አማርኛ: Open Bible Stories

Updated ? hours ago # views See on DCS

21. እግዚአብሔር ስለ መሲሑ ተስፋ ሰጠ

Image

ገና ከመጀመሪያው፣ እግዚአብሔር መሲሑን ለመላክ ዐቀደ፡፡ የመጀመሪያው የመሲሑ ተስፋ ወደ አዳምና ሔዋን መጣ፡፡ እግዚአብሔር የእባቡን ራስ የሚቀጠቅጥ የሔዋን ዘር እንደሚወለድ ተስፋ ሰጠ፡፡ ሔዋንን ያታለለው እባብ ሰይጣን ነበር፡፡ ተስፋው መሲሑ ሰይጣንን ፍጹም ያሸንፈዋል የሚል ነው፡፡

Image

በእርሱ በኩል የዓለም ሕዝብ ወገኖች ሁሉ በረከት እንደሚቀበሉ እግዚአብሔር ለአብርሃም ተስፋ ሰጠው፡፡ ይህ በረከት ወደ ፊት መሲሑ ሲመጣ ይፈጸማል፡፡ እርሱ በዓለም ካሉ ከሁሉም የሕዝብ ወገኖች የሆኑ ሕዝቦች እንዲድኑ ያደርጋል፡፡

Image

ወደ ፊት እንደ ሙሴ ያለ ሌላ ነቢይ እንደሚያስነሣ እግዚአብሔር ለሙሴ ተስፋ ሰጠው፡፡ ይህ ቆይቶ ስለሚመጣው መሲሕ የተሰጠ ሌላ ተስፋ ነበር፡፡

Image

ከዝርያዎቹ አንዱ በእግዚአብሔር ሕዝብ ላይ ንጉሥ ሆኖ ለዘላለም እንደሚገዛ እግዚአብሔር ለንጉሥ ዳዊት ተስፋ ሰጠው፡፡ ይህም መሲሑ ከዳዊት ዝርያዎች አንዱ ይሆናል ማለት ነበር፡፡

Image

እግዚአብሔር ዐዲስ ቃል ኪዳን እንደሚያደርግ በነቢዩ ኤርምያስ በኩል ተስፋ ሰጠ፣ ይህ ቃል ኪዳን እግዚአብሔር በሲና ከእስራኤል ጋር እንዳደረገው ቃል ኪዳን ግን አይደለም፡፡ በዐዲሱ ቃል ኪዳን እግዚአብሔር ሕጉን በሕዝቡ ልብ ይጽፋል፣ ሕዝቡ እግዚአብሔርን በግል ያውቁታል፣ ሕዝቡም ይሆናሉ፣ እግዚአብሔርም ኃጢአታቸውን ይቅር ይላል፡፡ መሲሑ ዐዲሱን ኪዳን ይጀምራል፡፡

Image

ደግሞም የእግዚአብሔር ነቢያት መሲሑ ነቢይም፣ ካህንም እንዲሁም ንጉሥም ይሆናል አሉ፡፡ ነቢይ የእግዚአብሔርን ቃል የሚሰማ ከዚያም የእግዚአብሔርን ቃል ለሕዝቡ የሚያውጅ ሰው ነው፡፡ እግዚአብሔር ለመላክ ተስፋ የሰጠው መሲሕ እንከን የሌለው ነቢይ ይሆናል፡፡

Image

የእስራኤላውያን ካህናት ስለ ሕዝብ ኃጢአት ለሚደርስባቸው ቅጣት ምትክ እንዲሆን በሕዝብ ፈንታ ለእግዚአብሔር መሥዋዕቶችን ያቀርቡ ነበር፡፡ ደግሞም ካህናት ስለ ሕዝቡ ወደ እግዚአብሔር ይጸለዩ ነበር፡፡ መሲሑ ደግሞ ፍጹም መሥዋዕት አድርጎ ራሱን ለእግዚአብሔር የሚያቀርብ ፍጹም ሊቀ ካህናት ይሆናል፡፡

Image

ንጉሥ ማለት በመንግሥቱ ላይ የሚገዛና በሕዝቡ ላይ የሚፈርድ ሰው ነው። እንዲሁም መሲሑ በቅድመ አያቱ በዳዊት ዙፋን ላይ የሚቀመጥ ፍጹም ንጉሥ ይሆናል። በመላው ዓለም ላይ ለዘላለም ይገዛል፣ እንዲሁም ሁልጊዜ በቅንነት ይፈርዳል፤ ትክክለኛ ውሳኔም ይሰጣል።

Image

የእግዚአብሔር ነቢያት ስለ መሲሑ ሌሎች ብዙ ነገሮችን ተንብየዋል፡፡ ነቢዩ ሚልክያስ መሲሑ ከመምጣቱ በፊት ታላቅ ነቢይ እንደሚመጣ አስቀድሞ ተነበየ፡፡ መሲሑ ከአንዲት ድንግል እንደሚወለድ ነቢዩ ኢሳይያስ ተነበየ፡፡ ነቢዩ ሚክያስ መሲሑ በቤተልሔም ከተማ ይወለዳል አለ፡፡

Image

ነቢዩ ኢሳይያስ መሲሑ በገሊላ ይኖራል፣ ልባቸው የተሰበረ ሰዎችን ያጽናናል፣ እንዲሁም ለተማረኩት ነጻነትንና ለታሰሩት መፈታትን ያውጃል ብሎአል፡፡ ደግሞም ነቢዩ መሲሑ የታመሙና መስማት፣ ማየት፣ መናገር፣ ወይም መራመድ የማይችሉትን ሕዝብ እንደሚፈውስ ተነበየ፡፡

Image

ደግሞም ነቢዩ ኢሳይያስ ሰዎች ያለ ምክንያት መሲሑን እንደሚጠሉትና እንደማይቀበሉት ተነበየ። ሌሎች ነቢያት መሲሑን የገደሉት እነዚያ በልብሶቹ ላይ ዕጣ እንድሚጣጣሉና ወዳጁ አሳልፎ እንደሚሰጠው አስቀድመው ተነበዩ። ነቢዩ ዘካርያስ መሲሑን አሳልፎ የሚሰጠው ወዳጅ ሠላሳ ብር እንደሚከፈለው ተነበየ።

Image

ደግሞም ነቢያት ስለ መሲሑ አሟሟት ተናገሩ፡፡ ኢሳይያስ ሰዎች በመሲሑ እንደሚተፉበት፣ እንደሚያፌዙበትና እንደሚመቱት ተነበየ፡፡ ምንም ክፉ ነገር ያላደረገ ቢሆንም እንኳ ይወጉታል፤ በታላቅ መከራና ሥቃይ ይሞታል፡፡

Image

ደግሞም ነቢያት መሲሑ ምንም ኃጢአት የሌለበት ፍጹም ይሆናል ብለዋል፡፡ የሌሎች ሰዎችን የኃጢአት ቅጣት ለመቀበል እርሱ ይሞታል፡፡ የእርሱ መቀጣት በእግዚአብሔርና በሰዎች መካከል ሰላምን ያመጣል፡፡ በዚህ ምክንያት መሲሑን ማድቀቅ የእግዚአብሔር ፈቃድ ነበር፡፡

Image

መሲሑ እንደሚሞትና እግዚአብሔር ደግሞ ከሙታን እንደሚያስነሣው ነቢያት አስቀድመው ተነበዩ፡፡ እግዚአብሔር በመሲሑ ሞትና ትንሣኤ በኩል ኃጢአተኞችን ለማዳንና ዐዲሱን ኪዳን ለመጀመር የያዘውን ዕቅዱን ይፈጽማል፡፡

Image

እግዚአብሔር ለነቢያት ስለ መሲሑ ብዙ ነገሮችን ገለጠላቸው፣ ነገር ግን መሲሑ ከእነዚያ ነቢያት በአንዳቸውም ዘመን አልመጣም። ከእነዚህ ትንቢቶች የመጨረሻው ከተተነበየ ከ400 ዓመታት በኋላ፣ ልክ በትክክለኛው ጊዜ፣ እግዚአብሔር መሲሑን ወደ ዓለም ላከ።

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከዘፍጥረት 3፡15፤ 12፡1-3፤ ዘዳግም 18፡15፤ 2ኛ ሳሙኤል 7፤ ኤርምያስ 31፤ ኢሳይያስ 59፡16፤ ዳንኤል 7፤ ሚልክያስ 4፡5፤ ኢሳይያስ 7፡14፤ ሚክያስ 5፡2፤ ኢሳይያስ 9፡1-7፤ 35፡3-5፤ 61፡53፤ መዝሙር 22፡18፤ 35፡19፤ 69፡4፤ 41፡9፤ ዘካርያስ 11፡12-13፤ ኢሳይያስ 50፡6፤ መዝሙር 16፡10-11፡፡