25. ሰይጣን ኢየሱስን ፈተነው

ኢየሱስ ከተጠመቀ በኋላ ወዲያውኑ፣ መንፈስ ቅዱስ ወደ ምድረ በዳ ወሰደው፣ እዚያም አርባ ቀንና አርባ ሌሊት ጾመ፡፡ ከዚያም ሰይጣን ወደ ኢየሱስ መጣና ኃጢአት እንዲሠራ ኢየሱስን ፈተነው፡፡

‹‹የእግዚአብሔር ልጅስ ከሆንክ፣እነዚህን ድንጋዮች ወደ እንጀራ ለውጥ›› በማለት ሰይጣን ኢየሱስን ፈተነው፡፡

ኢየሱስ፣ ‹‹‹ሰዎች ለመኖር እንጀራ ብቻ አያስፈልጋቸውም፣ ነገር ግን እግዚአብሔር የሚናገረው እያንዳንዱ ቃል ያስፈልጋቸዋል› ተብሎ በእግዚአብሔር ቃል ተጽፎአል!›› ብሎ መለሰለት፡፡

ከዚያም ሰይጣን ኢየሱስን ወደ ቤተ መቅደስ ጫፍ ወሰደውና፣ ‹‹የእግዚአብሔር ልጅ ከሆንክ ራስህን ወደ ታች ወርውር፣ ምክንያቱም፣ ‹ድንጋይ እግርህን እንዳይመታህ ይሸከሙህ ዘንድ እግዚአብሔር መላእክቱን ያዛል ተብሎ ተጽፎል››› አለ፡፡

ነገር ግን ኢየሱስ ከእግዚአብሔር ቃል በመጥቀስ ለሰይጣን መለሰለት፡፡ ‹‹በእግዚአብሔር ቃል፣ ‹ጌታ አምላክህን አትፈታተነው› ተብሎ ተጽፎአል›› አለው፡፡

ከዚያም ሰይጣን የዓለምን መንግሥታትና ክብራቸውን ሁሉ ዐሳየውና፣ ‹‹ወድቀህ ብትሰግድልኝ ይህን ሁሉ እሰጥሃለሁ›› አለ፡፡

ኢየሱስ፣ ‹‹ከኔ ራቅ፣ አንተ ሰይጣን! በእግዚአብሔር ቃል፣ ‹ለጌታህ ለአምላክህ ስገድ እርሱንም ብቻ አምልክ› ተብሎ ተጽፎአል›› አለው፡፡

ኢየሱስ ለሰይጣን ፈተና አልተሸነፈም፣ ስለዚህ ሰይጣን ለጊዜው ትቶት ሄደ፡፡ ከዚያ በኋላ መላእክት መጥተው ኢየሱስን አገለገሉት፡፡
የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከማቴዎስ 4፡1-11፤ ማርቆስ 1፡12-13፤ ሉቃስ 4፡1-13፡፡