Image

ዮሐንስ ለሃይማኖት መሪዎቹ እንዲህ አላቸው፣ ‹‹እናንተ መርዛማ እባቦች! ንስሐ ግቡና ባሕሪያችሁን ለውጡ። መልካም ፍሬ የማያፈራ ዛፍ ሁሉ ይቈረጥና ወደ እሳት ይጣላል።›› ነቢያት ‹‹እነሆ፣ መንገድህን የሚያዘጋጅ መልእክተኛዬን በፊትህ እልካለሁ።›› በማለት የተናገሩት ትንቢት በሐንስ ተፈጸመ።

Image

አንዳንድ አይሁዶች መሲሕ ስለ መሆኑ ዮሐንስን ጠየቁት፡፡ ዮሐንስ እንዲህ ብሎ መለሰ፣ ‹‹እኔ መሲሑ አይደለሁም፣ ነገር ግን ከእኔ በኋላ የሚመጣ አንድ ሰው አለ፡፡እርሱ እጅግ ታላቅ ስለሆነ እኔ የጫማውን ማሰሪያ እንኳ ልፈታ እንኳ አይገባኝም፡፡››

Image

በቀጣዩ ቀን፣ ኢየሱስ በዮሐንስ ለመጠመቅ መጣ፡፡ ዮሐንስ ባየው ጊዜ፣ ‹‹ተመልከቱ! እነሆ፣ የዓለምን ኃጢአት የሚያስወግድ የእግዚአብሔር በግ›› አለ፡፡

Image

ዮሐንስ ኢየሱስን፣ ‹‹እኔ አንተን ለማጥመቅ ተገቢ ሰው አይደለሁም። ይልቁን አንተ እኔን ማጥመቅ አለብህ›› አለው። ኢየሱስ ግን፣ ‹‹ ይህ መደረግ ያለበት ትክክለኛ ነገር ስለሆነ አንተ እኔን ማጥመቅ አለብህ›› አለው። ስለዚህ ኢየሱስ ከቶ ኃጢአት ባይሠራም እንኳ ዮሐንስ ኢየሱስን አጠመቀው።

Image

ኢየሱስ ከተጠመቀ በኋላ ከውኃው እንደ ወጣ፣ የእግዚአብሔር መንፈስ በርግብ አምሳል ታየና ወርዶ በእርሱ ላይ ዐረፈ፡፡ በዚሁ ጊዜ የእግዚአብሔር ድምፅ ከሰማይ፣ ‹‹አንተ እኔ የምወድህ ልጄ ነህ፣ በአንተም በጣም ደስ ብሎኛል›› ብሎ ተናገረ፡፡

Image

እግዚአብሔር ለዮሐንስ፣ ‹‹መንፈስ ቅዱስ ይወርድና አንተ በምታጠምቀው በአንድ ሰውዬ ላይ ያርፋል።ያ ሰያውዬ የእግዚአብሔር ልጅ ነው›› ብሎ ተናግሮት ነበር። አንድ አምላክ ብቻ አለ። ነገር ግን ዮሐንስ ኢየሱስን ባጠመቀው ጊዜ፣ እግዚአብሔር አብ ሲናገር ሰማ፣ እግዚአብሔር ወልድን ዐየ፣ እርሱም ኢየሱስ ነው፣ እንዲሁም መንፈስ ቅዱስን ዐየ።

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከማቴዎስ 3፤ ማርቆስ 1፡9-11፤ ሉቃስ 3፡1-23፡፡

25. ሰይጣን ኢየሱስን ፈተነው

Image

ኢየሱስ ከተጠመቀ በኋላ ወዲያውኑ፣ መንፈስ ቅዱስ ወደ ምድረ በዳ ወሰደው፣ እዚያም አርባ ቀንና አርባ ሌሊት ጾመ፡፡ ከዚያም ሰይጣን ወደ ኢየሱስ መጣና ኃጢአት እንዲሠራ ኢየሱስን ፈተነው፡፡

Image

‹‹የእግዚአብሔር ልጅስ ከሆንክ፣እነዚህን ድንጋዮች ወደ እንጀራ ለውጥ›› በማለት ሰይጣን ኢየሱስን ፈተነው፡፡

Image

ኢየሱስ፣ ‹‹‹ሰዎች ለመኖር እንጀራ ብቻ አያስፈልጋቸውም፣ ነገር ግን እግዚአብሔር የሚናገረው እያንዳንዱ ቃል ያስፈልጋቸዋል› ተብሎ በእግዚአብሔር ቃል ተጽፎአል!›› ብሎ መለሰለት፡፡

Image

ከዚያም ሰይጣን ኢየሱስን ወደ ቤተ መቅደስ ጫፍ ወሰደውና፣ ‹‹የእግዚአብሔር ልጅ ከሆንክ ራስህን ወደ ታች ወርውር፣ ምክንያቱም፣ ‹ድንጋይ እግርህን እንዳይመታህ ይሸከሙህ ዘንድ እግዚአብሔር መላእክቱን ያዛል ተብሎ ተጽፎል››› አለ፡፡

Image

ነገር ግን ኢየሱስ ከእግዚአብሔር ቃል በመጥቀስ ለሰይጣን መለሰለት፡፡ ‹‹በእግዚአብሔር ቃል፣ ‹ጌታ አምላክህን አትፈታተነው› ተብሎ ተጽፎአል›› አለው፡፡

Image

ከዚያም ሰይጣን የዓለምን መንግሥታትና ክብራቸውን ሁሉ ዐሳየውና፣ ‹‹ወድቀህ ብትሰግድልኝ ይህን ሁሉ እሰጥሃለሁ›› አለ፡፡

Image

ኢየሱስ፣ ‹‹ከኔ ራቅ፣ አንተ ሰይጣን! በእግዚአብሔር ቃል፣ ‹ለጌታህ ለአምላክህ ስገድ እርሱንም ብቻ አምልክ› ተብሎ ተጽፎአል›› አለው፡፡

Image

ኢየሱስ ለሰይጣን ፈተና አልተሸነፈም፣ ስለዚህ ሰይጣን ለጊዜው ትቶት ሄደ፡፡ ከዚያ በኋላ መላእክት መጥተው ኢየሱስን አገለገሉት፡፡

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከማቴዎስ 4፡1-11፤ ማርቆስ 1፡12-13፤ ሉቃስ 4፡1-13፡፡

26. ኢየሱስ አገልግሎቱን ጀመረ

Image

ኢየሱስ የሰይጣንን ፈተና ካሸፈነ በኋላ፣ ይኖርበት ወደ ነበረው ወደ ገሊላ አውራጃ በመንፈስ ቅዱስ ኃይል ተሞልቶ ተመለሰ። ከቦታ ወደ ቦታም እየሄደ አስተማረ። ሁሉም ሰው ስለ እርሱ መልካም ይናገር ነበር።

Image

ኢየሱስ በልጅነቱ ይኖረበት ወደ ነበረው ወደ ናዝሬት ከተማ ተመለሰ። በሰንበት ቀንም አይሁድ እግዚአብሔርን ወደሚያመልኩበት ስፈራ ሄደ። ያነብ ዘንድ የነቢዩን የኢሳይያስን ጥቅልል መጽሐፍ ሰጡት። ኢየሱስ ጥቅልል መጽሐፉን ከፍቶ በከፊል ለሕዝቡ አነበበላቸው።

Image

ኢየሱስ፣ ‹‹ለድሆች የምሥራችን፣ ለተማረኩት ነጻትን፣ ለዕውሮች ማየትን፣ ለታሰሩትም መፈታትን እሰብክ ዘንድ እግዚአብሔር መንፈሱን ሰጥቶኛል፡፡ ይህች የተወደደችው የጌታ ዓመት ነች›› ብሎ አነበበ፡፡

Image

ከዚያም ኢየሱስ ተቀመጠ፡፡ ሁላቸውም ቀርበው ተመለከቱት፡፡አሁን ያነበበው የእግዚአብሔር ቃል ስለ መሲሑ የሚናገር መሆኑን ያውቁ ነበር፡፡ ኢየሱስ፣ ‹‹ይህ ያነበብኩላችሁ ቃል ልክ አሁን እየተፈጸመ ነው ›› አለ፡፡ ሕዝቡ ሁሉ ተደነቁ፡፡ ‹‹ይህ የዮሴፍ ልጅ አይደለምን?›› አሉ፡፡

Image

ከዚያም ኢየሱስ፣ ‹‹ነቢይ በገዛ አገሩ እንደማይከበር የታወቀ ነው፣ በነቢዩ ኤልያስ ዘመን፣ በእስራኤል ብዙ መበለቶች ነበሩ፡፡ ነገር ግን ለሦስት ዓመት ተኩል ዝናብ ባልዘነበ ጊዜ መበለት የሆነችውን ሴት እንዲረዳ እግዚአብሔር ኤልያስ ከሌላ አገር ወደ ሆነችው መበለት ላከ እንጂ ከእስራኤል የሆነች መበለትን እንዲረዳ አልላከውም፡፡››

Image

ኢየሱስ መናገሩን በቀጠል፣ ‹‹በነቢዩ ኤልሳዕ ዘመንም በእስራኤል የቆዳ ሕመም የያዛቸው ብዙ ሰዎች ነበሩ፡፡ ነገር ግን ኤልሳዕ አንዳቸውንም አልፈወሰም፡፡ ነገር ግን የእስራኤል ጠላቶች አዛዥ የነበረውን የንዕማንን ቆዳ በሽታ ብቻ ፈወሰ፡፡›› ኢየሱስን ይሰሙ የነበሩት ሕዝብ አይሁዳውያን ነበሩ፡፡ ስለዚህ ይህን ሲናገር በሰሙት ጊዜ ተናደዱበት፡፡

Image

የናዝሬት ሕዝብ ኢየሱስን ከአምልኮው ቦታ ጐተቱትና ወርውረው ሊገድሉት ወደ ገደል አፋፍ ወሰዱት፡፡ ነገር ግን ኢየሱስ በሕዝቡ መካከል ተራመደና ወደ ናዝሬት ከተማ ሄደ፡፡

Image

ከዚያም ኢየሱስ በገሊላ አውራጃ ሁሉ ተዘዋወረ፣ ብዙ ሕዝብም ወደ እርሱ መጡ፡፡ ማየት፣ መራመድ፣ መስማት፣ ወይም መናገር የማይችሉትን ጨምሮ ብዙ የታመሙ ወይም የአካል ጕዳተኞች የሆኑ ሰዎችን ወደ እርሱ አመጡ ኢየሱስም ፈወሳቸው፡፡

Image

አጋንንት የነበሩባቸው ብዙ ሰዎችን ወደ ኢየሱስ አመጡ፡፡ በኢየሱስ ትእዛዝ አጋንንቱ ከሰዎቹ ወጡ፣ ብዙ ጊዜም፣ ‹‹አንተ የእግዚአብሔር ልጅ ነህ!›› ብለው ይጮኹ ነበር፡፡ ሕዝቡ ተደነቁና እግዚአብሔርን አመለኩ፡፡

Image

ከዚያም ኢየሱስ የእርሱ ሐዋርያት ተብለው የተጠሩትን ዐሥራ ሁለት ሰዎች መረጠ፡፡ ሐዋርያቱ ከኢየሱስ ጋር እየተጓዙ ከእርሱ ተማሩ፡፡

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከማቴዎስ 4፡12-25፤ ማርቆስ 1፡14-15፣ 35-39፤ 3፡13-21፤ ሉቃስ 4፡14-30፣ 38-44፡፡

27.የደጉ ሳምራዊ ታሪክ

Image

አንድ ቀን አንድ የአይሁድ ሕግ ዐዋቂ ሊፈትነው ወደ ኢየሱስ መጣ፣ ‹‹መምህር ሆይ፣ የዘላለምን ሕይወት እንድወርስ ምን ላድርግ?›› አለው፡፡ ኢየሱስ፣ ‹‹በእግዚአብሔር ሕግ የተጻፈው ምንድን ነው?›› ብሎ መለሰለት፡፡

Image

ሕግ ዐዋቂውም ‹‹የእግዚአብሔር ሕግ፣ ጌታ አምላክህን በፍጹም ልብህ በፍጹም ነፍስህም በፍጹም ኃይልህም በፍጹም ዐሳብህም ውደድ። ባልንጀራህንም እንደ ራስህ ውደድ›› ይላል ብሎ መለሰ። ኢየሱስ፣ ‹‹ትክክል ነህ! ይህን አድርግ በሕይወትም ትኖራለህ›› አለው።

Image

ነገር ግን ሕግ ዐዋቂው ጻድቅ መሆኑን ለማረጋገጥ ፈለገ፣ ስለዚህ፣ ‹‹ባልንጀራዬ ማን ነው?›› ብሎ ጠየቀ፡፡

Image

ኢየሱስ ምሳሌ በመናገር ለሕግ ዐዋቂው መለሰለት። ‹‹ከኢየሩሳሌም ወደ ኢያሪኮ ይጓዝ የነበረ አንድ አይሁዳዊ ነበረ።››

Image

‹‹ሰውዬው በመጓዝ ላይ እያለ ወንበዴዎች አጠቁት፡፡ ያለውን ነገር ሁሉ ወሰዱበትና እጅግ ደበደቡት፡፡ በሞት አፋፍም ጥለውት ሄዱ፡፡››

Image

ከዚያ በኋላ ብዙም ሳይቆይ አንድ አይሁዳዊ ካህን በዚያም መንገድ ይጓዝ ነበር፡፡ ይህ የሃይማኖት መሪ የተዘረፈውንና የተደበደበውን ሰው ባየ ጊዜ መንገዱን ቀይሮ ሳይረዳው ትቶት ሄደ።››

Image

ከዚያ በኋላ ብዙም ሳይቆይ፣ አንድ ሌዋዊ መጣ፡፡ (ሌዋውያን በቤተ መቅደስ ካህናቱን የሚረዱ የአይሁድ ነገድ ነበሩ፡፡) ሌዋዊውም ደግሞ እንዳይረዳው መንገዱን ቀይሮ የተዘረፈውንና የተደበደበውን ሰው ችላ ብሎ ትቶት ሄደ፡፡››

Image

በዚያ መንገድ የወረደው የሚቀጥለው ሰው ሳምራዊ ነበር፡፡ (ሳምራውያን የሌሎች አገሮች ሰዎችን ያገቡ የአይሁድ ዝርያዎች ነበሩ፡፡ ሳምራውያንና አይሁዳውያን አይዋደዱም ነበር፡፡) ነገር ግን ሳምራዊው አይሁዳዊውን ባየ ጊዜ በጣም አድርጎ ራራለት፡፡ ስለዚህ ተንከባከበውና ቊስሉን አሰረለት፡፡››

Image

‹‹ከዚያ በኋላ ሳምራዊው ሰውዬውን አንሥቶ በራሱ አህያ ላይ አስቀምጦት ወደ እንግዶች ማደሪያ ወሰደው ተንከባከበውም፡፡››

Image

‹‹በማግሥቱም ሳምራዊው ጕዞውን መቀጠል ግድ ሆነበት፡፡ ለእንግዶች ማረፊያ ኃላፊ ገንዘብ ሰጠውና፣ ‹‹እባክህ ተንከባከበው፣ ከዚህ ሌላ ገንዘብ የምታወጣ ከሆነ በምመለስበት ጊዜ እከፍልሃለሁ›› አለው፡፡

Image

ኢየሱስም ሕግ ዐዋቂውን፣ ‹‹ምን ታስባለህ? ለተዘረፈውና ለተደበደበው ሰው ባልንጀራው ከሦስቱ ሰዎች የትኛው ነበር?›› ብሎ ጠየቀው፡፡ እርሱም፣ ‹‹ምሕረት ያደረገለት ነበር›› ብሎ መለሰለት፡፡ ኢየሱስ፣ ‹‹አንተም ሄደህ እንደዚሁ አድርግ›› ብሎ ነገረው፡፡

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከሉቃስ 10፡25-37፡፡

28. ባለ ጠጋው ወጣት

Image

አንድ ቀን አንድ ባለጠጋ ወጣት ገዥ ወደ ኢየሱስ መጣና፣ ‹‹ቸር መምህር፣ የዘላለምን ሕይወት እንድወርስ ምን ላድርግ?›› ብሎ ጠየቀው፡፡ ኢየሱስ፣ ‹‹ስለ ምን ‹ቸር› ትለኛለህ? ቸር አንድ ብቻ አለ፣ እርሱም እግዚአብሔር ነው፡፡ ነገር ግን አንተ የዘላለም ሕይወት እንዲኖርህ ከፈለግህ ለእግዚአብሔር ሕግ ታዘዝ›› አለው፡፡

Image

‹‹የትኞቹን ልታዘዝ?›› ብሎ ጠየቀው፡፡ ኢየሱስ እንዲህ ብሎ መለሰለት፣ ‹‹አትግደል፡፡ አታመንዝር፡፡ አትስረቅ፡፡ አትዋሽ፡፡ አባትህንና እናትህን አክብር፣ ባልጀራህንም እንደ ራስህ ውደድ፡፡››

Image

ነገር ግን ወጣቱ፣ ‹‹ከልጅነቴ ጀምሮ እነዚህን ሕጎች ሁሉ ፈጽሜአለሁ፡፡ ለዘላለም ለመኖር ሌላስ ምን ማድረግ ያስፈልገኛል?›› አለ፡፡ ኢየሱስ ዐየውና ወደደው፡፡

Image

ኢየሱስ፣ ‹‹ፍጹም ለመሆን ብትፈልግ፣ ያለህን ንብረት ሁሉ ሽጥና ገንዘቡን ለድሆች ስጥ፣ በሰማይም የሀብት መዝገብ ታገኛለህ፡፡ ከዚያም በኋላ ናና ተከተለኝ›› ብሎ መለሰለት፡፡

Image

ወጣቱ፣ ኢየሱስ የተናገረውን በሰማ ጊዜ፣ በጣም ሀብታም ነበርና ያለውን ንብረት ሁሉ ለድኻ መስጠት ስላልፈለገ በጣም ዐዘነ፡፡ ከኢየሱስ ፊቱን አዞረና ሄደ፡፡

Image

በዚያን ጊዜ ኢየሱስ ደቀ መዛሙርቱን እንዲህ አላቸው፣ ‹‹ለሀብታሞች ወደ እግዚአብሔር መንግሥት መግባት እጅግ አስቸጋሪ ነው! አዎ፣ ሀብታም ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ከሚገባ ይልቅ ግመል በመርፌ ቀዳዳ ቢያልፍ ይቀላል፡፡››

Image

ደቀ መዛሙርቱ ኢየሱስ የተናገረውን በሰሙ ጊዜ ደነገጡና፣ ‹‹ታዲያ ማን ሊድን ይችላል?›› አሉ፡፡

Image

ኢየሱስ ደቀ መዛሙርቱን ተመለከተና፣ ‹‹ይህ በሰው ዘንድ አይቻልም፣ በእግዚአብሔር ዘንድ ግን ሁሉ ይቻላል›› አለ፡፡

Image

ጴጥሮስ ኢየሱስን፣ ‹‹እኛ ሁሉን ትተን ተከተልንህ፡፡ ዋጋችን ምን ይሆን?›› አለው፡፡

Image

ኢየሱስ እንዲህ ብሎ መለሰለት፣ ‹‹ስለ እኔ ቤቶችን፣ ወንድሞችን፣ እኅቶችን፣ አባትን፣ እናትን ወይም ንብረትን የተወ ሁሉ መቶ እጥፍ ይቀበላል፤ የዘላለምንም ሕይወት ይወርሳል፡፡ ነገር ግን ፊተኞች የሆኑ ብዙዎች ኋለኞች ይሆናሉ፣ ኋለኞችም የሆኑ ብዙዎች ፊተኞች ይሆናሉ፡፡››

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከማቴዎስ 19፡16-30፤ ማርቆስ 10፡17-31፤ ሉቃስ 18፡18-30፡፡

29. የምሕረት የለሹ ባሪያ ታሪክ

Image

አንድ ቀን ጴጥሮስ ኢየሱስን፣ ‹‹መምህር ሆይ፣ ወንድሜ ቢበድለኝ ስንት ጊዜ ይቅር ልበለው?እስከ ሰባት ጊዜ ነውን?›› ብሎ ጠየቀው፡፡ ኢየሱስ፣ ‹‹ሰባት ጊዜ አይደለም፣ ሰባ ጊዜ ሰባት እንጂ›› አለው፡፡ ኢየሱስ ይህን ሲል ሁልጊዜ ይቅር ማለት አለብን ማለቱ ነው፡፡ ከዚያም ኢየሱስ ይህን ምሳሌ ተናገረ፡፡

Image

ኢየሱስ እንዲህ አለ፣ ‹‹የእግዚአብሔር መንግሥት ከባርያዎቹ ጋር ሒሳብ ሊተሳሰብ የፈለገን አንድ ንጉሥ ትመስላለች፡፡ ከባሮቹ አንዱ የ200,000 ዓመታት ደመወዝ የሚያክል ከፍተኛ ዕዳ ነበረበት፡፡››

Image

ባሪያው ዕዳውን መክፈል ስላልቻለ፣ ንጉሡ፣ ‹‹ዕዳውን ይከፍል ዘንድ ይህን ሰውና ቤተ ሰቡን ለባርነት ሽጡአቸው›› አለው፡፡

Image

‹‹ባሪያው በንጉሡ ፊት ተንበረከከና፣ ‹እባክህን ታገሠኝ፣ ያለብኝን ዕዳ ሁሉ እከፍልሃለሁ› አለው፡፡ ንጉሡ ለባሪያው አዘነለት፣ ዕዳውንም ሁሉ ሰረዘለትና እንዲሄድ ለቀቀው፡፡››

Image

‹‹ነገር ግን ባሪያው ከንጉሡ ዘንድ በወጣ ጊዜ፣ የአራት ወር ደመወዝ የሚያክል ገንዘብ የእርሱ ዕዳ ያለበትን ከባልንጀሮቹ ባሪያዎች አንዱን አገኘ፡፡ ባሪያውም ባልንጀራውን ባሪያ ያዘውና፣ ‹ዕዳህን ክፈለኝ!››› አለው፡፡

Image

‹‹ባልንጀራው ባሪያ በፊቱ ተንበርክኮ፣ ‹እባክህን ታገሠኝ፣ ያለብኝን ዕዳ ሁሉ እከፍልሃለሁ› አለው፡፡ ነገር ግን ያ ባሪያ ባልንጀራ ባሪያውን ዕዳውን እስኪከፍለው ድረስ በወኅኒ ጣለው፡፡››

Image

‹‹ሌሎች ባሮችም የሆነውን ነገር ዐይተው እጅግ ተረበሹ፡፡ ወደ ንጉሡ ሄደውም የሆነውን ነገር ሁሉ ነገሩት፡፡››

Image

‹‹ንጉሡ ባሪያውን ጠራና፣ ‹አንተ ክፉ ባሪያ! ስለ ለመንኸኝ ዕዳህን ሁሉ ተውሁልህ፡፡ አንተም እንዲሁ ማድረግ ነበረብህ› አለው፡፡ ንጉሡ በጣም ተቈጣና ዕዳውን ሁሉ እስኪከፍል ድረስ ክፉውን ባሪያ በወኅኒ ጣለው፡፡››

Image

ከዚያም ኢየሱስ እንዲህ አለ፣ ‹‹ከእናንተ እያንዳንዱ ወንድሙን ከልቡ ይቅር ካላለ፣ የሰማይ አባቴ በእናንተም እንዲሁ ያደርግባችኋል፡፡››

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከማቴዎስ 18፡21-35፡፡

30. ኢየሱስ አምስት ሺህ ሰዎችን መገበ

Image

ኢየሱስ በተለያዩ ብዙ መንደሮች እንዲሰብኩና ሰዎችን እንዲያስተምሩ ሐዋርያቱን ላከ፡፡ እነርሱም ኢየሱስ ወደ ነበረበት በተመለሱ ጊዜ፣ ያደረጉትን ነገር ነገሩት፡፡ ከዚያ በኋላ ኢየሱስ ከሐይቁ ማዶ ጸጥታ ወዳለበት ቦታ አብረውት እንዲሄዱና ጥቂት እንዲያርፉ ጋበዛቸው፡፡ ስለዚህ ጀልባ ውስጥ ገቡና ወደ ሐይቁ ማዶ ሄዱ፡፡

Image

ነገር ግን በጀልባው ሲሄዱ ኢየሱስንና ደቀ መዛሙርቱን ያዩአቸው ብዙ ሰዎች ነበሩ፡፡ እነዚህ ሰዎች ሊቀድሙአቸው በሐይቁ ዳርቻ ሮጡ፡፡ ስለዚህ ኢየሱስና ደቀ መዛሙርቱ ወደ ማዶ በደረሱ ጊዜ፣ በጣም ብዙ ሰዎች አስቀድመው እዚያ ደርሰው ይጠባበቁአቸው ነበር፡፡

Image

ሕዝቡ ሴቶችና ልጆች ሳይቈጠሩ ከ5000 በላይ ወንዶች ነበሩ፡፡ ኢየሱስ ለሕዝቡ እጅግ አዘነላቸው፡፡ ለኢየሱስ እነዚህ ሕዝብ እረኛ እንደሌላቸው በጎች ነበሩ፡፡ ስለዚህ አስተማራቸውና በመካከላቸው የነበሩትን በሽተኞች ፈወሳቸው፡፡

Image

ቀኑ ሊመሽ ሲሆን ደቀ መዛሙርቱ እንዲህ ብለው ለኢየሱስ ነገሩት፣ ‹‹ጊዜው መሽቶአል፤ በአቅራቢያውም ከተሞች የሉም፡፡ ስለዚህ የሚበሉትን ነገር ይገዙ ዘንድ ሕዝቡን አሰናብታቸው፡፡››

Image

ኢየሱስ ግን ደቀ መዛሙርቱን፣ ‹‹የሚበሉትን እናንተ ስጡአቸው!›› አላቸው፡፡ እነርሱም፣ ‹‹ይህን ማድረግ እንዴት እንችላለን? ያለን አምስት እንጀራና ሁለት ትንንሽ ዓሣ ብቻ ነው›› ብለው መለሱለት፡፡

Image

ሃምሳ ሃምሳ ሆነው ሣሩ ላይ እንዲቀመጡ ለሕዝቡ ይነግሩ ዘንድ ኢየሱስ ለደቀ መዛሙርቱ ነገራቸው፡፡

Image

ከዚያም ኢየሱስ አምስቱን እንጀራና ሁለቱን ዓሣ ይዞ ወደ ሰማይ ተመለከተ፣ ስለ ምግቡም እግዚአብሔርን አመሰገነ፡፡

Image

ከዚያም ኢየሱስ እንጀራውንና ዓሣውን ቈረሰ፡፡ የቈረሰውን ለሕዝቡ እንዲያቀርቡም ለደቀ መዛሙርቱ ሰጣቸው፡፡ ደቀ መዛሙርቱ ምግቡን ማደላቸውን ቀጠሉ፣ በፍጹም አያልቅም ነበር! ሕዝቡ ሁሉ በልተው ጠገቡ፡፡

Image

ከዚያ በኋላ ደቀ መዛሙርቱ ቊርስራሹን ምግብ ሰበሰቡ፣ እርሱም ዐሥራ ሁለት መሶብ ሙሉ ነበር! ምግቡ ሁሉ የመጣው ከአምስቱ እንጀራና ከሁለቱ ዓሣ ነበር፡፡

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከማቴዎስ 14፡13-21፤ ማርቆስ 6፡31-44፤ ሉቃስ 9፡10-17፤ ዮሐንስ 6፡5-15፡፡

31. ኢየሱስ በውሃ ላይ ተራመደ

Image

ከዚያም ኢየሱስ ሕዝቡን እያሰናበተ እያለ ጀልባ ውስጥ ገብተው እየቀዘፉ ወደ ማዶ እንዲሻገሩ ለደቀ መዛሙርቱ ነገራቸው፡፡ ኢየሱስ ሕዝቡን ካሰናበተ በኋላ ለመጸለይ ወደ ተራራ ወጣ፡፡ በዚያ ኢየሱስ ብቻውን ነበር፣ እስከ እኩለ ሌሊትም ጸለየ፡፡

Image

በዚያን ጊዜ፣ ደቀ መዛሙርቱ ጀልባቸውን እየቀዘፉ ነበር፣ ይሁን እንጂ በእኩለ ሌሊት የደረሱት ወደ ሐይቁ አጋማሽ ብቻ ነበር፡፡ ነፋሱ በእነርሱ ላይ በኃይል ይነፍስ ስለ ነበር የሚቀዝፉት በጣም በችግር ነበር፡፡

Image

በዚያን ጊዜ ኢየሱስ መጸለዩን ጨረሰና ወደ ደቀ መዛሙርቱ ሄደ፡፡ በውሃው ላይ እየተራመደ ሐይቁን አቋርጦ ወደ ጀልባቸው መጣ!

Image

ደቀ መዛሙርቱ ኢየሱስን ባዩ ጊዜ በጣም ፈሩ፣ ምክንያቱም ምትሐት ያዩ መሰላቸው፣ ኢየሱስም እንደ ፈሩ ዐወቀ፣ ስለዚህ ወደ እነርሱ ተጣራና፣ ‹‹አትፍሩ፡፡ እኔ ነኝ!›› አላቸው፡፡

Image

በዚያን ጊዜ ጴጥሮስ ኢየሱስን፣ ‹‹መምህር ሆይ፣ አንተስ ከሆንክ በውሃው ላይ ወደ አንተ እንድመጣ እዘዝ›› አለው፡፡ ኢየሱስም ጴጥሮስን፣ ‹‹ና!›› አለው፡፡

Image

ስለዚህ ጴጥሮስ ከጀልባው ወጣና በውሃው ላይ ወደ ኢየሱስ መራመድ ጀመረ፡፡ ነገር ግን ትንሽ እንደ ተራመደ ዓይኖቹን ከኢየሱስ ዞር አደረገና ማዕበሉን ማየትና ብርቱውን ነፋስም መስማት ጀመር፡፡

Image

በዚያን ጊዜ ጴጥሮስ ፈራና በውሃው መስጠም ጀመረ፡፡ ‹‹መምህር ሆይ፣ አድነኝ!›› ብሎ ጮኸ፡፡ ኢየሱስ ወዲያው እጆቹን ዘረጋና ያዘው፡፡ ከዚያም ጴጥሮስን፣ ‹‹አንተ እምነት የጎደለህ፣ ለምን ተጠራጠርህ?›› አለው፡፡

Image

ጴጥሮስና ኢየሱስ ወደ ጀልባው በገቡ ጊዜ፣ ነፋሱ ወዲያውኑ ቆመና ውሃው ጸጥ አለ፡፡ ደቀ መዛሙርቱ ተደነቁ፡፡ ‹‹በእውነት አንተ የእግዚአብሔር ልጅ ነህ›› እያሉ ለኢየሱስ ሰገዱለት፡፡

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከማቴዎስ 14፡22-23፤ ማርቆስ 6፡45-52፤ ዮሐንስ 6፡16-21፡፡

32. ኢየሱስ ርኵስ መንፈስ የያዘውን ሰውና የታመመችውን ሴት ፈወሰ

Image

አንድ ቀን ኢየሱስና ደቀ መዛሙርቱ በጀልባ ሐይቁን አቋርጠው የጌርጌሴኖን ሰዎች ወደሚኖሩበት አካባቢ ሄዱ፡፡

Image

ወደ ሐይቁ ማዶ በደረሱ ጊዜ ርኵስ መንፈስ የያዘው ሰው ሮጦ ወደ ኢየሱስ መጣ፡፡

Image

ይህ ሰው ማንም ሊቈጣጠረው የማይችል እጅግ ብርቱ ነበረ፡፡ እንዲያውም ሰዎች እጆቹንና እግሮቹን በሰንሰለት አስረውት ነበር፣ ነገር ግን ሰንሰለቱን ይበጣጥስ ነበር፡፡

Image

ሰውዬው በአካባቢው ባሉ መቃብሮች መካከል ይኖር ነበር፡፡ ይህ ሰው ቀኑንና ሌሊቱን ሁሉ ይጮኽ ነበር፡፡ ልብስም አይለብስም ነበር፣ ሰውነቱንም በተደጋጋሚ በድንጋይ ይቧጭር ነበር፡፡

Image

ሰውዬው ወደ ኢየሱስ በመጣ ጊዜ፣ በፊቱ በጉልበቱ ወድቆ ሰገደለት፡፡ ኢየሱስ ርኵስ መንፈሱን፣ ‹‹ከዚህ ሰው ውጣ!›› አለው፡፡

Image

ርኵስ መንፈሱ ያለበት ሰው ከፍ ባለ ድምፅ ‹‹የልዑል እግዚአብሔር ልጅ ኢየሱስ ሆይ፣ ከእኔ ምን ትፈልጋለህ? እባክህን አታሠቃየኝ!›› ብሎ ከፍ ባለ ድምፅ ጮኸ፡፡ ከዚያም ኢየሱስ ርኵስ መንፈሱን፣ ‹‹ስምህ ማን ነው?›› ብሎ ጠየቀው፡፡ እርሱም፣ ‹‹ብዙዎች ነንና ስሜ ሌጌዎን ነው›› ብሎ መለሰ፡፡ (‹ሌጌዎን› በሮማ ጦር ሠራዊት ብዙ ሺህ ወታደሮችን የያዘ ክፍል ነበር፡፡)

Image

ርኵሳን መናፍስቱ፣ ‹‹እባክህን ከዚህ አካባቢ አታርቀን!›› ብለው ኢየሱስን ለመኑት፡፡ በአቅራቢያው ባለ ኮረብታ ላይ የእሪያ መንጋ ተሰማርቶ ነበር፡፡ ስለዚህ ርኵሳን መናፍስቱ ኢየሱስን፣ ‹‹እባክህን በዚህ ፈንታ ወደ እሪያዎቹ እንድንገባ ስደደን!›› ብለው ለመኑት፡፡ ኢየሱስ፣ ‹‹ሂዱ!›› አላቸው፡፡

Image

ርኵሳን መናፍስቱ ከሰውዬው ወጡና ወደ እሪያዎቹ ገቡ፡፡ እሪያዎቹ ከአፋፉ ቊልቊል ሮጡና በሐይቁ ሰጠሙ፡፡ በመንጋው 2,000 ያህል እሪያዎች ነበሩ፡፡

Image

እሪያዎቹን ይጠብቁ የነበሩት ሰዎች የሆነውን ነገር ባዩ ጊዜ ወደ ከተማ ሮጡና ኢየሱስ ያደረገውን ነገር ላገኙት ሰው ሁሉ ተናገሩ፡፡ የከተማው ሰዎች መጡና ርኵሳን መናፍስት የነበሩበትን ሰው ዐዩ፡፡ ልብሱን ለብሶ ጤናማ ሰው ሆኖ በጸጥታ ተቀምጦ ነበር፡፡

Image

ሰዎቹ በጣም ፈርተው ነበርና ኢየሱስን እንዲሄድ ጠየቁት፡፡ ስለዚህ ኢየሱስ ጀልባ ውስጥ ገባና ለመሄድ ተዘጋጀ፡፡ ርኵሳን መናፍስት የነበሩበት ሰውዬም ከኢየሱስ ጋር ለመሄድ ለመነው፡፡

Image

ነገር ግን ኢየሱስ፣ ‹‹አይደለም፣ ወደ ቤትህ ሄደህ እግዚአብሔር ስላደረገልህ ነገር ሁሉና እንዴት እንደ ማረህ ለወዳጆችህና ለቤተ ሰብህ እንድትነግር እፈልጋለሁ›› አለው፡፡

Image

ስለዚህ ሰውዬው ሄደና ኢየሱስ ስላደረገለት ነገር ለሁሉም ሰው ተናገረ፡፡ ታሪኩን የሰማ ሰው ሁሉ በአድናቆትና በአግራሞት ተሞላ፡፡

Image

ኢየሱስ ወደ ሐይቁ ማዶ ተመለሰ፡፡ እዚያ በደረሰ ጊዜ ብዙ ሕዝብ በዙሪያው ተሰበሰቡና አጨናነቁት፡፡ በሕዝቡ መካከል ለዐሥራ ሁለት ዓመት ደም ሲፈስባት የነበረች ሴት ነበረች፡፡ እንዲፈውሱአት ገንዘብዋን ሁሉ ለሐኪሞች ከፍላ ነበር፣ ነገር ግን ባሰባት እንጂ አልተፈወሰችም፡፡

Image

ኢየሱስ ብዙ በሽተኞችን እንደ ፈወሰ ሰምታ ነበርና፣ ‹‹የኢየሱስን ልብስ ብቻ ብዳስስ ያኔ እኔም እንደምፈወስ እርግጠኛ ነኝ!›› ብላ ዐሰበች፡፡ ስለዚህ ከኢየሱስ ኋላ መጣችና ልብሱን ዳሰሰች፡፡ ልብሱን እንደ ዳሰሰች ወዲያውኑ ደምዋ ቆመ!

Image

ወዲያውኑ፣ ኢየሱስ ኃይል ከእርሱ እንደ ወጣ ዐወቀ፡፡ ስለዚህ ወደ ኋላ ዞረና፣ ‹‹ማን ነው የዳሰሰኝ?›› ብሎ ጠየቀ፡፡ ደቀ መዛሙርቱ፣ ‹‹በዙሪያህ የተሰበሰቡና የሚያጋፉህ ብዙ ሰዎች አሉ፡፡ ለምን ‹ማን ዳሰሰኝ› ብለህ ትጠይቃለህ?›› ብለው መለሱለት፡፡

Image

ሴቲቱ በጣም ፈርታ እየተንቀጠቀጠች በኢየሱስ ፊት ተደፋች፡፡ ከዚያም ምን እንዳደረገችና እንደ ተፈወሰች ነገረችው፡፡ ኢየሱስም፣ ‹‹እምነትሽ አድኖሻል፡፡በሰላም ሂጂ›› አላት፡፡

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከማቴዎስ 8፡28-34፤ 9፡20-22፤ ማርቆስ 5፡1-20፤ 5፡24-34፤ ሉቃስ 8፡26-39፤ 8፡42-48፡፡

33. የአርሶ አደሩ ታሪክ

Image

አንድ ቀን ኢየሱስ በሐይቁ ዳርቻ አጠገብ በጣም ብዙ ሕዝብ እያስተማረ ነበር፡፡ ኢየሱስ ሊናገራቸው በቂ ቦታ ለማግኘት በውሃው ዳርቻ በጀልባ ገብቶ እስኪቀመጥ ድረስ በጣም ብዙ ሰዎች ሊሰሙት መጡ፡፡ በጀልባው ተቀመጠና ሕዝቡን አስተማረ፡፡

Image

ኢየሱስ ይህንን ምሳሌ ተናገረ፡፡ ‹‹አንድ አርሶ አደር ዘር ሊዘራ ወጣ፡፡ በእጁ ዘሩን ሲዘራ አንዳንዱ በመንገድ ዳር ወደቀ፣ ወፎችም መጥተው ያን ዘር በሙሉ በሉት፡፡››

Image

‹‹ሌላው ዘር ብዙ አፈር በሌለበት በአለታማ መሬት ላይ ወደቀ፣ ዘሩም ቶሎ ወዲያው በቀለ፤ ነገር ግን ብዙ አፈር ስለሌለ ሥሩ ወደ መሬት መጥለቅ አልቻለም፡፡ ፀሐይዋ በወጣችና በሞቀች ጊዜ፣ ቡቃያው ጠወለገና ደረቀ፡፡››

Image

‹‹አሁንም ሌላው ዘር በእሾኽ መካከል ወደቀ፡፡ ይህ ዘር መብቀል ጀመረ፣ ነገር ግን እሾኹ አነቀው፡፡ ስለዚህ በእሾኻማው መሬት ላይ የበቀለው ቡቃያ ምንም ፍሬ አላፈራም፡፡››

Image

‹‹ሌላው ዘር በመልካም መሬት ላይ ወደቀ፡፡ ይህ ዘር በቀለና አንዱ 30፣ አንዱ 60፣ አንዱም መቶ ፍሬ ሰጠ፡፡ ጆሮ ያለው ይስማ!››

Image

ይህ ምሳሌ ደቀ መዛሙርቱን ግራ አጋባቸው፡፡ ስለዚህ ኢየሱስ እንዲህ ብሎ አብራራላቸው፣ ‹‹ዘሩ የእግዚአብሔር ቃል ነው፡፡ በመንገዱ ዳር የተዘራው ዘር የሚያሳየው የእግዚአብሔርን ቃል የሚሰማ ሰው ነው፣ ነገር ግን አያስተውለውም፣ ዲያብሎስም ቃሉን ይወስድበታል፡፡››

Image

‹‹በአለታማ መሬት የተዘራው ዘር የሚያሳየው የእግዚአብሔርን ቃል ሰምቶ በደስታ የሚቀበለው ሰው ነው፡፡ ነገር ግን መከራ ወይም ስደት በሚያጋጥመው ጊዜ እምነቱን ይተዋል፡፡››

Image

‹‹በእሾኻማው መሬት ላይ የተዘራው ዘር የሚያሳየው የእግዚአብሔርን ቃል የሚሰማ ሰው ነው፣ ነገር ግን ከጊዜ በኋላ የዚህ ዓለም ዐሳብ፣ ባለጠግነትና ደስታ ለእግዚአብሔር ያለውን ፍቅር ያንቃል፡፡ ከዚህ የተነሣ፣ የሰማው ትምህርት ፍሬ አያፈራም፡፡

Image

‹‹በመልካሙ መሬት ላይ የተዘራው ዘር የሚያሳየው ግን የእግዚአብሔርን ቃል የሚሰማ፣ የሚያምነውና ፍሬ የሚያፈራ ሰው ነው፡፡››

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከማቴዎስ 13፡1-8፣ 18-23፤ ማርቆስ 4፡1-8፣ 13-20፤ ሉቃስ 8፡4-15፡፡

34.ኢየሱስ ሌሎች ታሪኮችን አስተማረ

Image

ኢየሱስ ስለ እግዚአብሔር መንግሥት ሌሎች ብዙ ምሳሌዎችን አስተማረ፡፡ ለምሳሌ፣ እንዲህ አለ፣ ‹‹የእግዚአብሔር መንግሥት ሰው በማሳው የዘራትን የሰናፍጭ ዘር ትመስላለች፡፡ እርስዋም ከሁሉ ዘር የምታንስ ነች፡፡››

Image

‹‹ነገር ግን የሰናፍጭ ዘር ባደገች ጊዜ አዕዋፍ መጥተው እስኪሰፍሩ ድረስ በአትክልት ቦታ ካሉ ተክሎች ሁሉ ትበልጣለች፡፡

Image

ኢየሱስ ሌላ ምሳሌ ተናገረ፣ ‹‹የእግዚአብሔር መንግሥት ሴት ወስዳ ሁሉ እስኪቦካ ድረስ ከዱቄት ጋር የለወሰችውን እርሾ ትመስላለች፡፡

Image

‹‹ደግሞ የእግዚአብሔር መንግሥት ሰው በእርሻ ውስጥ የሸሸገውን የሀብት መዝገብ ትመስላለች፡፡ ሌላ ሰው መዝገቡን አገኘውና እንደ ገና ቀበረው፡፡ በጣም በደስታ ተሞልቶ ነበርና ሄዶ ያለውን ነገር ሁሉ ሸጠና በገንዘቡ እርሻውን ገዛው፡፡››

Image

‹‹ደግሞ የእግዚአብሔር መንግሥት ዋጋዋ እጅግ ውድ የሆነ ዕንቊ ትመስላለች፡፡ የዕንቊ ነጋዴ ባገኛት ጊዜ ያለውን ነገር ሁሉ ሸጠና ገዛት፡፡››

Image

ከዚያ በኋላ ኢየሱስ በራሳቸው መልካም ሥራ ለሚታመኑና ሌሎችን ለሚንቁ አንዳንድ ሰዎች ምሳሌ ተናገረ፡፡ ‹‹ሁለት ሰዎች ሊጸልዩ ወደ ቤተ መቅደስ ሄዱ፡፡ አንዱ ቀረጥ ሰብሳቢ ሲሆን፣ ሌላው የሃይማኖት መሪ ነበር››፡፡

Image

‹‹የሃይማኖት መሪው እንዲህ ብሎ ጸለየ፣ ‹እግዚአብሔር ሆይ፣ እንደ ሌሎች ሰዎች ሁሉ፣ ቀማኛ፣ ዓመፀኛ፣ አመንዝራ፣ እንደዚሁም እንደዚህኛው ቀረጥ ሰብሳቢ ስላልሆንኩ አመሰግንሃለሁ፡፡››

Image

‹‹እኔ በየሳምንቱ ሁለት ጊዜ እጾማለሁ፣ ከማገኘውም ገንዘብና ንብረት ሁሉ ከዐሥር አንድ አወጣለሁ፡፡››

Image

‹‹ቀረጥ ሰብሳቢው ግን ከሃይማኖት መሪው ራቅ ብሎ ቆመ፣ ወደ ሰማይ እንኳ አልተመለከተም፡፡ በዚህ ፈንታ፣ ደረቱን በእጁ እየመታ፣ ‹እግዚአብሔር ሆይ፣ እኔ ኃጢአተኛ ስለ ሆንኩ እባክህን ማረኝ››› አለ፡፡

Image

ከዚያ በኋላ ኢየሱስ እንዲህ አለ፣ ‹‹እውነት እላችኋለሁ፣ እግዚአብሔር የቀረጥ ሰብሳቢውን ጸሎት ሰማና ጻድቅ ነህ አለው፡፡ የሃይማኖት መሪውን ጸሎት ግን አልወደደም፡፡ እግዚአብሔር ራሱን ከፍ ከፍ የሚያደርገውን ሁሉ ያዋርዳል፣ ራሱን የሚያዋርደውን ግን ከፍ ከፍ ያደርጋል፡፡››

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከማቴዎስ 13፡31-33፣ 44-46፤ ማርቆስ 4፡30-32፤ ሉቃስ 13፡18-21፤ 18፡9-14፡፡

35. የርኅሩኁ አባት ታሪክ

Image

አንድ ቀን ኢየሱስ ብዙ ቀረጥ ሰብሳቢዎችንና ሊሰሙት የተሰበሰቡ ሌሎች ኃጢአተኞችን ያስተምር ነበር፡፡

Image

በዚያ የነበሩ አንዳንድ የሃይማኖት መሪዎች ኢየሱስ ኃጢአተኞችን ወዳጆች አድርጎ ሲቀበላቸው ዐዩ፣ እርስ በርሳቸውም ይነቅፉት ጀመር፡፡ ስለዚህ ኢየሱስ ይህንን ምሳሌ ነገራቸው፡፡

Image

ሁለት ልጆች ያሉት አንድ ሰው ነበር፡፡ ታናሹ ልጅ አባቱን፣ ‹አባቴ ሆይ፣ ከገንዘብህ የሚደርሰኝን ድርሻ አሁን እንድትሰጠኝ እፈልጋለሁ!› አለው፡፡ ስለዚህ አባትዬው ገንዘቡን ለሁለቱ ልጆቹ አካፈላቸው፡፡››

Image

‹‹ታናሹ ልጅ ወዲያውኑ ያለውን ሁሉ ሰበሰበና ሩቅ አገር ሄዶ በኃጢአት የተሞላ ኑሮ እየኖረ ገንዘቡን አጠፋ፡፡

Image

‹‹ከዚያ በኋላ ታናሹ ልጅ በነበረበት አገር ጽኑ ረሀብ ሆነ፣ ምግብ የሚገዛበት ገንዘብም አልነበረውም፡፡ ስለዚህ የተገኘው ሥራ እሪያዎችን የመመገብ ሥራ ብቻ ስለ ነበር በዚያ ሥራ ገባ፡፡ በጣም ተጐሳቊሎና ተርቦ ስለ ነበር የእሪያዎችን ምግብ እንኳ ለመብላት ይመኝ ነበር፡፡››

Image

‹‹በመጨረሻ፣ ታናሹ ልጅ ለራሱ እንዲህ አለ፣ ‹እዚህ ምን እያደረግሁ ነው ያለሁት? የአባቴ አገልጋዮች ሁሉ እንኳ የሚበሉት ብዙ ምግብ አላቸው፣ እኔ ግን እዚህ በረሃብ እሞታለሁ፡፡ ወደ አባቴ ተመልሼ እሄድና ከአገልጋዮቹ እንደ አንዱ እንዲያደርገኝ እለምነዋለሁ፡፡›››

Image

ስለዚህ ታናሹ ልጅ ወደ አባቱ ቤት ተመልሶ መሄድ ጀመረ፡፡ ገና በሩቅ እያለ አባቱ ዐየውና አዘነለት፡፡ ወደ ልጁ ሮጠና አቀፈው ሳመውም፡፡››

Image

ልጁም፣ ‹አባቴ ሆይ፣ እግዚአብሔርንና አንተን በድዬአለሁ፡፡ ከእንግዲህ ልጅህ ልባል አይገባኝም› አለ፡፡

Image

‹‹ነገር ግን አባቱ ከአገልጋዮቹ ለአንዱ እንዲህ ብሎ ነገረው፣ ‹ፈጥነህ ሂድና ምርጥ ልብስ አምጥተህ ለልጄ አልብሰው! ለጣቱም ቀለበት፤ ለእግሩም ጫማ አድርግለት፡፡ ከዚያም በልተን ፈንጠዝያ እናደርግ ዘንድ የሰባ ፍሪዳ አምጥተህ እረድ፣ ምክንያቱም ይህ ልጄ ሞቶ ነበር፣ አሁን ሕያው ሆኖአል! ጠፍቶ ነበር፣ አሁን ግን ተገኝቶአል!›››

Image

‹‹ስለዚህ ሰዎቹ ፈንጠዝያ ማድረግ ጀመሩ፡፡ ብዙም ሳይቆይ፣ ታላቅ ወንድሙ ይሠራበት ከነበረው እርሻ ወደ ቤት መጣ፡፡ የሙዚቃና የዘፈን ድምፅም ሰማ፣ ምን እየሆነ ነው ብሎም ተገረመ፡፡››

Image

‹‹ታላቁ ልጅም ታናሽ ወንድሙ ስለ መጣ ሰዎች እየተደሰቱ መሆናቸውን ባወቀ ጊዜ፣ በጣም ስለ ተቈጣ ወደ ቤት ለመግባት ፈቃደኛ አልሆነም፡፡ አባቱ ወጣና ገብቶ ከእነርሱ ጋር እንዲደሰት ለመነው፣ እርሱ ግን እምቢ አለ፡፡››

Image

ታላቁ ልጅ አባቱን እንዲህ አለው፣ ‹እነዚህን ዓመታት ሁሉ በታማኝነት ለአንተ ሠርቼአለሁ! አንድም ቀን ስታዘኝ እምቢ ብዬህ አላውቅም። ይሁን እንጂ ከጓደኞቼ ጋር እንድደሰት አንድ ጥቦት ፍየል እንኳ እስከ አሁን ሰጥተኸኝ አታውቅም። ነገር ግን አሁን ይህ ኃጢአት በመሥራት ገንዘብህን ያባከነው ልጅህ ወደ ቤትህ በመጣ ጊዜ፣ የሰባ ፍሪዳ አረድህለት!›

Image

‹‹አባቱ እንዲህ ብሎ መለሰለት፣ ‹ልጄ፣ አንተ ሁልጊዜ ከእኔ ጋር ነህ፣ ያለኝም ነገር ሁሉ የአንተ ነው፡፡ ነገር ግን ይህ ወንድምህ ሞቶ ነበር፣ አሁን ግን ሕያው ሆኖአል፡፡ ጠፍቶ ነበር፣ አሁን ግን ተገኝቶአል! ስለዚህ እኛ መደሰታችን ትክክል ነው›› አለው።

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከሉቃስ 15፡11-32፡፡

36. የኢየሱስ መልክ ተለወጠ

Image

አንድ ቀን ኢየሱስ ከደቀ መዛሙርቱ ሦስቱን፦ ጴጥሮስን፣ ያዕቆብንና ዮሐንስን ይዞ ብቻቸውን ሊጸልዩ ወደ ረጅም ተራራ ወጡ፡፡(ዮሐንስ የተባለው ደቀ መዝሙር ኢየሱስን ያጠመቀው ዮሐንስ አይደለም፡፡)

Image

ኢየሱስ በመጸለይ ላይ እያለ፣ ፊቱ እንደ ፀሐይ አበራ፣ ልብሱም እንደ ብርሃን ነጭ ሆነ፣ ንጻቱም በምድር ላይ ያለ ማንኛውም ሰው ሊያነጻው እስከማይችል ድረስ በጣም ነጭ ነበር፡፡

Image

በዚያን ጊዜ ሙሴና ነቢዩ ኤልያስ ታዩ፡፡ እነዚህ ሰዎች በመቶዎች ከሚቈጠሩ ዓመታት በፊት በምድር ላይ ይኖሩ ነበር፡፡ እነርሱም በቅርቡ በኢየሩሳሌም ስለሚሆነው ስለ ኢየሱስ ሞት ከእርሱ ጋር ተነጋገሩ፡፡

Image

ሙሴና ኤልያስ ከኢየሱስ ጋር በመነጋገር ላይ እያሉ ጴጥሮስ ኢየሱስን፣ ‹‹በዚህ መሆን ለእኛ መልካም ነው፡፡ ሦስት ዳሶችን አንድ ለአንተ፣ አንድ ለሙሴ፣ እንዲሁም አንድ ለኤልያስ እንሥራ›› አለው፡፡ ጴጥሮስ የሚናገረውን አያውቅም ነበር፡፡

Image

ጴጥሮስ እየተናገረ እያለ፣ ብሩህ ደመና መጥቶ ከበባቸውና ከደመናውም ድምፅ፣ ‹‹በእርሱ ደስ የሚለኝ የምወደው ልጄ ይህ ነው፣ እርሱን ስሙት›› አለ፡፡ ሦስቱ ደቀ መዛሙርት ፈሩና መሬት ላይ ወደቁ፡፡

Image

በዚያን ጊዜ ኢየሱስ ዳሰሳቸውና፣ ‹‹አትፍሩ፣ ተነሡ›› አላቸው፡፡ ዙሪያቸውን ሲያዩ ከእነርሱ ጋር ያለው ኢየሱስ ብቻ ነበር፡፡

Image

ኢየሱስና ሦስቱ ደቀ መዛሙርት ከተራራው ወረዱ፡፡ በዚያን ጊዜ ኢየሱስ እንዲህ አላቸው፣ ‹‹በዚህ ስለ ሆነው ነገር አሁን ለማንም አትናገሩ፡፡ እኔ በቅርብ ጊዜ እሞታለሁ፣ ተመልሼም ሕያውም እሆናለሁ፡፡ ከዚያ በኋላ ለሰዎች መናገር ትችላላችሁ፡፡››

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከማቴዎስ 17፡1-9፤ ማርቆስ 9፡2-8፤ ሉቃስ 9፡28-36፡፡

37. ኢየሱስ አልዓዛርን ከሞት አስነሣ

Image

አንድ ቀን ኢየሱስ አልዓዛር በጣም ታሞአል የሚል መልእክት ደረሰው፡፡ አልዓዛርና ሁለቱ እኅቶቹ ማርያምና ማርታ የኢየሱስ የቅርብ ወዳጆች ነበሩ፡፡ ኢየሱስ ይህንን ወሬ በሰማ ጊዜ፣ ‹‹ይህ ሕመም ለእግዚአብሔር ክብር ነው እንጂ ለሞት አይደለም›› አለ፡፡ ኢየሱስ እነርሱን ይወዳቸው ነበር፣ ነገር ግን ለሁለት ቀናት በነበረበት ስፍራ ቆየ፡፡

Image

ሁለቱ ቀናት ካለፉ በኋላ፣ ኢየሱስ ደቀ መዛሙርቱን፣ ‹‹ወደ ይሁዳ ምድር ተመልሰን እንሂድ›› አላቸው፡፡ ደቀ መዛሙርቱም መልሰው ‹‹ነገር ግን መምህር ሆይ፣ ‹‹ከጥቂት ጊዜ በፊት በዚያ ያሉት ሕዝብ ሊገድሉህ ይፈልጉ ነበር!›› አሉ፡፡ ኢየሱስ፣ ‹‹ወዳጃችን አልዓዛር አንቀላፍቶአል፣ ከእንቅልፉ ማስነሣት አለብኝ›› አላቸው፡፡

Image

የኢየሱስ ደቀ መዛሙርት፣ ‹‹ጌታ ሆይ፣ አልዓዛር ተኝቶስ ከሆነ፣ ተሽሎታል›› ብለው መለሱለት፡፡ በዚያን ጊዜ ኢየሱስ፣ ‹‹አልዓዛር ሞቶአል፡፡ እናንተ በእኔ ታምኑ ዘንድ እዚያ ባለመኖሬ ደስ ብሎኛል›› ብሎ በግልጽ ነገራቸው።

Image

ኢየሱስ አልዓዛር ወደ ተወለደበት ከተማ በደረሰ ጊዜ፣ አልዓዛር ከሞተ አራት ቀን ሆኖት ነበር፡፡ ማርታ ኢየሱስን ልትገናኘው ወጣችና እንዲህ አለች፣ ‹‹ጌታ ሆይ፣ አንተ እዚህ ብትኖር ኖሮ ወንድሜ አይሞትም ነበር፡፡ ነገር ግን እግዚአብሔር የምትለምነውን ሁሉ እንደሚሰጥህ አምናለሁ፡፡››

Image

ኢየሱስም መልሶ፣ ‹‹እኔ ትንሣኤና ሕይወት ነኝ፡፡ በእኔ የሚያምን ሁሉ ቢሞት እንኳ ሕያው ይሆናል፡፡ በእኔ የሚያምን ሁሉ ከቶ አይሞትም፡፡ ይህን ታምኛለሽን?›› አላት፡፡ ማርታም፣ ‹‹አዎን፣ ጌታ ሆይ! አንተ መሲሑ፣ የእግዚአብሔር ልጅ መሆንህን አምናለሁ›› ብላ መለሰችለት፡፡

Image

ከዚያም ማርያም መጣች፡፡ በኢየሱስ እግር ወደቀችና፣ ‹‹ጌታ ሆይ፣ አንተ በዚህ ኖረህ ብትሆን ኖሮ ወንድሜ ባልሞተም ነበር›› አለች፡፡ ኢየሱስ፣ ‹‹አልዓዛርን ወዴት ነው ያኖራችሁት?›› ብሎ ጠየቃቸው፡፡ እነርሱም ‹‹በመቃብር ነው፡፡ ናና እይ›› ብለው ነገሩት፡፡ ከዚያም ኢየሱስ አለቀሰ፡፡

Image

መቃብሩ ዋሻ ነበር፣ ድንጋይም በአፉ ላይ ተገጥሞበት ነበር፡፡ ኢየሱስ ወደ መቃብሩ በደረሰ ጊዜ ‹‹ድንጋዩን አንከባሉት›› ብሎ ነገራቸው፡፡ ነገር ግን ማርታ፣ ‹‹ከሞተ አራት ቀን ሆኖታል፡፡ አሁን ይሸታል›› አለችው፡፡

Image

ኢየሱስ፣ ‹‹በእኔ ብታምኚስ የእግዚአብሔርን ክብር ታይዋለሽ ብዬ አልነገርኩሽምን?›› አላት፡፡ ስለዚህ ድንጋዩን አንከባለሉት፡፡

Image

ከዚያ በኋላ ኢየሱስ ወደ ላይ ተመለከተና፣ ‹‹አባት ሆይ፣ ስለምትሰማኝ አመሰግንሃለሁ፡፡ አንተ ሁልጊዜ እንደምትሰማኝ ዐውቃለሁ፣ ነገር ግን አንተ እንደ ላክኸኝ ያምኑ ዘንድ እዚህ ስለ ቆሙት ስለ እነዚህ ሰዎች ሁሉ ይህን እላለሁ›› አለ፡፡ ከዚያም ኢየሱስ፣ ‹‹አልዓዛር ሆይ፣ ወደ ውጭ ና!›› ብሎ ጮኸ፡፡

Image

ስለዚህ አልዓዛር ወጣ! በከፈን እንደ ተገነዘ ነበር፡፡ ኢየሱስም፣ ‹‹ፍቱትና ይሂድ ተዉት!›› አላቸው፡፡ ከአይሁድ ብዙዎች በዚህ ተአምር ምክንያት በኢየሱስ አመኑ፡፡

Image

ነገር ግን የአይሁድ የሃይማኖት መሪዎች ቀኑ፣ ስለዚህ ኢየሱስንና አልዓዛርን እንዴት መግደል እንዳለባቸው ለማቀድ በአንድ ላይ ተሰበሰቡ፡፡

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከዮሐንስ 11፡1-46፡፡

38. ኢየሱስ ተላልፎ ተሰጠ

Image

አይሁድ በያመቱ የፋሲካን በዓል ያከብሩ ነበር፡፡ ይህም በዓል ከብዙ ምእት ዓመታት በፊት እግዚአብሔር ቅድመ አያቶቻቸውን ከግብፅ ባርነት እንዴት እንዳዳናቸው ለማስታወስ የሚከበር ነበር፡፡ ኢየሱስ በይፋ መስበኩንና ማስተማሩን ከጀመረ ከሦስት ዓመት ገደማ በኋላ፣ ይህን ፋሲካ በኢየሩሳሌም ከእነርሱ ጋር ሊያከብር እንደ ፈለገ፣ በዚያም እንደሚገደል ለደቀ መዛሙርቱ ነገራቸው፡፡

Image

ከኢየሱስ ደቀ መዛሙርት አንዱ ይሁዳ ተብሎ ይጠራ ነበር፡፡ ይሁዳ የሐዋርያቱ ገንዘብ ያዥ ነበር፣ ነገር ግን ገንዘብ ይወድ ነበርና ብዙ ጊዜ ከከረጢቱ ውስጥ ገንዘብ ይሰርቅ ነበር፡፡ ኢየሱስና ደቀ መዛሙርቱ ወደ ኢየሩሳሌም ከደረሱ በኋላ፣ ይሁዳ ወደ አይሁድ መሪዎች ሄደና ገንዘብ ከሰጡት ኢየሱስን አሳልፎ ሊሰጣቸው እንደሚችል ነገራቸው፡፡ ኢየሱስ መሲሕ መሆኑን የአይሁድ መሪዎች እንደ ካዱና ሊገድሉት ያሤሩ እንደ ነበር ያውቅ ነበር፡፡

Image

የአይሁድ መሪዎችም በሊቀ ካህናቱ ተመርተው፣ ኢየሱስን አሳልፎ እንዲሰጣቸው ለይሁዳ ሠላሳ ጥሬ ብር ከፈሉት፡፡ ልክ ነቢያት እንደ ተነበዩት ይህ ሆነ፡፡ ይሁዳም ተስማማ፣ ገንዘቡንም ተቀብሎ ሄደ፡፡ ኢየሱስን እንዲይዙት ሊረዳቸው አጋጣሚ መፈለግ ጀመረ፡፡

Image

በኢየሩሳሌም፣ ኢየሱስ ከደቀ መዛሙርቱ ጋር ፋሲካን አከበረ፡፡ በፋሲካው ምግብ ጊዜ ኢየሱስ እንጀራን አንሥቶ ቈረሰ፡፡ እንዲህም አለ፣ ‹‹እንካችሁ ይህንን ብሉ፡፡ ይህ ስለ እናንተ የተሰጠ ሥጋዬ ነው፡፡ ይህንን ለመታሰቢያዬ አድርጉት፡፡›› በዚህ ዓይነት ኢየሱስ ሥጋው ስለ እነርሱ እንደሚሠዋ ነገራቸው፡፡

Image

ከዚያም ኢየሱስ ጽዋን አንሣና፣ ‹‹ይህንን ጠጡ፡፡ ለኃጢአት ይቅርታ የሚፈስ የዐዲስ ኪዳን ደሜ ነው፡፡ ይህንን በጠጣችሁ ጊዜ ሁሉ ለመታሰቢያዬ አድርጉት፡፡››

Image

ከዚያም ኢየሱስ ደቀ መዛሙርቱን፣ ‹‹ከእናንተ አንዱ እኔን አሳልፎ ይሰጠኛል›› አላቸው፡፡ ደቀ መዛሙርቱ ደንግጠው፣ እንዲህ ያለ ነገር ማን ያደርጋል ብለውም ጠየቁት፡፡ ኢየሱስ፣ ‹‹ይህንን ቊራሽ እንጀራ የምሰጠው ሰው እኔን አሳልፎ የሚሰጠኝ እርሱ ነው›› አለ፡፡ ከዚያ በኋላ እንጀራውን ለይሁዳ ሰጠው፡፡

Image

ይሁዳ እንጀራውን ከተቀበለ በኋላ፣ ሰይጣን ገባበት፡፡ ይሁዳ ኢየሱስን እንዲይዙት የአይሁድ መሪዎችን ሊረዳቸው ሄደ፡፡ ጊዜው ማታ ነበር፡፡

Image

ኢየሱስና ደቀ መዛሙርቱ እራት ከበሉ በኋላ ወደ ደብረ ዘይት ሄዱ፡፡ ኢየሱስ፣ ‹‹ዛሬ ማታ ሁላችሁም እኔን ብቻዬን ትተዉኛላችሁ፡፡ ‹እረኛውን እመታለሁ፤ በጎቹም ሁሉ ይበተናሉ› ተብሎ ተጽፎአል›› አለ፡፡

Image

ጴጥሮስ፣ ‹‹ሌሎቹ ሁሉ ቢተዉህ እንኳ፣ እኔ ግን አላደርገውም!›› ብሎ መለሰ፡፡ በዚያን ጊዜ ኢየሱስ ጴጥሮስን እንዲህ አለው፣ ‹‹ሰይጣን ሁላችሁንም እንደ ስንዴ ሊያበጥራችሁ፥ ይፈልጋል፣ ነገር ግን ጴጥሮስ እምነትህ እንዳይደክም ጸልዬልሃለሁ፡፡ እንደዚያም ሆኖ ግን ዛሬ ማታ ዶሮ ከመጮኹ በፊት እንደውም አላውቀውም ብለህ ሦስት ጊዜ ትክደኛለህ፡፡››

Image

በዚያን ጊዜ ጴጥሮስ ለኢየሱስ፣ ‹‹የምሞት እንኳ ቢሆን፣ ከቶ አልክድህም›› አለው፡፡ ሌሎቹም ደቀ መዛሙርት ሁሉ ይህንኑ አሉ፡፡

Image

ከዚያ በኋላ ኢየሱስ ከደቀ መዛሙርቱ ጋር ጌቴሴማኒ ወደሚባል ቦታ ሄደ፡፡ ኢየሱስ ወደ ፈተና እንዳይገቡ እንዲጸልዩ ለደቀ መዛሙርቱ ነገራቸው፡፡ ከዚያም ኢየሱስ ብቻውን ሊጸልይ ሄደ፡፡

Image

ኢየሱስ፣ ‹‹አባቴ ሆይ፣ ቢቻልስ ይህን የመከራ ጽዋ እንዳልጠጣው አድርግ፡፡ ነገር ግን ፈቃድህ ይሁን›› ብሎ ሦስት ጊዜ ጸለየ። ኢየሱስ በጣም ታወከ፤ ላቡም እንደ ደም ነጠብጣብ ነበረ፡፡ እግዚአብሔርም እንዲያበረታታው መልአክ ላከ፡፡

Image

ከእያንዳንዱ የጸሎት ጊዜ በኋላ ኢየሱስ ወደ ደቀ መዛሙርቱ ተመልሶ ይመጣ ነበር። እነርሱ ግን ተኝተው ነበር፡፡ ሦስተኛ ተመልሶ በመጣ ጊዜ ግን፣ ‹‹ተነሡ! አሳልፎ የሚሰጠኝ ደርሷል›› አለ፡፡

Image

ይሁዳ ከአይሁድ መሪዎች፣ ከወታደሮችና ከብዙ ሕዝብ ጋር መጣ፡፡ ሰይፍና ዱላ ይዘው ነበር፡፡ ይሁዳ ወደ ኢየሱስ መጣና፣ ‹‹መምህር ሆይ፣ ሰላም ለአንተ ይሁን›› ብሎ ሳመው፡፡ ይህም የአይሁድ መሪዎች ማንን እንደሚይዙ ምልክት ነበር፡፡ ከዚያም ኢየሱስ፣ ‹‹ይሁዳ፣ በመሳም አሳልፈህ ትሰጠኛለህን?›› አለ፡፡

Image

ወታደሮቹ ኢየሱስን ሲይዙት፣ ጴጥሮስ ሰይፉን መዘዘና የሊቀ ካህናቱን አገልጋይ ጆሮ ቈረጠ፡፡ ኢየሱስ፣ ‹‹ሰይፍህን ወደ ስፍራው መልስ! ይከላከሉልኝ ዘንድ የመላእክት ሠራዊት እንዲልክልኝ አባቴን መጠየቅ እችል ነበር፤ ነገር ግን አባቴን መታዘዝ አለብኝ›› አለው፡፡ ከዚያም ኢየሱስ የሰውዬውን ጆሮ ፈወሰው፡፡ ኢየሱስ ከተያዘ በኋላ ደቀ መዛሙርቱ ሁሉ ሸሹ፡፡

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከማቴዎስ 26፡14-56፤ ማርቆስ 14፡10-50፤ ሉቃስ 22፡1-53፤ ዮሐንስ 12፡6፤ 18፡1-11፡፡

39. ኢየሱስ ለፍርድ ቀረበ

Image

አሁን ጊዜው እኩለ ሌሊት ነው። ሊቀ ካህናቱ የምርመራ ጥያቄ ይጠይቀው ዘንድ ወታደሮቹ ኢየሱስን ወደ ሊቀ ካህናቱ ቤት ወሰዱት። ጴጥሮስ ራቅ ብሎ ከኋላ ተከተላቸው። ኢየሱስን ወደ ቤቱ ባስገቡት ጊዜ፣ ጴጥሮስ በውጪ ሆኖ እሳት ይሞቅ ነበር።

Image

በቤቱ ውስጥ የአይሁድ መሪዎች ኢየሱስን ለምርመራ አቀረቡት። በእርሱ ላይ የዋሹ ብዙ የሐሰት ምስክሮችን አመጡ። ይሁን እንጂ፣ ቃላቸው እርስ በርሱ አልተስማማም፣ ስለዚህ የአይሁድ መሪዎች ኢየሱስ በማንኛውም ነገር ወንጀለኛ መሆኑን ማረጋገጥ አልቻሉም።

Image

በመጨረሻ፣ ሊቀ ካህናቱ ኢየሱስን ትኵር ብሎ ተመለከተውና፣ ‹‹ንገረን፣ አንተ መሲሑ፣ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ነህን?›› አለው።

Image

ኢየሱስም፣ ‹‹አዎን ነኝ፣ ከእግዚአብሔር ጋር ተቀምጬ ሳለሁና ከሰማይም ስመጣ ታያለህ›› አለው። ሊቀ ካህናቱ በቊጣ ልብሱን ቀደደና ለሌሎቹ የሃይማኖት መሪዎች፣ ‹‹ምንም ዓይነት ምስክሮች አያስፈልጉንም! የእግዚአብሔር ልጅ ነኝ ሲል ራሳችሁ ሰምታችሁታል። ፍርዳችሁ ምንድን ነው?›› ብሎ ጮኸ።

Image

ሁሉም የአይሁድ መሪዎች፣ ‹‹ሞት ይገባዋል!›› ብለው ለሊቀ ካህናቱ መለሱለት። ከዚያም ኢየሱስን ፊቱን ሸፈኑት፣ ተፉበት፣ መቱት፣ ዘበቱበትም።

Image

ጴጥሮስ ከቤቱ ውጪ በመጠበቅ ላይ እያለ የቤት ሠራተኛ የሆነች ልጅ ዐየችውና፣ ‹‹አንተም ደግሞ ከኢየሱስ ጋር ነበርክ!›› አለችው፡፡ ጴጥሮስ እርስዋ የተናገረችውን ካደ፡፡ ከዚያ በኋላ ሌላዋ የቤት ሠራተኛ ያንኑ ተናገረች፣ ጴጥሮስም እንደገና ካደ፡፡ በመጨረሻ ሕዝቡ ‹‹ሁለታችሁም ከገሊላ ስለሆናችሁ አንተ ከኢየሱስ ጋር መሆንህን እናውቃለን›› አሉ፡፡

Image

ከዚያም ጴጥሮስ፣ ‹‹ይህንን ሰው እኔ አላውቀውም!›› ብሎ ማለ። ወዲያውኑ ዶሮ ጮኸ፣ ኢየሱስም ዘወር አለና ጴጥሮስን ተመለከተው።

Image

ጴጥሮስ ከዚያ ሄደና በምሬት አለቀሰ። ይህ በእንዲህ እንዳለ፣ ኢየሱስን አሳልፎ የሰጠው ይሁዳ፣ የአይሁድ መሪዎች እንዲሞት በኢየሱስ ላይ እንደ ፈረዱበት ዐየ። ይሁዳ በሐዘን ተሞልቶ ሄደና ራሱን ገደለ።

Image

በነጋታው ማለዳ ላይ የአይሁድ መሪዎች ኢየሱስን ወደ ሮማው ገዥ ወደ ጲላጦስ አመጡት። ጲላጦስ ኢየሱስን ወንጀለኛ ነህ ብሎ ይፈርድበትና በሞት እንዲቀጣ ያደርጋል ብለው ተስፋ አድርገው ነበር። ጲላጦስ ኢየሱስን፣ ‹‹የአይሁድ ንጉሥ ነህን?›› ብሎ ጠየቀው።

Image

ኢየሱስ እንዲህ ብሎ መለሰለት፣ ‹‹አንተም ብለሃል፣ ነገር ግን መንግሥቴ ምድራዊ መንግሥት አይደለችም። እንደዚያ ቢሆን ኖሮ፣ አገልጋዮቼ ይዋጉልኝ ነበር። እኔ ስለ እግዚአብሔር እውነትን ለመናገር ወደ ምድር መጥቼአለሁ። እውነትን የሚወድ ሁሉ እኔን ይሰማኛል።›› ጲላጦስ፣ ‹‹እውነት ምንድን ነው?›› አለ።

Image

ጲላጦስ ከኢየሱስ ጋር ከተናገረ በኋላ ወደ ሕዝቡ ወጣና፣ ‹‹በዚህ ሰው ላይ ምንም ወንጀል አላገኘሁበትም›› አለ። የአይሁድ መሪዎችና ሕዝቡ ግን፣ ‹‹ስቀለው!›› ብለው ጮኹ። ጲላጦስ፣ ‹‹ወንጀለኛ አይደለም›› ብሎ መለሰላቸው። እነርሱ ግን የበለጠ ጮኹ። ከዚያም ጲላጦስ ለሦስተኛ ጊዜ፣ ‹‹ወንጀለኛ አይደለም!›› አለ።

Image

ጲላጦስ ሕዝቡ ረበሻ ያስነሣል ብሎ ፈራ፣ ስለዚህ ኢየሱስን እንዲሰቅሉት ወታደሮቹን አዘዘ። የሮማ ወታደሮችም ኢየሱስን ገረፉትና ቀይ የነገሥታት ልብስ አለበሱት፣ እንዲሁም የሾኽ አክሊል በራሱ ላይ አደረጉ። ከዚያም፣ ‹‹እነሆ፣ የአይሁድ ንጉሥ!›› እያሉ ዘበቱበት።

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከማቴዎስ 26፡57-27፡26፤ ማርቆስ 14፡53-15፡15፤ ሉቃስ 22፡54-23፡25፤ ዮሐንስ 18፡12-19፡16።

40. ኢየሱስ ተሰቀለ

Image

ወታደሮቹ በኢየሱስ ላይ ከዘበቱበት በኋላ፣ ሊሰቅሉት ወሰዱት። የሚሞትበትን መስቀል እንዲሸከም አደረጉት።

Image

ወታደሮቹ ኢየሱስን ‹‹የራስ ቅል›› ተብሎ ወደሚጠራው ስፍራ አመጡትና እጆቹንና እግሮቹን በመስቀል ላይ ጠረቁአቸው። ኢየሱስ ግን፣ ‹‹አባት ሆይ፣ የሚያደርጉትን ዐያውቁምና ይቅር በላቸው›› አለ። ጲላጦስ፣ ‹‹የአይሁድ ንጉሥ›› ብለው ምልክት እንዲጽፉና ከኢየሱስ ራስ በላይ በመስቀሉ ላይ እንዲያኖሩት አዘዘ።

Image

ወታደሮቹ በኢየሱስ ልብስ ላይ ዕጣ ተጣጣሉ። ይህንን ባደረጉበት ጊዜ፣ ‹‹ልብሶቼን ተከፋፈሉ፣ በእጀ ጠባቡም ላይ ዕጣ ተጣጣሉበት›› የሚለውን ትንቢት ፈጸሙ።

Image

ኢየሱስ በሁለት ወንበዴዎች መካከል ተሰቀለ። አንደኛው በኢየሱስ ላይ ዘበተበት፣ ሌላኛው ግን፣ ‹‹አንተ እግዚአብሔርን አትፈራም? እኛ ወንጀለኞች ነን፣ ይህ ሰው ግን ወንጀል የለበትም›› አለ። ከዚያም ኢየሱስን፣ ‹‹እባክህን በመንግሥትህ ዐስበኝ›› አለው። ኢየሱስ፣ ‹‹ዛሬ ከእኔ ጋር በገነት ትሆናለህ›› ብሎ መለሰለት።

Image

የአይሁድ መሪዎችና በሕዝቡ መካከል የነበሩ ሌሎች ሰዎች በኢየሱስ ላይ ዘበቱበት። ‹‹የእግዚአብሔር ልጅ ከሆንክ ከመስቀል ላይ ውረድና ራስህን አድን! ከዚያ በኋላ እናምንብሃለን›› አሉት።

Image

በዚያ ሰዓት ጊዜው ገና እኩለ ቀን ቢሆንም፣ በምድር ሁሉ ላይ ጨለማ ሆነ፡፡ ጨለማውም ከእኩለ ቀን እስከ ዘጠኝ ሰዓት ድረስ ቆየ፡፡

Image

ከዚያ በኋላ ኢየሱስ፣ ‹‹ተፈጸመ! አባት ሆይ፣ ነፍሴን በእጅህ እሰጣለሁ›› ብሎ ጮኸ፡፡ ከዚያም ራሱን አዘነበለና ነፍሱን አሳልፎ ሰጠ፡፡ በሞተ ጊዜ የምድር መንቀጥቀጥ ሆነ፣ በቤተ መቅደስ የነበረው ትልቁ መጋረጃም ከላይ እስከ ታች ለሁለት ተቀደደ፡፡

Image

ኢየሱስ በሞቱ በኩል ወደ እግዚአብሔር እንዲመጡ ለሰዎች ሁሉ መንገድ ከፈተላቸው፡፡ ኢየሱስን ይጠብቅ የነበረው ወታደር የሆነውን ሁሉ ባየ ጊዜ፣ ‹‹በእርግጥ ይህ ሰው ወንጀል የለበትም፡፡ የእግዚአብሔር ልጅ ነው›› አለ፡፡

Image

በዚያን ጊዜ ኢየሱስ መሲሕ መሆኑን ያመኑ ሁለት የአይሁድ መሪዎች፣ ዮሴፍና ኒቆዲሞስ የኢየሱስን ሥጋ እንዲሰጣቸው ጲላጦስን ለመኑት። ሥጋውን በጨርቅ ገነዙትና ከአለት በተወቀረ መቃብር አኖሩት። ከዚያም የመቃብሩን በር ትልቅ ድንጋይ አንከባልለው ዘጉት።

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከማቴዎስ 27፡27-61፤ ማርቆስ 15፡16-47፤ ሉቃስ 23፡26-56፤ ዮሐንስ 19፡17-42።

41. እግዚአብሔር ኢየሱስን ከሙታን አስነሣው

Image

ወታደሮቹ ኢየሱስን ከሰቀሉት በኋላ፣ የማያምኑ የአይሁድ መሪዎች ጲላጦስን፣ ‹‹ያ ውሸታም ኢየሱስ፣ ከሦስት ቀን በኋላ ከሙታን እነሣለሁ ብሎአል፡፡ ደቀ መዛሙርቱ ሥጋውን እንዳይሰርቁትና ከሙታን ተነሥቶአል እንዳይሉ መቃብሩ መጠበቅ አለበት›› አሉት፡፡

Image

ጲላጦስ፣ ‹‹ወታደሮችን ውሰዱና መቃብሩን በደንብ እንዲጠብቁ አድርጉ›› አለ። ስለዚህ በመቃብሩ መግቢያ ባለው ድንጋይ ላይ ማኅተም አደረጉና ሥጋውን ማንም እንዳይሰርቀው በዚያ ወታደሮችን አቆሙ።

Image

ኢየሱስ የተሰቀለበት ቀን ማግስት ሰንበት ነበረ። አይሁድ በዚያ ቀን ወደ መቃብር እንዲሄዱ አይፈቀድላቸውም ነበር። ስለዚህ ከሰንበት ቀን በኋላ በማለዳ ጥቂት ሴቶች ሥጋው ላይ ሽቱ ለማድረግ ወደ ኢየሱስ መቃብር ሊሄዱ ተዘጋጁ።

Image

በድንገትም ታላቅ የምድር መንቀጥቀጥ ሆነ። እንደ መብረቅ የሚያበራ መልአክ ከሰማይ ታየ። የመቃብሩን መግቢያ ከድኖ የነበረውን ድንጋይ አንከባለለና ተቀመጠበት። መቃብሩን ይጠብቁ የነበሩት ወታደሮች በፍርሃት እንደ ሞቱ ሰዎች ሆነው መሬት ላይ ወደቁ።

Image

ሴቶቹ ወደ መቃብሩ በደረሱ ጊዜ መልአኩ፣ ‹‹አትፍሩ! ኢየሱስ እዚህ የለም። ልክ እነሣለሁ ብሎ እንደ ተናገረው ከሞት ተነሥቶአል! መቃብሩን ተመልከቱ›› ብሎ ነገራቸው። ሴቶቹ ወደ መቃብሩ ውስጥ ተመለከቱና የኢየሱስን ሥጋ ያኖሩበትን ስፍራ ዐዩ። ሥጋው በዚያ አልነበረም።

Image

ከዚያም መልአኩ ለሴቶቹ፣ ‹‹ሂዱና ‹ኢየሱስ ከሙታን ተነሥቶአል፤ ቀድሞአችሁ ወደ ገሊላ ይሄዳል ብላችሁ ለደቀ መዛሙርቱ ንገሩአቸው››› ብሎ ነገራቸው።

Image

ሴቶቹ በፍርሃትና በታላቅ ደስታ ተሞልተው ነበር። የምሥራቹን ለደቀ መዛሙርቱ ለመንገር እየሮጡ ሄዱ።

Image

ሴቶቹ የምሥራቹን ለደቀ መዛሙርቱ ለመንገር በመሄድ ላይ እያሉ፣ ኢየሱስ ታያቸው፣ እነርሱም ሰገዱለት። ኢየሱስ፣ ‹‹አትፍሩ። ወደ ገሊላ እንዲሄዱ ለደቀ መዛሙርቴ ንገሩአቸው። በዚያ ያዩኛል›› አላቸው።

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከማቴዎስ 27፡62-28፡15፤ ማርቆስ 16፡1-11፤ ሉቃስ 24፡1-12፤ ዮሐንስ 20፡1-18።

42. ኢየሱስ ወደ ሰማይ ተመለሰ

Image

ኢየሱስ ከሙታን በተነሣበት ቀን ከደቀ መዛሙርቱ ሁለቱ በአቅራቢያው ወዳለች ከተማ እየሄዱ ነበር። ሲጓዙም፣ በኢየሱስ ላይ ስለ ደረሰበት ነገር ሲነጋገሩ ነበር። እርሱ መሲሕ እንደ ሆነ ተስፋ አድርገው ነበር፣ ነገር ግን እርሱ ተገደለ። አሁን ሴቶቹ እንደ ገና ሕያው ሆኖአል አሉ። ሁለቱ ደቀ መዛሙርት የቱን ማመን እንዳለባቸው ግራ ገብቷቸው ነበር።

Image

ኢየሱስ ወደ እነርሱ ቀረበና አብሮአቸው መጓዝ ጀመረ፣ እነርሱ ግን ዐላወቁትም ነበር። ስለ ምን ይነጋገሩ እንደ ነበረ ጠየቃቸው፣ እነርሱም ባለፉት ጥቂት ቀናት ውስጥ ኢየሱስን በተመለከተ ስለ ሆኑት አስገራሚ ነገሮች ሁሉ ነገሩት። የሚነጋገሩት በኢየሩሳሌም የሆነውን ነገር ከማያውቅ ከእንግዳ ሰው ጋር መስሏቸው ነበር።

Image

ከዚያም ኢየሱስ፣ ስለ መሲሑ የእግዚአብሔር ቃል የተናገረውን አብራራላቸው። መሲሑ መከራ እንደሚቀበልና እንደሚገደል፣ ነገር ግን በሦስተኛው ቀን እንደሚነሣ ነቢያት የተናገሩትን አስታወሳቸው። ሁለቱ ሰዎች ሊያድሩባት ወዳሰቡአት ከተማ ሲደርሱ፣ ጊዜው መሽቶ ነበር።

Image

ሁለቱ ሰዎች ከእነርሱ ጋር እንዲያድር ኢየሱስን ጋበዙት፣ እርሱም እሺ አላቸው። እራት ለመብላት በተዘጋጁ ጊዜ ኢየሱስ እንጀራን አንሥቶ እግዚአብሔርን አመሰገነ፣ ከዚያም ቈረሰው። ወዲያውኑ ኢየሱስ መሆኑን ዐወቁ። ነገር ግን በዚያን ጊዜ እርሱ ከዓይናቸው ተሰወረ።

Image

ሁለቱም ሰዎች፣ ‹‹ኢየሱስ ነው! የእግዚአብሔርን ቃል ሲያብራራልን ልባችን ሲቃጠልብን የነበረው ስለዚህ ነው!›› ተባባሉ፡፡ ወዲያውኑ፣ ወደ ኢየሩሳሌም ተመለሱ፡፡ በደረሱም ጊዜም ለደቀ መዛሙርቱ፣ ‹‹ኢየሱስ ሕያው ነው! ዐይተነዋል!›› ብለው ነገሩአቸው፡፡

Image

ደቀ መዛሙርቱ እየተነጋገሩ እያሉ፣ ኢየሱስ በድንገት በነበሩበት ክፍል በመካከላቸው ተገኘና፣ ‹‹ሰላም ለእናንተ ይሁን!›› አላቸው። ደቀ መዛሙርቱ መንፈስ መሰላቸው፣ ኢየሱስ ግን፣ ‹‹ለምን ትፈራላችሁ፤ ትጠራጠራላችሁም? እጆቼንና እግሮቼን እዩ። መናፍስት እንደ እኔ አካል የላቸውም›› አላቸው። መንፈስ አለመሆኑን ለማረጋገጥ የሚበላ ነገር እንዲሰጡት ጠየቃቸው። እነርሱም ከተጠበሰ ዓሣ አንድ ሰጡት፣ እርሱም በላ።

Image

ኢየሱስም፣ ‹‹በእግዚአብሔር ቃል ስለ እኔ የተጻፈው ሁሉ መፈጸም አለበት ብዬ ነግሬአችኋለሁ›› አለ። በዚያን ጊዜ የእግዚአብሔርን ቃል እንዲረዱ አእምሮአቸውን ከፈተላቸው። ‹‹መሲሑ መከራ እንደሚቀበል፣ እንደሚሞት፣ በሦስተኛው ቀን ከሙታን እንደሚነሣ ከረጅም ዘመን በፊት ተጽፎአል›› አላቸው።

Image

“ደግሞም የኃጢአታቸውን ይቅርታ ለማግኘት ሰዎች ሁሉ ንስሐ ይገቡ ዘንድ ደቀ መዛሙርቴ እንደሚያውጁ በመጻሕፍት ተጽፎአል። እነርሱ ከኢየሩሳሌም ጀምሮ ይህን ያደርጋሉ፣ ከዚያም በሁሉም ስፍራ ወዳሉ የሕዝብ ወገኖች ሁሉ ይሄዳሉ። እናንተ የእነዚህ ነገሮች ምስክሮች ናችሁ።” አላቸው።

Image

በቀጣዮቹ አርባ ቀናት ኢየሱስ ብዙ ጊዜ ለደቀ መዛሙርቱ ታያቸው። አንድ ጊዜ ከ500 ለሚበልጡ ሰዎች በአንድ ጊዜ ታይቷቸው ነበር! እርሱ ሕያው መሆኑን በብዙ መንገድ ለደቀ መዛሙርቱ አረጋገጠላቸው፣ ስለ እግዚአብሔር መንግሥትም አስተማራቸው።

Image

ኢየሱስ ለደቀ መዛሙርቱ እንዲህ አላቸው፣ ‹‹ሥልጣን ሁሉ በሰማይና በምድር ተሰጥቶኛል። ስለዚህ ሂዱ፣ የሕዝብ ወገኖችን ሁሉ በአብ፣ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም እያጠመቃችኋቸው፣ ያዘዝኋችሁንም ሁሉ እንዲፈጽሙ እያስተማራችኋቸው ደቀ መዛሙርቴ አድርጓቸው። እኔ ሁልጊዜ ከእናንተ ጋር ነኝ።››

Image

ኢየሱስ ከሙታን ከተነሣ ከአርባ ቀናት በኋላ ደቀ መዛሙርቱን፣ ‹‹መንፈስ ቅዱስ በእናንተ ላይ ወርዶ ኃይልን እስክትቀበሉ ድረስ በኢየሩሳሌም ቆዩ›› አላቸው፡፡ ከዚያ በኋላ ኢየሱስ ወደ ሰማይ ወጣ፣ ደመናም ከዓይናቸው ሰወረችው፡፡ ኢየሱስ ሁሉንም ነገር ሊገዛ በእግዚአብሔር ቀኝ ተቀመጠ፡፡

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከማቴዎስ 28፡16-20፤ ማርቆስ 16፡12-20፤ ሉቃስ 24፡13-53፤ ዮሐንስ 20፡19-23፤ የሐዋርያት ሥራ 1፡1-11።

43. ቤተ ክርስቲያን ተጀመረች

Image

ኢየሱስ ወደ ሰማይ ከተመለሰ በኋላ፣ ደቀ መዛሙርቱ ኢየሱስ እንዳዘዛቸው በኢየሩሳሌም ቆዩ። በዚያ የነበሩት አማኞች ያለ ማቋረጥ ለመጸለይ ይሰበሰቡ ነበር።

Image

አይሁድ በያመቱ ከፋሲካ በኋላ ባሉት 50 ቀናት ጴንጤቆስጤ ተብሎ የሚጠራን ልዩ በዓል ያከብሩ ነበር። ጴንጤቆስጤ አይሁድ የመከር በዓልን የሚያከብሩበት ቀን ነበር። አይሁድ የጴንጤቆስጤን በዓል በአንድነት ለማክበር ከመላው ዓለም ወደ ኢየሩሳሌም ይመጡ ነበር። በዚህ ዓመት፣ ኢየሱስ ወደ ሰማይ ከተመለሰ ከአንድ ሳምንት ገደማ በኋላ የጴንጤቆስጤ በዓል መጣ።

Image

አማኞቹ ሁሉ በአንድነት ተሰብስበው እያሉ፣ በድንገት የነበሩበት ቤት እንደ ብርቱ ነፋስ ባለው ድምፅ ተሞላ። ከዚያም በአማኞቹ ሁሉ ራስ ላይ የእሳት ነበልባል የሚመስል ነገር ታየ። ሁላቸውም በመንፈስ ቅዱስ ተሞሉና በሌሎች ቋንቋዎች መናገር ጀመሩ።

Image

በኢየሩሳሌም የነበሩት ሰዎች ድምፁን በሰሙ ጊዜ፣ የሆነውን ነገር ለማየት ብዙ ሰዎች መጡ። አማኞቹ የእግዚአብሔርን ድንቅ ሥራዎች ሲያውጁ ሰዎቹ በሰሙ ጊዜ እነዚህን ነገሮች በገዛ ራሳቸው ቋንቋ በመስማታቸው ተደነቁ።

Image

አንዳንዶቹ ሰዎች ደቀ መዛሙርቱ ሰክረዋል ብለው ወቀሱአቸው። ነገር ግን ጴጥሮስ ቆመና እንዲህ አላቸው፣ ‹‹እስቲ ስሙኝ! እነዚህ ሰዎች አልሰከሩም! እግዚአብሔር በነቢዩ ኢዮኤል ‹በመጨረሻው ቀን መንፈሴን አፈስሳለሁ!› ያለው ትንቢት በዚህ ተፈጽሟል።

Image

‹‹የእስራኤል ሰዎች ሆይ፣ እናንተ እንዳያችሁትና እንደምታውቁት ኢየሱስ በእግዚአብሔር ኃይል ብዙ ታላላቅ ምልክቶችንና ድንቆችን ያደረገ ሰው ነው። ነገር ግን እናንተ ሰቀላችሁት!››

Image

‹‹ኢየሱስ ቢሞትም እንኳ እግዚአብሔር ከሙታን አስነሣው። ይህም ‹ቅዱስህን በመቃብር መበስበስን ያይ ዘንድ አትተወውም› የሚለው ትንቢት ፍጻሜ ነው። እግዚአብሔር ኢየሱስን ሕያው አድርጎ ከሞት እንዳስነሣው እኛ ምስክሮች ነን።››

Image

‹‹ኢየሱስ አሁን በእግዚአብሔር አብ ቀኝ በክብር ተቀምጦአል። ደግሞም ኢየሱስ ልክ ተስፋ እንደ ሰጠው መንፈስ ቅዱስን ልኮአል። አሁን የምታዩአቸውንና የምትሰሙአቸውን ነገሮች ያደረገው መንፈስ ቅዱስ ነው ።

Image

‹‹ይህንን ኢየሱስን ሰቀላችሁት። ነገር ግን እግዚአብሔር ኢየሱስን ጌታና መሲሕ እንዳደረገው በእርግጥ እወቁ!››

Image

ጴጥሮስን ይሰሙ የነበሩት ሰዎች በተናገራቸው ነገሮች በእጅጉ ተነኩ። ስለዚህ ጴጥሮስንና ደቀ መዛሙርቱን፣ ‹‹ወንድሞች ሆይ፣ ምን እናድርግ?›› ብለው ጠየቁአቸው።

Image

ጴጥሮስ እንዲህ ብሎ መለሰላቸው፣ ‹‹እግዚአብሔር ኃጢአታችሁን ይቅር እንዲላችሁ እያንዳንዳችሁ ንስሐ ግቡና በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ተጠመቁ። ይህን ብታደርጉ እርሱ የመንፈስ ቅዱስን ስጦታ ደግሞ ይሰጣችኋል።››

Image

3000 የሚያህሉ ሰዎች ጴጥሮስ የተናገረውን አምነው የኢየሱስ ደቀ መዛሙርት ሆኑ። እነርሱ ተጠምቀው በኢየሩሳሌም ያለችው ቤተ ክርስቲያን ምእመናን ሆኑ።፡

Image

ደቀ መዛሙርቱ ያለ ማቋረጥ የሐዋርያትን ትምህርት ሰሙ፣ አብረው ጊዜ አሳለፉ፣ አብረው በሉ፣ አንዳቸው ለሌላኛው ጸለዩ። አብረው እግዚአብሔርን አመሰገኑ፣ የነበራቸውንም ነገር ሁሉ እርስ በርስ ተካፈሉ። ሁሉም ሰው ያከብራቸው ነበር። በየዕለቱም ሌሎች ብዙ ሰዎች አማኞች ሆኑ።

_የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከሐዋርያት ሥራ 2። _

44. ጴጥሮስና ዮሐንስ ይለምን የነበረውን ሰው ፈወሱ

Image

አንድ ቀን ጴጥሮስና ዮሐንስ ወደ ቤተ መቅደስ እየሄዱ ሳሉ፣ ወደ ቤተ መቅደሱ ደጃፍ እንደ ቀረቡ፣ ገንዘብ ይለምን የነበረ ሽባ ሰው ዐዩ።

Image

ጴጥሮስ ሽባውን ተመለከተውና፣ ‹‹የምሰጥህ ምንም ገንዘብ የለኝም። ያለኝን ግንእሰጥሃለሁ። በኢየሱስ ስም ተነሣና ተመላለስ!›› አለው።

Image

ወዲያውኑ እግዚአብሔር ሽባውን ሰው ፈወሰው፣ እርሱም መራመድና መዝለል፣ እግዚአብሔርንም ማመስገን ጀመረ። በቤተ መቅደሱ አጥር ግቢ የነበሩት ሰዎችም ተደነቁ።

Image

ሕዝቡም የተፈወሰውን ሰው ለማየት ፈጥነው ተሰበሰቡ፡፡ ጴጥሮስ እንዲህ አላቸው፣ ‹‹ይህ ሰው ስለ ተፈወሰ ለምን ትደነቃላችሁ? በገዛ ኃይላችን ወይም በበጎነታችን አልፈወስነውም፡፡ ይህንን ሰው የፈወሰው የኢየሱስ ኃይልና ኢየሱስ የሚሰጠው እምነት ነው፡፡››

Image

‹‹ኢየሱስን እንዲገድለው ለሮማው ገዥ የነገራችሁት እናንተ ናችሁ። የሕይወትን ራስ ገደላችሁት፣ እግዚአብሔር ግን ከሙታን አስነሣው። ታደርጉት የነበረውን ነገር ባትረዱም እንኳ፣ መሲሑ መከራ እንደሚቀበልና እንደሚሞት የተነገሩትን ትንቢቶች ለመፈጸም እግዚአብሔር በድርጊቶቻችሁ ተጠቀመ። ስለዚህ ኃጢአታችሁ ይታጠብላችሁ ዘንድ አሁን ንስሐ ግቡና ወደ እግዚአብሔር ተመለሱ።››

Image

የቤተ መቅደሱ መሪዎች ጴጥሮስና ዮሐንስ ይናገሩት በነበረው ነገር በጣም ተበሳጩ። ስለዚህ ያዙአቸውና እስር ቤት አስገቡአቸው። ነገር ግን ብዙ ሰዎች የጴጥሮስን መልእክት አመኑ፣ በኢየሱስ ያመኑት ሰዎች ቊጥርም ወደ 5,000 ገደማ ዐደገ።

Image

በማግስቱ፣ የአይሁድ መሪዎች ጴጥሮስንና ዮሐንስን ወደ ሊቀ ካህናቱና ወደ ሌሎቹ የሃይማኖት መሪዎች አመጡአቸው። ጴጥሮስንና ዮሐንስን፣ ‹‹ይህንን ሽባ ሰው በምን ኃይል ፈወሳችሁት?›› ብለው ጠየቁአቸው።

Image

ጴጥሮስ እንዲህ ብሎ መለሰላቸው፣ ‹‹ይህ ሰው በመሲሑ በኢየሱስ ኃይል ተፈውሶ በፊታችሁ ቆሞአል። እናንተ ኢየሱስን ሰቀላችሁት፣ እግዚአብሔር ግን እንደ ገና ሕያው አድርጎ ከሙታን አስነሣው! እናንተ አልተቀበላችሁትም፣ ነገር ግን በኢየሱስ ኃይል ካልሆነ በቀር ሌላ የመዳን መንገድ የለም!››

Image

ጴጥሮስና ዮሐንስ በጣም በድፍረት በመናገራቸው እነዚህ መሪዎች ደነገጡ፣ ምክንያቱም እነዚህ ሰዎች ያልተማሩ ተራ ሰዎች መሆናቸውን አይተው ነበር። ነገር ግን እነዚህ ሰዎች ከኢየሱስ ጋር እንደ ነበሩ አስታወሱ። ጴጥሮስንና ዮሐንስን ካስጠነቀቁአቸው በኋላ፣ እንዲሄዱ አሰናበቱአቸው።

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከሐዋርያት ሥራ 3፡1-4፡22።

45. እስጢፋኖስ እና ፊሊጶስ

Image

በጥንትዋ ቤተ ክርስቲያን ከነበሩት መሪዎች አንዱ እስጢፋኖስ ተብሎ የሚጠራ ሰው ነበር። እርሱ መልካም ስም ያለውና መንፈስ ቅዱስና ጥበብ የሞላበት ሰው ነበር። እስጢፋኖስ ብዙ ተአምራትን ያደረገና ሰዎች በኢየሱስ እንዲያምኑ በደንብ አስረድቶ ያሳምናቸው ነበር።

Image

አንድ ቀን እስጢፋኖስ ስለ ኢየሱስ በሚያስተምርበት ጊዜ፣ በኢየሱስ ያላመኑ አንዳንድ አይሁዶች ከእስጢፋኖስ ጋር መከራከር ጀመሩ። በጣም ተቈጡና ስለ እስጢፋኖስ ለሃይማኖት መሪዎች ዋሽተው ተናገሩ። ‹‹ስለ ሙሴና ስለ እግዚአብሔር ክፉ ነገሮችን ሲናገር ሰምተነዋል!›› አሉ። ስለዚህ የሃይማኖት መሪዎቹ እስጢፋኖስን ያዙትና ወደ ሊቀ ካህናቱና ወደ ሌሎቹ የአይሁድ መሪዎች አምጥተው ሌሎች ተጨማሪ የሐሰት ምስክሮች ስለ እስጢፋኖስ ዋሽተው እንዲመሰክሩ አደረጉ።

Image

ሊቀ ካህናቱ እስጢፋኖስን፣ ‹‹እነዚህ ነገሮች እውነት ናቸውን?›› ብሎ ጠየቀው፡፡ እስጢፋኖስ ከአብርሃም ዘመን ጀምሮ እስከ ኢየሱስ ዘመን ድረስ እግዚአብሔር ስላደረጋቸው ብዙ ታላላቅ ነገሮች፣ እንዲሁም የእግዚአብሔር ሕዝብ በተከታታይ በእርሱ ላይ ስለ ማመፃቸው በማስታወስ መልስ ሰጠ፡፡ ከዚያም እንዲህ አለ፣ ‹‹እናንተ አንገተ ደንዳኖችና ዓመፀኞች ልክ ቅድመ አያቶቻችሁ እግዚአብሔርን እንደ ተቃወሙትና ነቢያቱን እንደ ገደሉ ሁልጊዜ መንፈስ ቅዱስን ትቃወማላችሁ፡፡ እናንተ ግን ከእነርሱ ይልቅ የባሰ ክፉ ነገር አድርጋችኋል፡፡ መሲሑን ገድላችኋል!››

Image

የሃይማኖት መሪዎቹ ይህንን በሰሙ ጊዜ፣ በጣም ተናደው ጆሮአቸውን ደፈኑና ከፍ ባለ ድምፅ ጮኹ። እስጢፋኖስን ከከተማይቱ ውጪ ጐተቱትና ሊገድሉት በድንጋይ ወገሩት።

Image

እስጢፋኖስ በመሞት ላይ እያለ፣ ‹‹ኢየሱስ ሆይ፣ ነፍሴን ተቀበላት›› ብሎ ጮኸ። ከዚያም በጉልበቱ ተንበረከከና፣ ‹‹ጌታ ሆይ፣ ይህንን ኃጢአት አትቊጠርባቸው›› ብሎ እንደ ገና ጮኸ። ከዚያ በኋላ ሞተ።

Image

ሳውል የተባለ አንድ ወጣት እስጢፋኖስን ከሚገድሉት ሰዎች ጋር ተስማምቶ በእርሱ ላይ ድንጋይ በሚወረውሩበት ጊዜ ልብሳቸውን ይጠብቅ ነበር። በዚያን ዕለት በኢየሩሳሌም የነበሩ ብዙ ሰዎች የኢየሱስን ተከታዮች ማሳደድ ጀመሩ፣ ስለዚህ አማኞቹ ወደ ሌሎች ስፍራዎች ሸሹ። ነገር ግን ስደቱ ቢኖርም እንኳ፣ በሄዱበት ስፍራ ሁሉ ስለ ኢየሱስ ሰበኩ።

Image

ፊልጶስ የተባለ የኢየሱስ ደቀ መዝሙር በስደቱ ጊዜ ከኢየሩሳሌም ከሸሹት አማኞች አንዱ ነበር። ወደ ሰማርያ ሄዶ ስለ ኢየሱስ ሰበከና ብዙ ሰዎች ዳኑ። ከዚያ በኋላ አንድ ቀን ከእግዚአብሔር የተላከ መልአክ በምድረ በዳ ወዳለ አንድ መንገድ እንዲሄድ ለፊልጶስ ነገረው። ፊልጶስ በመንገዱ በመሄድ ላይ እያለ አንድ ትልቅ ኢትዮጵያዊ ባለ ሥልጣን በሰረገላው ሲሄድ ዐየ። ወደዚህ ሰው ሄዶ እንዲያነጋግረው መንፈስ ቅዱስ ለፊልጶስ ነገረው።

Image

ፊልጶስ ወደ ሰረገለው በቀረበ ጊዜ፣ ኢትዮጵያዊው ነቢዩ ኢሳይያስ ከጻፈው ውስጥ አንዱን ክፍል ሲያነብ ሰማ፡፡ ሰውዬው እንዲህ ብሎ ሲያነብ ነበር፣ ‹‹እንደ በግ ወደ መታረድ ተነዳ፣ የበግ ጠቦትም በሸላቹ ፊት ዝም እንደሚል እንዲሁ አፉን አልከፈተም፡፡ በፍርድ ተወሰደ፣ አላከበሩትምም፡፡ ከሕያዋን ምድር አስወገዱት፡፡››

Image

ፊልጶስ ኢትዮጵያዊውን፣ ‹‹የምታነበውን ታስተውለዋለህን?›› ብሎ ጠየቀው። ኢትዮጵያዊውም፣ ‹‹አይደለም። የሚያስረዳኝ ሰው ሳይኖር እንዴት ልረዳ እችላለሁ። እባክህን ናና ከጐኔ ተቀመጥ። ኢሳይያስ የጻፈው ስለ ራሱ ነውን ወይስ ስለ ሌላ ሰው?›› ብሎ መለሰ።

Image

ኢሳይያስ የጻፈው ስለ ኢየሱስ መሆኑን ፊልጶስ ለኢትዮጵያዊው አብራራለት። ደግሞም ፊልጶስ ስለ ኢየሱስ የሚናገረውን የምሥራች ሲያስረዳው ሌሎች የእግዚአብሔር ቃል ክፍሎችን ተጠቀመ።

Image

ፊልጶስና ኢትዮጵያዊው ሲጓዝ ሳለ፣ ውሃ ወዳለበት ስፍራ ደረሱ፡፡ ኢትዮጵያዊውም፣ ‹‹እነሆ፣ በዚያ ቦታ ውሃ አለ! ልጠመቅን?›› አለ፡፡ ለነጂውም ሰረገላውን እንዲያቆመው ነገረው፡፡

Image

ስለዚህ ወደ ውሃው ወረዱ፣ ፊልጶስም ኢትዮጵያዊውን አጠመቀው። ከውሃው ከወጡ በኋላ መንፈስ ቅደስ በድንገት ፊልጶስን ወደ ሌላ ስፍራ ወሰደው፤ ስለ ኢየሱስ ለሰዎች መናገሩንም ቀጠለ።

Image

ኢትዮጵያዊው ኢየሱስን በማወቁ እየተደሰተ ወደ አገሩ ለመመለስ ጕዞውን ቀጠለ።

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከሐዋርያት ሥራ 6፡8-8፡5፤ 8፡26-40።

46. ጳውሎስ ክርስቲያን ሆነ

Image

ሳውል እስጢፋኖስ ሲገደል የገዳዮችን ልብስ ይጠብቅ የነበረ ወጣት ነው። እርሱ በኢየሱስ የማያምን ነበር፣ ስለዚህም አማኞችን ያሳድድ ነበር። ወንዶችንና ሴቶችን እየያዘ ወደ እስር ቤት ለመጨመር በኢየሩሳሌም ከቤት ወደ ቤት ይሄድ ነበር። ሊቀ ካህናቱ በዚያ ያሉትን ክርስቲያኖች ይይዝና ወደ ኢየሩሳሌም ያመጣቸው ዘንድ ወደ ደማስቆ ከተማ እንዲሄድ ለሳውል ፈቃድ ሰጡት።

Image

ሳውል ወደ ደማስቆ በመጓዝ ላይ እያለ፣ ከሰማይ ብሩህ ብርሃን በዙሪያው ሁሉ አበራ፣ እርሱም መሬት ላይ ወደቀ። ከዚያም፣ ‹‹ሳውል! ሳውል! ስለ ምን ታሳድደኛለህ?›› የሚል ድምፅ ሰማ። ሳውል፣ ‹‹ጌታ ሆይ፣ አንተ ማን ነህ?›› ብሎ ጠየቀ። ኢየሱስም፣ ‹‹የምታሳድደኝ እኔ ኢየሱስ ነኝ›› ብሎ መለሰለት።

Image

ሳውልም ከወደቀበት በተነሣ ጊዜ፣ ማየት ተሳነው። ወዳጆቹ ወደ ደማስቆ እየመሩ ወሰዱት። ሳውል ለሦስት ቀናት ምንም አልበላም ወይም አልጠጣም።

Image

በደማስቆ ሐናንያ የተባለ አንድ ደቀ መዝሙር ነበረ። እግዚአብሔር ለሐናንያ፣ ‹‹ሳውል ወዳለበት ቤት ሂድ። እንደ ገና ያይ ዘንድ እጅህን ጫንበት›› አለው። ሐናንያ ግን፣ ‹‹ጌታ ሆይ፣ ይህ ሰው አማኞችን እንዴት እንዳሳደደ ሰምቼአለሁ›› አለ። እግዚአብሔር፣ ‹‹ሂድ! ለአይሁዶችና ለአሕዛብ ስሜን እንዲያውጅ መርጬዋለሁ። ስለ ስሜ ብዙ መከራ ይቀበላል›› አለው።

Image

ስለዚህ ሐናንያ ወደ ሳውል ሄደ። እጆቹን ጫነበት፣ እንዲህም አለ፣ ‹‹ወደዚህ ስትመጣ በመንገድ ላይ የታየህ ኢየሱስ፣ እንደ ገና ታይና በመንፈስ ቅዱስ ትሞላ ዘንድ ወዳንተ ላከኝ።›› ሳውል ወዲያውኑ ማየት ቻለ፣ ሐናንያም አጠመቀው። ከዚያ በኋላ ሳውል ምግብ በላ፣ በረታም።

Image

ሳውል ወዲያውኑ፣ ‹‹ኢየሱስ የእግዚአብሔር ልጅ ነው!›› በማለት በደማስቆ ለነበሩ አይሁድ መስበክ ጀመረ። አይሁዶች አማኞችን ለማጥፋት የሞከረው ሰው አሁን ደግሞ በኢየሱስ በማመኑ ተደነቁ! ሳውል ኢየሱስ መሲሕ መሆኑን ለአይሁዶች አረጋገጠላቸው።

Image

ከብዙ ቀናት በኋላ አይሁዶች ሳውልን ለመግደል ዐቀዱ። ይገድሉት ዘንድ በከተማይቱ በሮች የሚጠባበቁትን ሰዎች አቆሙ። ነገር ግን ሳውል ስለ ዕቅዱ ሰማ፣ ወዳጆቹም እንዲያመልጥ ረዱት። አንድ ሌሊት በቅርጫት አድርገው በከተማዪቱ ቅጥር አወረዱት። ሳውል ከደማስቆ ካመለጠ በኋላ ስለ ኢየሱሰ መስበኩን ቀጠለ።

Image

ሳውል ከደቀ መዛሙርቱ ጋር ለመገናኘት ወደ ኢየሩሳሌም ሄደ፣ እነርሱ ግን ፈሩት። በዚያን ጊዜ በርናባስ የተባለ አማኝ ሳውልን ወደ ሐዋርያቱ ወሰደውና ሳውል በደማስቆ እንዴት በድፍረት እንደ ሰበከ ነገራቸው። ከዚያ በኋላ ደቀ መዛሙርቱ ሳውልን ተቀበሉት።

Image

በኢየሩሳሌም ከነበረው ስደት የሸሹ አንዳንድ አማኞች ወደ አንጾኪያ ድረስ ርቀው ሄዱና ስለ ኢየሱስ ሰበኩ፡፡ በአንጾኪያ የነበሩት ብዙዎቹ ሰዎች አይሁዶች አልነበሩም፣ ነገር ግን ለመጀመሪያ ጊዜ ብዙዎቻቸው በኢየሱስ አመኑ፡፡ በርናባስና ሳውል እነዚህን ዐዳዲስ አማኞች በተጨማሪ ስለ ኢየሱስ ሊያስተምሯቸውና ቤተ ክርስቲያንን ሊያጠናክሩ ወደዚያ ሄዱ፡፡ በኢየሱስ ያመኑት ሰዎች ለመጀመሪያ ጊዜ በአንጾኪያ ‹‹ክርስቲያኖች›› ተባሉ፡፡

Image

አንድ ቀን በአንጾኪያ የነበሩ ክርስቲያኖች እየጾሙና እየጸለዩ እያሉ መንፈስ ቅዱስ፣ ‹‹ለጠራኋቸው ሥራ በርናባስንና ሳውልን ለዩልኝ›› አላቸው። ስለዚህ የአንጾኪያ ቤተ ክርስቲያን አገልጋዮች ለበርናባስና ለሳውል ጸለዩላቸው፣ እጆቻቸውንም ጫኑባቸው። ከዚያም በሌሎች ብዙ ቦታዎች ስለ ኢየሱስ የምሥራች እንዲሰብኩ ላኩአቸው። በርባናስና ሳውል ከተለያዩ የሕዝብ ወገኖች የሆኑ ሰዎችን አስተማሩ፣ ብዙ ሰዎችም በኢየሱስ አመኑ።

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከሐዋርያት ሥራ 8፡3፤ 9፡1-31፤ 11፡19-26፤ 13፡1-3።

47. ጳውሎስና ሲላስ በፊልጵስዩስ

Image

ሳውል በሮማ የንጉሠ ነገሥት ግዛት ሁሉ በሚጓዝበት ጊዜ፣ ‹‹ጳውሎስ›› የሚለውን ሮማዊ ስሙን ይጠቀም ጀመር። አንድ ቀን ጳውሎስና ጓደኛው ሲላስ ስለ ኢየሱስ የምሥራች ሊያውጁ ወደ ፊልጵስዩስ ከተማ ሄዱ። ሰዎች ሊጸልዩ ወደ ተሰበሰቡበት ከከተማይቱ ውጭ በወንዙ አጠገብ ወዳለ ስፍራ ሄዱ። በዚያ ነጋዴ የነበረች ልድያ የሚሉአት አንዲት ሴት አገኙ። እርስዋ እግዚአብሔርን የምትወድና የምታመልክ ሴት ነበረች።

Image

ስለ ኢየሱስ የተነገረውን መልእክት እንድታምን እግዚአብሔር የልድያን ልብ ከፈተላት፤ እርስዋና ቤተ ሰብዋ ተጠመቁ፣ በቤትዋ እንዲቀመጡም ጳውሎስንና ሲላስን ጋበዘቻቸው፣ ስለዚህ እነርሱ ከእርስዋና ከቤተ ሰብዋ ጋር ለተወሰነ ጊዜ ቆዩ።

Image

ጳውሎስና ሲላስ ብዙ ጊዜ በጸሎት ስፍራ ከሰዎች ጋር ይገናኙ ነበር። በየዕለቱ ወደዚያ ሲሄዱ ጋኔን የያዛት አንዲት የቤት ሠራተኛ ትከተላቸው ነበር። እርሷም በዚህ ጋኔን አማካይነት ስለ መጪው ጊዜ ለሰዎች ትተነብይላቸው ነበር፣ ስለዚህ በጥንቈላ ለጌቶችዋ ብዙ ገንዘብ ታስገኝ ነበር።

Image

የቤት ሠራተኛይቱም እነርሱ ሲዘዋወሩ እየተከተለቻቸው፣ ‹‹እነዚህ ሰዎች የልዑል እግዚአብሔር አገልጋዮች ናቸው። ለእናንተ የመዳንን መንገድ ይነግሩአችኋል!›› በማለት መጮህዋን ቀጠለች። ይህንን ደጋግማ ስለ አደረገች ጳውሎስ ተበሳጨ።

Image

በመጨረሻም አንድ ቀን ሠራተኛይቱ መጮኽ በጀመረች ጊዜ ጳውሎስ ወደ እርስዋ ዘወር አለና በእርስዋ የነበረውን ጋኔን፣ ‹‹በኢየሱስ ስም ከእርስዋ ውጣ›› አለው፡፡ ወዲያውኑ ጋኔኑ ለቀቃት፡፡

Image

በዚህ የባሪያዪቱ ጌቶች በጣም ተቈጡ! ያለ ጋኔኑ ባሪያዪቱ ልጅ ስለ ሰዎች መጪ ጊዜ መናገር እንደማትችል ዐወቁ። ይህም ማለት ለሰዎች የወደፊቱን ነገር ልትነግራቸው ስለማትችል ለጌቶችዋ ገንዘብ አይከፍሉም ማለት ነው።

Image

ስለዚህ የባሪያዪቱ ጌቶች ጳውሎስንና ሲላስን ወደ ሮማ ባለ ሥልጣናት ወሰዱአቸው፣ እነርሱም ደብድበው ወደ እስር ቤት ጣሉአቸው።

Image

የሮማ ወታደሮችም ጳውሎስንና ሲላስን በእስር ቤት ውስጠኛ ክፍል አሰሩአቸው፤ እግሮቻቸውንም ከግንድ ጋር አሰሩአቸው፡፡ ሆኖም ግን እኩለ ሌሊት ላይ ለእግዚአብሔር የምስጋና መዝሙር ዘመሩ፡፡

Image

በድንገት ኃይለኛ የመሬት መንቀጥቀጥ ሆነ! የእስር ቤቱ በሮች ሁሉ ወለል ብለው ተከፈቱ፣ የእስረኞቹ ሁሉ ሰንሰለቶችም ረገፉ።

Image

የእስር ቤቱ ጠባቂ ከእንቅልፉ ነቃ፣ የእስር ቤቱ በሮች ሁሉ መከፈታቸውን ባየ ጊዜ በጣም ደነገጠ! እስረኞቹ ሁሉ ያመለጡ መሰለው፣ ስለዚህ ራሱን ለመግደል ዐሰበ። (እስረኞቹ እንዲያመልጡ ካደረገ የሮማ ባለ ሥልጣናት እንደሚገድሉት ያውቅ ነበር።) ነገር ግን ጳውሎስ ዐየውና፣ ‹‹ተው! ራስህን አትጕዳ። እኛ ሁላችንም እዚህ አለን›› ብሎ ጮኸ።

Image

የእስር ቤቱ ጠባቂ ወደ ጳውሎስና ሲላስ እየተንቀጠቀጠ መጣና፣ ‹‹እድን ዘንድ ምን ላድርግ?›› ብሎ ጠየቀ። ጳውሎስ፣ ‹‹በጌታ በኢየሱስ እመን፣ አንተና ቤተ ሰዎችህ ትድናላችሁ›› ብሎ መለሰለት። ከዚያም የእስር ቤት ጠባቂው ጳውሎስንና ሲላስን ወደ ቤቱ ወሰዳቸውና ቊስላቸውን አጠበላቸው። ጳውሎስ በቤቱ ለነበሩት ሁሉ ስለ ኢየሱስ የምሥራች ሰበከላቸው።

Image

የእስር ቤት ጠባቂውና መላው ቤተ ሰቡ በኢየሱስ አምነው ተጠመቁ። ከዚያም የእስር ቤት ጠባቂው ለጳውሎስና ለሲላስ ምግብ አቀረበላቸውና በአንድነት ደስ አላቸው።

Image

በማግስቱ የከተማው መሪዎች ጳውሎስንና ሲላስን ከእስር ቤት ፈቱአቸውና ከፊልጵስዩስ እንዲሄዱ ጠየቁአቸው፡፡ ጳውሎስና ሲላስ ልድያንና አንዳንድ ሌሎች ወዳጆችን ጐበኙና ከተማይቱን ለቀው ሄዱ፡፡ የኢየሱስ የምሥራች ቃል መስፋፋቱን ቀጠለ፤ ቤተ ክርስቲያንም ማደግዋን ቀጠለች፡፡

Image

ጳውሎስና ሌሎች ክርስቲያን መሪዎች ስለ ኢየሱስ የምሥራች እየሰበኩና እያስተማሩ ወደ ብዙ ከተሞች ተጓዙ። ደግሞም በአብያተ ክርስቲያናቱ ላሉ አማኞች ሊያበረታቱአቸውና ሊያስተምሩአቸው ብዙ መልእክቶችን ጻፉላቸው። ከእነዚህ መልእክቶች አንዳንዶቹ በመጽሐፍ ቅዱስ ያሉት መጻሕፍት ሆኑ።

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከሐዋርያት ሥራ 16፡11-40።

48. ኢየሱስ የተስፋው መሲሕ

Image

እግዚአብሔር ዓለምን በፈጠረ ጊዜ ሁሉም ነገር ፍጹም ነበረ። ኃጢአት አልነበረም። አዳምና ሔዋን እርስ በርሳቸው ይዋደዱ ነበር፣ እግዚአብሔርንም ይወዱት ነበር። በሽታ ወይም ሞት አልነበረም። እግዚአብሔር የፈለገው ዓለም እንደዚህ እንድትሆን ነበር።

Image

ሰይጣን በገነት ሔዋንን ያስት ዘንድ በእባቡ በኩል ተናገረ። በዚያን ጊዜ እርስዋና አዳም በእግዚአብሔር ላይ ኃጢአት ሠሩ። እነርሱ ኃጢአት በመሥራታቸው ምክንያት በምድር ያለ ሰው ሁሉ ይታመማል፤ ይሞታልም።

Image

አዳምና ሔዋን ኃጢአት በመሥራታቸው ምክንያት ከዚህም የበለጠ ክፉ ነገር ሆነ። እነርሱ የእግዚአብሔር ጠላቶች ሆኑ። ከዚህ የተነሣ ከዚያን ጊዜ አንሥቶ ሁሉም ሰው በኃጢአተኛ ባሕርይ ተወልዶአል፤ ደግሞም የእግዚአብሔር ጠላት ሆኖአል። በእግዚአብሔርና በሰዎች መካከል የነበረው ግንኙነት በኃጢአት ምክንያት ተቋረጠ። ነገር ግን እግዚአብሔር ያንን ግንኙነት የመመለስ ዕቅድ ነበረው።

Image

ከሔዋን ዝርያዎች አንዱ የሰይጣንን ራስ እንደሚቀጠቅጥ፣ ሰይጣንም ሰኰናውን እንዲያቈስል እግዚአብሔር ተስፋ ሰጠ። ይህም ሰይጣን መሲሑን ይገድላል፣ ነገር ግን እግዚአብሔር እንደ ገና ከሞት ያስነሣዋል ማለት ነው፣ ከዚያም መሲሑ የሰይጣንን ራስ ለዘላለም ይቀጠቅጠዋል። ከብዙ ዓመታት በኋላ እግዚአብሔር መሲሑ ኢየሱስ መሆኑን ገለጠ።

Image

እግዚአብሔር ምድርን ሁሉ በጥፋት ውሃ ባጠፋ ጊዜ፣ በእርሱ ያመኑትን ሰዎች ለማዳን መርከብ አቀረበ። ልክ እንደዚሁ ሰው ሁሉ በኃጢአቱ ምክንያት መጥፋት ይገባው ነበር፣ ነገር ግን እግዚአብሔር በእርሱ የሚያምኑትን ሁሉ ለማዳን ኢየሱስን ሰጠ።

Image

ለብዙ መቶ ዓመታት ካህናት ሰዎች ለኃጢአታቸው የሚገባቸውን ቅጣት መቀበል እንደሚገባቸው ለማሳየት ስለ ሕዝቡ ኃጢአት ያለ ማቋረጥ ለእግዚአብሔር መሥዋዕት አቀረቡ። ነገር ግን እነዚያ መሥዋዕቶች ኃጢአታቸውን ሊያስወግዱ አልቻሉም። ኢየሱስ ታላቁ ሊቀ ካህናት ነው። ከሌሎች ካህናት በተለየ ሁኔታ በዓለም ላይ ያሉ ሰዎችን ሁሉ ኃጢአት ማስወገድ የሚችል ብቸኛ መሥዋዕት አድርጎ ራሱን አቀረበ። ኢየሱስ ማንኛውም ሰው የሠራውን የእያንዳንዱን ኃጢአት ቅጣት ስለ ወሰደ ፍጹም ሊቀ ካህናት ነው።

Image

እግዚአብሔር ለአብርሃም፣ ‹‹የምድር ሕዝብ ወገኖች ሁሉ በአንተ ዘር ይባረካሉ›› ብሎ ነገረው። ኢየሱስ የአብርሃም ዘር ነው። በእርሱ በኩል የሕዝብ ወገኖች ሁሉ ተባርከዋል፣ ምክንያቱም በኢየሱስ የሚያምን ሰው ሁሉ ከኃጢአት ድኖአል፣ እንዲሁም የአብርሃም መንፈሳዊ ልጅ ይሆናል።

Image

ልጁን ይስሐቅን መሥዋዕት አድርጎ እንዲያቀርብ እግዚአብሔር ለአብርሃም በነገረው ጊዜ፣ እግዚአብሔር በልጁ በይስሐቅ ፈንታ የመሥዋዕት በግ አቀረበ። እኛ ሁላችንም በኃጢአታችን መሞት ይገባናል! ነገር ግን እግዚአብሔር መሥዋዕት ሆኖ በእኛ ቦታ እንዲሞት የእግዚአብሔር በግ የሆነውን ኢየሱስን ሰጠ።

Image

እግዚአብሔር በግብፅ ላይ የመጨረሻውን መቅሠፍት በላከ ጊዜ እንከን የሌለበት ጠቦት እንዲያርዱና ደሙን በበሩ መቃንና ጉበን ላይ እንዲረጩት ለእስራኤላውያን ቤተ ሰቦች ሁሉ ተናገረ። እግዚአብሔርም ደሙን ባየ ጊዜ ቤቶቹን አልፎ ሄደ፤ በኵር ልጆቻቸውንም አልገደለም። ይህ ታሪካዊ ድርጊት ፋሲካ ተብሎአል።

Image

ኢየሱስ የፋሲካ በጋችን ነው። እርሱ ፍጹምና ምንም ኃጢአት የሌለብት የእግዚእብሔር በግ ነው፤ በፋሲካ በዓል ጊዜም ተገደለ። ማንኛውም ሰው በኢየሱስ በሚያምንበት ጊዜ፣ የኢየሱስ ደም ለዚያ ሰው ኃጢአት ክፍያ ነው፣ የእግዚአብሔር ቅጣትም ከዚያ ሰው ላይ ያልፋል።

Image

እግዚአብሔር የተመረጡ ሕዝቡ ከነበሩት ከእስራኤላውያን ጋር ቃል ኪዳን አደረገ። ነገር ግን አሁን እግዚአብሔር ለሁሉም ሰው የሚሆን ዐዲስ ቃል ኪዳን አድርጎአል። በዚህ ዐዲስ ቃል ኪዳን ምክንያት ከማንም ሕዝብ ወገን የሆነ ማንኛውም ሰው በኢየሱስ በማመን የእግዚአብሔር ሕዝብ ወገን መሆን ይችላል።

Image

ሙሴ የእግዚአብሔርን ቃል ያወጀ ታላቅ ነቢይ ነበረ። ኢየሱስ ግን ከሁሉም የላቀ ነቢይ ነው። እርሱ አምላክ ነው፣ ስለዚህ እርሱ ያደረገውና የተናገረው ነገር ሁሉ የእግዚአብሔር ሥራና የእግዚአብሔር ቃል ነው።

Image

እግዚአብሔር ለንጉሥ ዳዊት ከትውልዱ አንዱ ንጉሥ ሆኖ በእግዚአብሔር ሕዝብ ላይ ለዘላለም እንደሚገዛ ተስፋ ሰጠው። ኢየሱስ የእግዚአብሔር ልጅና መሲሑ ስለሆነ፣ ለዘላለም መግዛት የሚችል ልዩ የዳዊት ዘር እርሱ ነው።

Image

ዳዊት የእስራኤል ንጉሥ ነበር፣ ኢየሱስ ግን የፍጥረት ዓለም ሁሉ ንጉሥ ነው! ተመልሶ ይመጣና በፍትሕና በሰላም መንግሥቱን ለዘላለም ይገዛል።

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከዘፍጥረት 1-3፤ 6፤ 14፤ 22፤ ዘጸአት 12፣ 20፤ 2ኛ ሳሙኤል 7፤ ዕብራውያን 3፡1-6፤ 4፡14-5፡10፤ 7፡1-8፡13፤ 9፡11-10፡18፤ ራእይ 21።

49. ዐዲሱ የእግዚአብሔር ቃል ኪዳን

Image

አንድ መልአክ ማርያም ለተባለች ድንግል የእግዚአብሔርን ልጅ እንደምትወልድ ነገራት፡፡ ስለዚህ እርስዋ ገና ድንግል እያለች መንፈስ ቅዱስ ጸለለላትና አረገዘች። ወንድ ልጅም ወለደችና ስሙን ኢየሱስ ብላ ጠራችው፡፡ ስለሆነም ኢየሱስ አምላክም ሰውም ሆነ፡፡

Image

ኢየሱስ የእግዚብሔር ልጅ መሆኑን የሚያረጋግጡ ብዙ ተአምራትን አደረገ፡፡ በውሃ ላይ ተራመደ፣ ማዕበልን ጸጥ አደረገ፣ ብዙ በሽተኞችን ፈወሰ፣ አጋንንትን አወጣ፣ ሙታንን ሕያው አድርጎ አስነሣ፣ እንዲሁም አምስት እንጀራና ሁለት ትንንሽ ዓሣ ከ5,000 ለበለጡ ሰዎች እንዲበቃ አደረገ፡፡

Image

ደግሞም ኢየሱስ ታላቅ መምህር ነው፣ የእግዚአብሔር ልጅ ስለሆነም በሥልጣን ተናገረ፡፡ ራሳችሁን እንደምትወዱ ሌሎች ሰዎችንም ውደዱ ብሎ አስተማረ፡፡

Image

ደግደግሞም እርሱ ሀብታችሁን ጨምሮ ማንኛውንም ነገር ከምትወዱት አብልጣችሁ እግዚአብሔርን መውደድ አለባችሁ ብሎ አስተማረ፡፡

Image

ኢየሱስ የእግዚአብሔር መንግሥት በዓለም ካለ ከማንኛውም ነገር ይልቅ የከበረች ነች አለ፡፡ ለማንኛውም ሰው እጅግ በጣም አስፈላጊው ነገር የእግዚአብሔር መንግሥት ዜጋ መሆን ነው፡፡ ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ለመግባት ከኃጢአታችሁ መንጻት አለባችሁ፡፡

Image

ኢየሱስ አንዳንድ ሰዎች እርሱን ተቀብለውት እንደሚድኑ፣ ሌሎች ግን እንደማይቀበሉት አስተማረ፡፡ አንዳንድ ሰዎች እንደ መልካም መሬት ናቸው አለ፡፡ የኢየሱስን የምሥራች ተቀብለው ይድናሉ፡፡ ሌሎች ሰዎች ደግሞ የእግዚአብሔር ቃል እንደማይገባበትና ምንም ፍሬ እንደማያፈራ መንገድ ዳር እንዳለ መሬት ናቸው፡፡ እነዚያ ሰዎች ስለ ኢየሱስ የሚናገረውን መልእክት የማይቀበሉና ወደ መንግሥቱ የማይገቡ ናቸው፡፡

Image

ኢየሱስ፣ እግዚአብሔር ኃጢአተኞችን በጣም እንደሚወድ አስተማረ፡፡ ይቅር ሊላቸውና ልጆቹም ሊያደርጋቸው ይፈልጋል፡፡

Image

ደግሞም ኢየሱስ እግዚአብሔር ኃጢአትን እንደሚጠላ ነግሮናል፡፡ አዳምና ሔዋን ኃጢአት በሠሩ ጊዜ፣ ኃጢአቱ ዝርያዎቻቸውን ሁሉ አበላሸ፡፡ ከዚህ የተነሣ በዓለም ላይ ያለ ሁሉም ሰው ኃጢአት ሠርቶአል፤ ከእግዚአብሔርም ተለይቶአል፡፡ ስለዚህ ሁሉም ሰው የእግዚአብሔር ጠላት ሆኖአል፡፡

Image

ነገር ግን በእርሱ የሚያምን ሁሉ የዘላለም ሕይወት እንዲኖረው እንጂ እንዳይጠፋ እግዚአብሔር አንድያ ልጁን እስኪሰጥ ድረስ ዓለሙን እንዲሁ ወዶአል፡፡

Image

በኃጢአታችሁ ምክንያት በደለኞች ናችሁና መሞት ይገባችኋል፡፡ እግዚአብሔር በእናንተ ላይ መቈጣት ነበረበት፣ ነገር ግን ቊጣውን በእናንተ ላይ በማድረግ ፈንታ በኢየሱስ ላይ አፈሰሰው፡፡ ኢየሱስ በመስቀል ላይ በሞተ ጊዜ፣ የእናንተን ቅጣት ተቀበለ፡፡፡

Image

ኢየሱስ በፍጹም ኃጢአት አላደረገም፣ ነገር ግን የእናንተን ኃጢአትና በዓለም ያለውን የእያንዳንዱን ሰው ኃጢአት ለማስወገድ መቀጣትንና ፍጹም መሥዋዕት ሆኖ መሞትን መረጠ፡፡ ኢየሱስ ራሱን መሥዋዕት አድርጎ አቀረበ፡፡ ኢየሱስ ራሱን መሥዋዕት አድርጎ ስላቀረበ እግዚአብሔር ማንኛውንም ኃጢአት፣ አስከፊ የሆነውን ኃጢአት እንኳ ይቅር ማለት ይችላል፡፡

Image

መልካም ሥራዎች ሊያድኑአችሁ አይችሉም፡፡ ከእግዚአብሔር ጋር ግንኙነት እንዲኖራችሁ ልታደርጉ የምትችሉበት ሌላ ምንም ነገር የለም፡፡ ኢየሱስ ብቻ ኃጢአታችሁን ሊያጥብ ይችላል፡፡ ኢየሱስ የእግዚአብሔር ልጅ መሆኑን፣ በእናንተ ፈንታ በመስቀል ላይ መሞቱን እግዚአብሔርም ከሙታን እንዳስነሣው ብቻ ማመን አለባችሁ፡፡

Image

እግዚአብሔር በኢየሱስ የሚያምነውንና ጌታው አድርጎ የሚቀበለውን ማንኛውንም ሰው ያድናል፡፡ ነገር ግን በእርሱ የማያምነውን ማንኛውንም ሰው አያድንም። ባለ ጠጎች ብትሆኑ ወይም ድሆች፣ ወንድ ወይም ሴት፣ ሽማግሌ ወይም ወጣት ብትሆኑ፣ ወይም የትም ብትኖሩ እግዚአብሔር ይወዳችኋል፤ በኢየሱስ እንድታምኑና ከእርሱ ጋር የቅርብ ግንኙነት እንዲኖራችሁም ይፈልጋል፡፡

Image

ኢየሱስ በእርሱ እንድታምኑና እንድትጠመቁ ይጋብዛችኋል፡፡ ኢየሱስ መሲሕና ብቸኛው የእግዚአብሔር ልጅ መሆኑን ታምናላችሁ? ኃጢአተኞች መሆናችሁንና እግዚአብሔርም እናንተን መቅጣት እንዳለበት ታምናላችሁ? ኢየሱስ ኃጢአታችሁን ለማስወገድ በመስቀል ላይ መሞቱን ታምናላችሁ?

Image

በኢየሱስና እርሱ ለእናንተ በሠራው ሥራ ብታምኑ፣ እናንተ ክርስቲያኖች ናችሁ! እግዚአብሔርም ከሰይጣንና ከጨለማ መንግሥት አውጥቶአችሁ በእግዚአብሔር የብርሃን መንግሥት ውስጥም አድርጎአችኋል፡፡ እግዚአብሔር ታደርጉት የነበረውን አሮጌውንና ኃጢአተኛውን መንገዳችሁን አስወግዶ ዐዲስና የጽድቅ መንገድ እንድትኖሩ ዐዲስ ሕይወትን ሰጥቶአችኋል፡፡

Image

እናንተ ክርስቲያኖች ከሆናችሁ፣ ኢየሱስ በሠራው ሥራ ምክንያት እግዚአብሔር ኃጢአታችሁን ይቅር ብሏችኋል። አሁን እግዚአብሔር የእርሱ ጠላቶች ሳትሆኑ የቅርብ ወዳጆቹ አድርጎ ይቈጥራችኋል።

Image

እናንተ የእግዚአብሔር ወዳጆችና የጌታ ኢየሱስ አገልጋዮች ከሆናችሁ፣ ኢየሱስ ለሚያስተምራችሁ ነገር ትታዘዛላችሁ። ክርስቲያኖች ብትሆኑም እንኳ፣ አሁንም ኃጢአት ለመሥራት ትፈተናላችሁ። ነገር ግን እግዚአብሔር የታመነ ነውና ‹‹ኃጢአታችሁን ብትናዘዙ ይቅር እላችኋለሁ›› ይላል። ኃጢአትን የምትቃወሙበትንም ኃይል ይሰጣችኋል።

Image

እግዚአብሔር እንድትጸልዩ፣ ቃሉን እንድታጠኑ፣ ከሌሎች ክርስቲያኖች ጋር እንድታመልኩ፣ ያደረገላችሁንም ለሌሎች እንድትነግሩ ይጠይቃችኋል። እነዚህ ነገሮች ሁሉ ከእርሱ ጋር የጠበቀ ግንኙነት እንዲኖራችሁ ይረዱአችኋል።

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከሮሜ 3፡21-26፤ 5፡1-11፤ ዮሐንስ 3፡16፤ ማርቆስ 16፡16፤ ቈላስይስ 1፡13-14፤ 2ኛ ቆሮንቶስ 5፡17-21፤ 1ኛ ዮሐንስ 1፡5-10፡፡

50. ኢየሱስ ይመለሳል

Image

ለ2,000 ዓመታት ያህል በዓለም ዙሪያ ያሉ ብዙ ሰዎች ስለ መሲሑ ኢየሱስ የሚነገረውን የምሥራች እየሰሙ ቈይተዋል። ቤተ ክርስቲያን እያደገች ኖራለች። ኢየሱስ በዓለም ፍጻሜ እንደሚመለስ ተስፋ ሰጥቶአል። እርሱ ገና እስካሁን ባይመለስም እንኳ፣ የሰጠውን የተስፋ ቃል ለመፈጸም ይመጣል።

Image

እግዚአብሔር የኢየሱስን መመለስ እየተጠባበቅን፣ ቅዱስ በሆነና እርሱን በሚያስከብረው መንገድ እንድንኖር ይፈልጋል። ደግሞም ስለ መንግሥቱ ለሌሎች እንድንናገር ይፈልጋል። ኢየሱስ በምድር ላይ ይኖር በነበረበት ጊዜ ሲያስተምር፣ ‹‹ደቀ መዛሙርቴ ስለ እግዚአብሔር መንግሥት የምሥራች በዓለም ሁሉ በሁሉም ስፍራ ላሉ ሰዎች ይሰብካሉ፣ በዚያን ጊዜ ፍጻሜ ይመጣል›› ብሏል።

Image

ብዙ የሕዝብ ወገኖች አሁንም ስለ ኢየሱስ አልሰሙም። ኢየሱስ ወደ ሰማይ ከመመለሱ በፊት፣ የምሥራቹን ላልሰሙት ሰዎች እንዲያውጁ ለክርስቲያኖች ነገራቸው። ‹‹ሂዱና የሕዝብ ወገኖችን ሁሉ ደቀ መዛሙርት አድርጉአቸው!›› አለ። ደግሞም ‹‹መከሩም ደርሶአል!›› አለ።

Image

ደግሞም ኢየሱስ እንዲህ አለ፣ ‹‹አገልጋይ ከጌታው አይበልጥም። ልክ የዚህ ዓለም ባለ ሥልጣናት እኔን እንደ ጠሉኝ፤ እናንተንም በእኔ ምክንያት ያሠቃዩአችሁና ይገድሉአችኋል። ምንም እንኳ በዚህ ዓለም መከራ ብትቀበሉም፣ አይዞአችሁ ምክንያቱም እኔ ይህን ዓለም የሚገዛውን ሰይጣንን አሸንፌዋለሁ። እናንተ በእኔ አምናችሁ እስከ መጨረሻ ብትጸኑ፣ በዚያን ጊዜ እግዚአብሔር ያድናችኋል!››

Image

ኢየሱስ የዓለም ፍጻሜ በሚሆንበት ጊዜ፣ በሰዎች ላይ የሚደርሰውን ነገር ለማብራራት ለደቀ መዛሙርቱ አንድ ምሳሌ ነገራቸው። ‹‹አንድ ሰው በእርሻው መልካም ዘርን ዘራ። ተኝቶ እያለ ጠላቱ መጣና በስንዴው ላይ የአረም ዘር ዘራበትና ሄደ።››

Image

‹‹የተዘራው ስንዴ በበቀለ ጊዜ፣ የሰውዬው አገልጋዮች፣ ‹ጌታው፣ በዚያ እርሻ መልካም ዘር ዘርተህ ነበር። ታዲያ በውስጡ ለምንድን ነው አረም ያለበት?› ብለው ጠየቁት፣ ጌታውም፣ ‹የዘራው ጠላት መሆን አለበት››› ብሎ መለሰላቸው።

Image

‹‹አገልጋዮቹ ለጌታቸው፣ ‹አረሙን እንንቀለውን?› ብለው ጠየቁት። ጌታቸው እንዲህ አለ፣ ‹አይደለም። ይህንን ብታደርጉ ስንዴውንም ትነቅሉታላችሁ። እስከ መከር ድረስ ይቆዩ፤ በዚያን ጊዜ መላእክትን እልካለሁ። እነርሱም አረሙን ሰብስበው ያቃጥላሉ። ስንዴውን ግን በጎተራዬ ያከማቻሉ››› አላቸው።

Image

ደቀ መዛሙርቱ የምሳሌው ትርጕም አልገባቸውም፣ ስለዚህ እንዲያብራራላቸው ኢየሱስን ጠየቁት። ኢየሱስ እንዲህ አለ፣ ‹‹መልካሙን ዘር የዘራው ሰው መሲሑን ይወክላል። እርሻው ዓለምን ይወክላል። መልካሙ ዘር የእግዚአብሔርን መንግሥት ሰዎች ይወክላል።››

Image

‹‹አረሙ ከክፉው ወገን የሆኑ ሰዎችን ይወክላል። አረሙን የዘራው ጠላት ዲያብሎስን ይወክላል። መከሩ የዓለምን ፍጻሜ ይወክላል፣ አጫጆቹም የእግዚአብሔርን መላእክት ይወክላሉ።

Image

‹‹በዓለም ፍጻሜ፣ መላእክት የዲያብሎስ ወገኖች የሆኑ ሰዎችን ሁሉ በአንድ ላይ ይሰበስቡና ወደሚንቀለቀል እሳት ይጥሉአቸዋል፣ በዚያም ይጮኻሉ፤ አስከፊ በሆነ ሥቃይም ጥርሶቻቸውን ያፋጫሉ፡፡ በዚያን ጊዜ ጻድቃን በአባታቸው በእግዚአብሔር መንግሥት እንደ ፀሐይ ያበራሉ፡፡››

Image

ደግሞም ኢየሱስ ልክ ከዓለም ፍጻሜ በፊት ወደ ምድር እንደሚመለስ ተናገረ። በሄደበት አኳኋን ተመልሶ ይመጣል፣ ይኸውም፣ አካላዊ ሰውነት ይኖረዋል፣ በሰማይ ደመናም ይመጣል። ኢየሱስ በሚመለስበት ጊዜ እያንዳንዱ በክርስቶስ አምኖ የሞተ ክርስቲያን ከሙታን ይነሣና በሰማይ ላይ ይገናኘዋል።

Image

በዚያን ጊዜ ገና በሕይወት ያሉ ክርስቲያኖች ወደ ሰማይ ይነጠቁና ከሙታን ከተነሡ ሌሎች ክርስቲያኖች ጋር ይቀላቀላሉ። በዚያ ሁላቸውም ከኢየሱስ ጋር ይሆናሉ። ከዚያ በኋላ ኢየሱስ ከሕዝቡ ጋር ፍጹም በሆነ ሰላምና አንድነት ለዘላለም ይኖራል።

Image

ኢየሱስ በእርሱ ለሚያምኑ ሁሉ አክሊል ለመስጠት ተስፋ ሰጥቶአል። እነርሱ ፍጹም በሆነ ሰላም ከእግዚአብሔር ጋር ለዘላለም ይኖራሉ ይነግሣሉም።

Image

ነገር ግን እግዚአብሔር በኢየሱስ በማያምኑ ሁሉ ላይ ይፈርዳል። ለዘላለም ወደሚያለቅሱበትና በሥቃይ ጥርሶቻቸውን ወደሚያፏጩበት ወደ ገሃነም እሳት ይጥላቸዋል። ከቶ የማይጠፋ እሳት ባለማቋረጥ ያቃጥላቸዋል።

Image

ኢየሱስ በሚመለሰበት ጊዜ፣ ሰይጣንና መንግሥቱን ሙሉ በሙሉ ያጠፋቸዋል። ሰይጣንን ለእግዚአብሔር ከመታዘዝ ይልቅ እርሱን ለመከተል ከመረጡት ሁሉ ጋር ለዘላለም ወደሚቃጠሉበት ወደ ገሃነም ይጥለዋል።

Image

አዳምና ሔዋን ለእግዚአብሔር ስላልታዘዙና ኃጢአትን ወደዚህ ዓለም ስላመጡ፣ እግዚአብሔር ዓለምን ረገማት፤ ሊያጠፋትም ወሰነ። ነገር ግን አንድ ቀን እግዚአብሔር ፍጹም የሆነ ዐዲስ ሰማይና ዐዲስ ምድር ይፈጥራል።

Image

ኢየሱስና ሕዝቡ በዐዲሲቱ ምድር ይኖራሉ፣ ኢየሱስ በሁሉም ነገር ላይ ለዘላለም ይነግሣል፡፡ እርሱ እንባን ሁሉ ያብሳል፣ ከእንግዲህ ወዲያ ሥቃይ፣ ሐዘን፣ ልቅሶ፣ ክፋት፣ ሕመም፣ ወይም ሞት አይኖርም፡፡ ኢየሱስ መንግሥቱን በሰላምና በፍትሕ ይገዛል፣ ለዘላለምም ከሕዝቡ ጋር ይሆናል፡፡

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከማቴዎስ 24፡14፤ 28፡18፤ ዮሐንስ 15፡20፤ 16፡33፤ ራእይ 2፡10፤ ማቴዎስ 13፡24-30፤ 36-42፤ 1ኛ ተሰሎንቄ 4፡13-5፡11፤ ያዕቆብ 1፡12፤ ማቴዎስ 22፡13፤ ራእይ 20፡10፤ 21፡1-22፡21፡፡