7. እግዚአብሔር ያዕቆብን ባረከ

ልጆቹም እያደጉ ሲሄዱ ያዕቆብ በቤት መቆየትን ይወድ ነበር። ኤሳው ግን አደን ማደን ይወድ ነበር። ርብቃ ያዕቆብን ትወድደው ነበር፣ ይስሐቅ ግን ኤሳውን ይወድደው ነበር።

ከዕለታት አንድ ቀን ኤሳው ከአደን ተመልሶ ሲመጣ በጣም ተርቦ ነበር። ኤሳው ያዕቆብን ‹‹እባክህ ካዘጋጀኸው ምግብ ትንሽ ስጠኝ›› አለው። ያዕቆብም “በመጀመሪያ የብኩርናህን መብት ስጠኝ” ሲል መለሰለት። ስለዚህም ኤሳው የብኩርናውን መብት ለያዕቆብ ሰጠው። ከዚያም ያዕቆብ ከሠራው ምግብ ሰጠው።

ይስሐቅ ኤሳውን ሊባርከው ፈለገ። ነገር ግን ይህን ከማድረጉ በፊት ርብቃና ያዕቆብ ይስሐቅን አታለሉት። ያዕቆብ ኤሳውን መስሎ ወደ ይስሐቅ ቀረበ።በዚያ ጊዜ ይስሐቅ አርጅቶ ነበር፤ ማየትም አይችልም ነበር። ስለዚህም ያዕቆብ የኤሳውን ልብሶች ለብሶ የፍየል ለምድ በአንገቱና በእጆቹ አድርጎ ወደ ይስሐቅ በመቅረብ ይስሐቅን አታለለው።

ያዕቆብ ወደ ይስሐቅ መጣና እንዲህ አለው፣ ‹‹እኔ ኤሳው ነኝ፤ መጥቻለውና ባርከኝ››አለው። ይስሐቅ የፍየሉን ፀጉር ዳሰሰና የልብሱንም ጠረን አሽትቶ ኤሳው እንደ ሆነ አሰበና ባረከው።

ያዕቆብ የብኵርና መብቱንና በረከቱን አታልሎ ስለ ወሰደበት ኤሳው ያዕቆብን ጠላው። አባታቸው ሲሞት ሊገድለውም አቀደ።

ነገር ግን ርብቃ የኤሳውን እቅድ ሰማች። ስለዚህም እሷና ይስሐቅ ከዘመዶቹ ጋር እንዲኖር ወደ ሩቅ አገር ያዕቆብን ሰደዱት።

ያዕቆብ ለረዥም ዓመታት ከርብቃ ዘመዶች ጋር ኖረ። በዚያም ጊዜ ትዳር መስርቶ 12 ወንዶች ልጆችና 1 ሴት ልጅ ወለደ። እግዚአብሔርም በጣም አበለጸገው።

በከነዓን ከኖረበት ከሃያ (20) ዓመታት በኋላ ያዕቆብ ከቤተ ሰቡ፣ ከአገልጋዮቹና ከመንጋው ሁሉ ጋር ወደ ከነዓን ምድር ተመለሰ።

ኤሳው አሁንም ሊገድለኝ ያስብ ይሆናል ብሎ በልቡ ስላሰበ ያዕቆብ እጅግ በጣም ፈራ። ስለዚህም የእጅ መንሻ እንዲሆነው የብዙ ከብቶች መንጋ ስጦታ አድርጎ ለኤሳው ላከለት። ከብቶቹን ያመጡለት የያዕቆብ አገልጋዮች ኤሳውን ‹‹አገልጋይህ ያዕቆብ እነዚህን ከብቶች ልኮልሃል። እርሱም በቅርቡ ይመጣል›› አሉት።

ኤሳው ግን ቀድሞውኑ ያዕቆብን ይቅር ብሎት ስለ ነበር ዳግም ለመገናኘት በመብቃታቸው ደስ አለው። ያዕቆብ በከነዓን ምድር በሰላም ኖረ፤ ከዚያም ይስሐቅ ሞተ። ያዕቆብና ኤሳውም ቀበሩት። እግዚአብሔር ለአብርሃም የገባለት የቃል ኪዳኑ ተስፋ አሁን ከይስሐቅ ወደ ያዕቆብ ተላለፈ።
የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከዘፍጥረት 25፡27-33፡20፡፡