36. የኢየሱስ መልክ ተለወጠ

አንድ ቀን ኢየሱስ ከደቀ መዛሙርቱ ሦስቱን፦ ጴጥሮስን፣ ያዕቆብንና ዮሐንስን ይዞ ብቻቸውን ሊጸልዩ ወደ ረጅም ተራራ ወጡ፡፡(ዮሐንስ የተባለው ደቀ መዝሙር ኢየሱስን ያጠመቀው ዮሐንስ አይደለም፡፡)

ኢየሱስ በመጸለይ ላይ እያለ፣ ፊቱ እንደ ፀሐይ አበራ፣ ልብሱም እንደ ብርሃን ነጭ ሆነ፣ ንጻቱም በምድር ላይ ያለ ማንኛውም ሰው ሊያነጻው እስከማይችል ድረስ በጣም ነጭ ነበር፡፡

በዚያን ጊዜ ሙሴና ነቢዩ ኤልያስ ታዩ፡፡ እነዚህ ሰዎች በመቶዎች ከሚቈጠሩ ዓመታት በፊት በምድር ላይ ይኖሩ ነበር፡፡ እነርሱም በቅርቡ በኢየሩሳሌም ስለሚሆነው ስለ ኢየሱስ ሞት ከእርሱ ጋር ተነጋገሩ፡፡

ሙሴና ኤልያስ ከኢየሱስ ጋር በመነጋገር ላይ እያሉ ጴጥሮስ ኢየሱስን፣ ‹‹በዚህ መሆን ለእኛ መልካም ነው፡፡ ሦስት ዳሶችን አንድ ለአንተ፣ አንድ ለሙሴ፣ እንዲሁም አንድ ለኤልያስ እንሥራ›› አለው፡፡ ጴጥሮስ የሚናገረውን አያውቅም ነበር፡፡

ጴጥሮስ እየተናገረ እያለ፣ ብሩህ ደመና መጥቶ ከበባቸውና ከደመናውም ድምፅ፣ ‹‹በእርሱ ደስ የሚለኝ የምወደው ልጄ ይህ ነው፣ እርሱን ስሙት›› አለ፡፡ ሦስቱ ደቀ መዛሙርት ፈሩና መሬት ላይ ወደቁ፡፡

በዚያን ጊዜ ኢየሱስ ዳሰሳቸውና፣ ‹‹አትፍሩ፣ ተነሡ›› አላቸው፡፡ ዙሪያቸውን ሲያዩ ከእነርሱ ጋር ያለው ኢየሱስ ብቻ ነበር፡፡

ኢየሱስና ሦስቱ ደቀ መዛሙርት ከተራራው ወረዱ፡፡ በዚያን ጊዜ ኢየሱስ እንዲህ አላቸው፣ ‹‹በዚህ ስለ ሆነው ነገር አሁን ለማንም አትናገሩ፡፡ እኔ በቅርብ ጊዜ እሞታለሁ፣ ተመልሼም ሕያውም እሆናለሁ፡፡ ከዚያ በኋላ ለሰዎች መናገር ትችላላችሁ፡፡››
የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከማቴዎስ 17፡1-9፤ ማርቆስ 9፡2-8፤ ሉቃስ 9፡28-36፡፡