21. እግዚአብሔር ስለ መሲሑ ተስፋ ሰጠ

ገና ከመጀመሪያው፣ እግዚአብሔር መሲሑን ለመላክ ዐቀደ፡፡ የመጀመሪያው የመሲሑ ተስፋ ወደ አዳምና ሔዋን መጣ፡፡ እግዚአብሔር የእባቡን ራስ የሚቀጠቅጥ የሔዋን ዘር እንደሚወለድ ተስፋ ሰጠ፡፡ ሔዋንን ያታለለው እባብ ሰይጣን ነበር፡፡ ተስፋው መሲሑ ሰይጣንን ፍጹም ያሸንፈዋል የሚል ነው፡፡

በእርሱ በኩል የዓለም ሕዝብ ወገኖች ሁሉ በረከት እንደሚቀበሉ እግዚአብሔር ለአብርሃም ተስፋ ሰጠው፡፡ ይህ በረከት ወደ ፊት መሲሑ ሲመጣ ይፈጸማል፡፡ እርሱ በዓለም ካሉ ከሁሉም የሕዝብ ወገኖች የሆኑ ሕዝቦች እንዲድኑ ያደርጋል፡፡

ወደ ፊት እንደ ሙሴ ያለ ሌላ ነቢይ እንደሚያስነሣ እግዚአብሔር ለሙሴ ተስፋ ሰጠው፡፡ ይህ ቆይቶ ስለሚመጣው መሲሕ የተሰጠ ሌላ ተስፋ ነበር፡፡

ከዝርያዎቹ አንዱ በእግዚአብሔር ሕዝብ ላይ ንጉሥ ሆኖ ለዘላለም እንደሚገዛ እግዚአብሔር ለንጉሥ ዳዊት ተስፋ ሰጠው፡፡ ይህም መሲሑ ከዳዊት ዝርያዎች አንዱ ይሆናል ማለት ነበር፡፡

እግዚአብሔር ዐዲስ ቃል ኪዳን እንደሚያደርግ በነቢዩ ኤርምያስ በኩል ተስፋ ሰጠ፣ ይህ ቃል ኪዳን እግዚአብሔር በሲና ከእስራኤል ጋር እንዳደረገው ቃል ኪዳን ግን አይደለም፡፡ በዐዲሱ ቃል ኪዳን እግዚአብሔር ሕጉን በሕዝቡ ልብ ይጽፋል፣ ሕዝቡ እግዚአብሔርን በግል ያውቁታል፣ ሕዝቡም ይሆናሉ፣ እግዚአብሔርም ኃጢአታቸውን ይቅር ይላል፡፡ መሲሑ ዐዲሱን ኪዳን ይጀምራል፡፡

ደግሞም የእግዚአብሔር ነቢያት መሲሑ ነቢይም፣ ካህንም እንዲሁም ንጉሥም ይሆናል አሉ፡፡ ነቢይ የእግዚአብሔርን ቃል የሚሰማ ከዚያም የእግዚአብሔርን ቃል ለሕዝቡ የሚያውጅ ሰው ነው፡፡ እግዚአብሔር ለመላክ ተስፋ የሰጠው መሲሕ እንከን የሌለው ነቢይ ይሆናል፡፡

የእስራኤላውያን ካህናት ስለ ሕዝብ ኃጢአት ለሚደርስባቸው ቅጣት ምትክ እንዲሆን በሕዝብ ፈንታ ለእግዚአብሔር መሥዋዕቶችን ያቀርቡ ነበር፡፡ ደግሞም ካህናት ስለ ሕዝቡ ወደ እግዚአብሔር ይጸለዩ ነበር፡፡ መሲሑ ደግሞ ፍጹም መሥዋዕት አድርጎ ራሱን ለእግዚአብሔር የሚያቀርብ ፍጹም ሊቀ ካህናት ይሆናል፡፡

ንጉሥ ማለት በመንግሥቱ ላይ የሚገዛና በሕዝቡ ላይ የሚፈርድ ሰው ነው። እንዲሁም መሲሑ በቅድመ አያቱ በዳዊት ዙፋን ላይ የሚቀመጥ ፍጹም ንጉሥ ይሆናል። በመላው ዓለም ላይ ለዘላለም ይገዛል፣ እንዲሁም ሁልጊዜ በቅንነት ይፈርዳል፤ ትክክለኛ ውሳኔም ይሰጣል።

የእግዚአብሔር ነቢያት ስለ መሲሑ ሌሎች ብዙ ነገሮችን ተንብየዋል፡፡ ነቢዩ ሚልክያስ መሲሑ ከመምጣቱ በፊት ታላቅ ነቢይ እንደሚመጣ አስቀድሞ ተነበየ፡፡ መሲሑ ከአንዲት ድንግል እንደሚወለድ ነቢዩ ኢሳይያስ ተነበየ፡፡ ነቢዩ ሚክያስ መሲሑ በቤተልሔም ከተማ ይወለዳል አለ፡፡

ነቢዩ ኢሳይያስ መሲሑ በገሊላ ይኖራል፣ ልባቸው የተሰበረ ሰዎችን ያጽናናል፣ እንዲሁም ለተማረኩት ነጻነትንና ለታሰሩት መፈታትን ያውጃል ብሎአል፡፡ ደግሞም ነቢዩ መሲሑ የታመሙና መስማት፣ ማየት፣ መናገር፣ ወይም መራመድ የማይችሉትን ሕዝብ እንደሚፈውስ ተነበየ፡፡

ደግሞም ነቢዩ ኢሳይያስ ሰዎች ያለ ምክንያት መሲሑን እንደሚጠሉትና እንደማይቀበሉት ተነበየ። ሌሎች ነቢያት መሲሑን የገደሉት እነዚያ በልብሶቹ ላይ ዕጣ እንድሚጣጣሉና ወዳጁ አሳልፎ እንደሚሰጠው አስቀድመው ተነበዩ። ነቢዩ ዘካርያስ መሲሑን አሳልፎ የሚሰጠው ወዳጅ ሠላሳ ብር እንደሚከፈለው ተነበየ።

ደግሞም ነቢያት ስለ መሲሑ አሟሟት ተናገሩ፡፡ ኢሳይያስ ሰዎች በመሲሑ እንደሚተፉበት፣ እንደሚያፌዙበትና እንደሚመቱት ተነበየ፡፡ ምንም ክፉ ነገር ያላደረገ ቢሆንም እንኳ ይወጉታል፤ በታላቅ መከራና ሥቃይ ይሞታል፡፡

ደግሞም ነቢያት መሲሑ ምንም ኃጢአት የሌለበት ፍጹም ይሆናል ብለዋል፡፡ የሌሎች ሰዎችን የኃጢአት ቅጣት ለመቀበል እርሱ ይሞታል፡፡ የእርሱ መቀጣት በእግዚአብሔርና በሰዎች መካከል ሰላምን ያመጣል፡፡ በዚህ ምክንያት መሲሑን ማድቀቅ የእግዚአብሔር ፈቃድ ነበር፡፡

መሲሑ እንደሚሞትና እግዚአብሔር ደግሞ ከሙታን እንደሚያስነሣው ነቢያት አስቀድመው ተነበዩ፡፡ እግዚአብሔር በመሲሑ ሞትና ትንሣኤ በኩል ኃጢአተኞችን ለማዳንና ዐዲሱን ኪዳን ለመጀመር የያዘውን ዕቅዱን ይፈጽማል፡፡

እግዚአብሔር ለነቢያት ስለ መሲሑ ብዙ ነገሮችን ገለጠላቸው፣ ነገር ግን መሲሑ ከእነዚያ ነቢያት በአንዳቸውም ዘመን አልመጣም። ከእነዚህ ትንቢቶች የመጨረሻው ከተተነበየ ከ400 ዓመታት በኋላ፣ ልክ በትክክለኛው ጊዜ፣ እግዚአብሔር መሲሑን ወደ ዓለም ላከ።
የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከዘፍጥረት 3፡15፤ 12፡1-3፤ ዘዳግም 18፡15፤ 2ኛ ሳሙኤል 7፤ ኤርምያስ 31፤ ኢሳይያስ 59፡16፤ ዳንኤል 7፤ ሚልክያስ 4፡5፤ ኢሳይያስ 7፡14፤ ሚክያስ 5፡2፤ ኢሳይያስ 9፡1-7፤ 35፡3-5፤ 61፡53፤ መዝሙር 22፡18፤ 35፡19፤ 69፡4፤ 41፡9፤ ዘካርያስ 11፡12-13፤ ኢሳይያስ 50፡6፤ መዝሙር 16፡10-11፡፡