10. ዐሥሩ መቅሠፍቶች

ሙሴና አሮን ወደ ፈርዖን ሄደው “የእስራኤል አምላክ “ሕዝቤን ልቀቅ! ይልሃል” አሉት። ፈርዖን ግን አልሰማቸውም። እስራኤላውያን ነጻ ሆነው እንዲሄዱ በመልቀቅ ፈንታ ከበፊቱ የከበደ ሥራ እንዲሠሩ አስገደዳቸው!

ፈርዖን ሕዝቡን አልለቅም ማለቱን ቀጠለ፤ ስለዚህ እግዚአብሔር በግብፅ ላይ ዐሥር መቅሠፍቶችን ላከ። እግዚአብሔር በእነዚህ መቅሠፍቶች አማካይነት ከፈርዖንና ከግብፅ አማልክት ሁሉ ይልቅ ኃያል መሆኑን ለፈርዖን ዐሳየው።

እግዚአብሔር የዓባይን ውሃ ወደ ደም ለወጠው፣ ነገር ግን ፈርዖን አሁንም እስራኤላውያንን እንዲሄዱ አልለቀቃቸውም።

እግዚአብሔር በግብፅ ሁሉ ላይ እንቁራሪቶችን ላከ። ፈርዖን እንቁራሪቶቹን እንዲያርቅ ሙሴን ለመነው። እንቁራሪቶቹ ሁሉ ከሞቱ በኋላ ግን ፈርዖን ልቡን እንደገና አደነደነና እስራኤላውያንን ከግብፅ እንዲወጡ አልለቀቃቸውም።

ስለዚህ እግዚአብሔር የቅማል መቅሰፍት ላከ። ከዚያም የዝንብ መቅሰፍት ላከ። ፈርዖን ሙሴንና አሮንን ጠራና መቅሠፍቱን ካቆሙ እስራኤላውያን ከግብፅ መሄድ እንደሚችሉ ነገራቸው። ሙሴ በጸለየ ጊዜ እግዚአብሔር የዝንብ መቅሰፍቶችን ሁሉ ከግብፅ አስወገደ። ነገር ግን ፈርዖን ልቡን አደነደነና ሕዝቡን ነፃ እንዲወጡ አልለቀቃቸውም።

ቀጥሎ እግዚአብሔር የግብፃውያን ከብቶች ሁሉ ታመው እንዲሞቱ አደረገ። ነገር ግን የፈርዖን ልብ ስለደነደነ እስራኤላውያንን አልለቀቀም።

ከዚያም እግዚአብሔር በፈርዖን ፊት ዐመድ ወደ ሰማይ እንዲበትን ለሙሴ ነገረው። ዐመዱን በበተነ ጊዜ በግብፃውያን ላይ የሚያም ቊስል ሆነባቸው፣ በእስራኤላውያን ላይ ግን ቊስሉ አልሆነባቸውም። እግዚአብሔር የፈርዖንን ልብ ስላደነደነ ፈርዖን እስራኤላውያንን አልለቀቀም።

ከዚያ በኋላ እግዚአብሔር በግብፅ ያለውን አብዛኛውን ቡቃያ ያሚያጠፋና ከቤት ውጪ የነበረውን ማንኛውንም ሰው የሚገድል በረዶ ላከ። ፈርዖን ሙሴንና አሮንን ጠርቶ፣ ‹‹በድዬአለሁ። መሄድ ትችላላችሁ›› ብሎ ነገራቸው። ስለዚህ ሙሴ ጸለየ፣ በረዶውም ከሰማይ መዝነቡን አቆመ።

ነገር ግን ፈርዖን እንደ ገና ኃጢአት ሠራ፤ ልቡንም አደነደነ። እስራኤላውያንን አልለቀቀም።

ስለዚህ እግዚአብሔር በግብፅ ላይ የአንበጣዎችን መንጋ አመጣ። እነዚህ አንበጣዎች ከበረዶው የተረፈውን ሰብል ሁሉ አወደሙት።

ከዚያም እግዚአብሔር ለሦስት ቀን የቆየ ጨለማ ላከ። ጭለማው በጣም ከባድ ስለነበር ግብፃውያን ከቤታቸው ሊወጡ አቻሉም ነበር። እስራኤላውያን በሚኖሩበት ስፍራ ግን ብርሃን ነበረ።

ከእነዚህ ዘጠኝ መቅሠፍቶች በኋላ እንኳ ፈርዖን አሁንም እስራኤላውያንን አልለቅም አለ። ፈርዖን መስማት እንቢ ስላለ፣ እግዚአብሔር አንድ የመጨረሻ መቅሠፍት ለመላከ ወሰነ። ይህ መቅሰፍት ፈርዖን ዐሳቡን እንዲቀይር ያደርጋል።
የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከዘጸአት 5-10፡፡