አማርኛ: Open Bible Stories

Updated ? hours ago # views See on DCS

42. ኢየሱስ ወደ ሰማይ ተመለሰ

Image

ኢየሱስ ከሙታን በተነሣበት ቀን ከደቀ መዛሙርቱ ሁለቱ በአቅራቢያው ወዳለች ከተማ እየሄዱ ነበር። ሲጓዙም፣ በኢየሱስ ላይ ስለ ደረሰበት ነገር ሲነጋገሩ ነበር። እርሱ መሲሕ እንደ ሆነ ተስፋ አድርገው ነበር፣ ነገር ግን እርሱ ተገደለ። አሁን ሴቶቹ እንደ ገና ሕያው ሆኖአል አሉ። ሁለቱ ደቀ መዛሙርት የቱን ማመን እንዳለባቸው ግራ ገብቷቸው ነበር።

Image

ኢየሱስ ወደ እነርሱ ቀረበና አብሮአቸው መጓዝ ጀመረ፣ እነርሱ ግን ዐላወቁትም ነበር። ስለ ምን ይነጋገሩ እንደ ነበረ ጠየቃቸው፣ እነርሱም ባለፉት ጥቂት ቀናት ውስጥ ኢየሱስን በተመለከተ ስለ ሆኑት አስገራሚ ነገሮች ሁሉ ነገሩት። የሚነጋገሩት በኢየሩሳሌም የሆነውን ነገር ከማያውቅ ከእንግዳ ሰው ጋር መስሏቸው ነበር።

Image

ከዚያም ኢየሱስ፣ ስለ መሲሑ የእግዚአብሔር ቃል የተናገረውን አብራራላቸው። መሲሑ መከራ እንደሚቀበልና እንደሚገደል፣ ነገር ግን በሦስተኛው ቀን እንደሚነሣ ነቢያት የተናገሩትን አስታወሳቸው። ሁለቱ ሰዎች ሊያድሩባት ወዳሰቡአት ከተማ ሲደርሱ፣ ጊዜው መሽቶ ነበር።

Image

ሁለቱ ሰዎች ከእነርሱ ጋር እንዲያድር ኢየሱስን ጋበዙት፣ እርሱም እሺ አላቸው። እራት ለመብላት በተዘጋጁ ጊዜ ኢየሱስ እንጀራን አንሥቶ እግዚአብሔርን አመሰገነ፣ ከዚያም ቈረሰው። ወዲያውኑ ኢየሱስ መሆኑን ዐወቁ። ነገር ግን በዚያን ጊዜ እርሱ ከዓይናቸው ተሰወረ።

Image

ሁለቱም ሰዎች፣ ‹‹ኢየሱስ ነው! የእግዚአብሔርን ቃል ሲያብራራልን ልባችን ሲቃጠልብን የነበረው ስለዚህ ነው!›› ተባባሉ፡፡ ወዲያውኑ፣ ወደ ኢየሩሳሌም ተመለሱ፡፡ በደረሱም ጊዜም ለደቀ መዛሙርቱ፣ ‹‹ኢየሱስ ሕያው ነው! ዐይተነዋል!›› ብለው ነገሩአቸው፡፡

Image

ደቀ መዛሙርቱ እየተነጋገሩ እያሉ፣ ኢየሱስ በድንገት በነበሩበት ክፍል በመካከላቸው ተገኘና፣ ‹‹ሰላም ለእናንተ ይሁን!›› አላቸው። ደቀ መዛሙርቱ መንፈስ መሰላቸው፣ ኢየሱስ ግን፣ ‹‹ለምን ትፈራላችሁ፤ ትጠራጠራላችሁም? እጆቼንና እግሮቼን እዩ። መናፍስት እንደ እኔ አካል የላቸውም›› አላቸው። መንፈስ አለመሆኑን ለማረጋገጥ የሚበላ ነገር እንዲሰጡት ጠየቃቸው። እነርሱም ከተጠበሰ ዓሣ አንድ ሰጡት፣ እርሱም በላ።

Image

ኢየሱስም፣ ‹‹በእግዚአብሔር ቃል ስለ እኔ የተጻፈው ሁሉ መፈጸም አለበት ብዬ ነግሬአችኋለሁ›› አለ። በዚያን ጊዜ የእግዚአብሔርን ቃል እንዲረዱ አእምሮአቸውን ከፈተላቸው። ‹‹መሲሑ መከራ እንደሚቀበል፣ እንደሚሞት፣ በሦስተኛው ቀን ከሙታን እንደሚነሣ ከረጅም ዘመን በፊት ተጽፎአል›› አላቸው።

Image

“ደግሞም የኃጢአታቸውን ይቅርታ ለማግኘት ሰዎች ሁሉ ንስሐ ይገቡ ዘንድ ደቀ መዛሙርቴ እንደሚያውጁ በመጻሕፍት ተጽፎአል። እነርሱ ከኢየሩሳሌም ጀምሮ ይህን ያደርጋሉ፣ ከዚያም በሁሉም ስፍራ ወዳሉ የሕዝብ ወገኖች ሁሉ ይሄዳሉ። እናንተ የእነዚህ ነገሮች ምስክሮች ናችሁ።” አላቸው።

Image

በቀጣዮቹ አርባ ቀናት ኢየሱስ ብዙ ጊዜ ለደቀ መዛሙርቱ ታያቸው። አንድ ጊዜ ከ500 ለሚበልጡ ሰዎች በአንድ ጊዜ ታይቷቸው ነበር! እርሱ ሕያው መሆኑን በብዙ መንገድ ለደቀ መዛሙርቱ አረጋገጠላቸው፣ ስለ እግዚአብሔር መንግሥትም አስተማራቸው።

Image

ኢየሱስ ለደቀ መዛሙርቱ እንዲህ አላቸው፣ ‹‹ሥልጣን ሁሉ በሰማይና በምድር ተሰጥቶኛል። ስለዚህ ሂዱ፣ የሕዝብ ወገኖችን ሁሉ በአብ፣ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም እያጠመቃችኋቸው፣ ያዘዝኋችሁንም ሁሉ እንዲፈጽሙ እያስተማራችኋቸው ደቀ መዛሙርቴ አድርጓቸው። እኔ ሁልጊዜ ከእናንተ ጋር ነኝ።››

Image

ኢየሱስ ከሙታን ከተነሣ ከአርባ ቀናት በኋላ ደቀ መዛሙርቱን፣ ‹‹መንፈስ ቅዱስ በእናንተ ላይ ወርዶ ኃይልን እስክትቀበሉ ድረስ በኢየሩሳሌም ቆዩ›› አላቸው፡፡ ከዚያ በኋላ ኢየሱስ ወደ ሰማይ ወጣ፣ ደመናም ከዓይናቸው ሰወረችው፡፡ ኢየሱስ ሁሉንም ነገር ሊገዛ በእግዚአብሔር ቀኝ ተቀመጠ፡፡

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከማቴዎስ 28፡16-20፤ ማርቆስ 16፡12-20፤ ሉቃስ 24፡13-53፤ ዮሐንስ 20፡19-23፤ የሐዋርያት ሥራ 1፡1-11።