አማርኛ: Open Bible Stories

Updated ? hours ago # views See on DCS

45. እስጢፋኖስ እና ፊሊጶስ

Image

በጥንትዋ ቤተ ክርስቲያን ከነበሩት መሪዎች አንዱ እስጢፋኖስ ተብሎ የሚጠራ ሰው ነበር። እርሱ መልካም ስም ያለውና መንፈስ ቅዱስና ጥበብ የሞላበት ሰው ነበር። እስጢፋኖስ ብዙ ተአምራትን ያደረገና ሰዎች በኢየሱስ እንዲያምኑ በደንብ አስረድቶ ያሳምናቸው ነበር።

Image

አንድ ቀን እስጢፋኖስ ስለ ኢየሱስ በሚያስተምርበት ጊዜ፣ በኢየሱስ ያላመኑ አንዳንድ አይሁዶች ከእስጢፋኖስ ጋር መከራከር ጀመሩ። በጣም ተቈጡና ስለ እስጢፋኖስ ለሃይማኖት መሪዎች ዋሽተው ተናገሩ። ‹‹ስለ ሙሴና ስለ እግዚአብሔር ክፉ ነገሮችን ሲናገር ሰምተነዋል!›› አሉ። ስለዚህ የሃይማኖት መሪዎቹ እስጢፋኖስን ያዙትና ወደ ሊቀ ካህናቱና ወደ ሌሎቹ የአይሁድ መሪዎች አምጥተው ሌሎች ተጨማሪ የሐሰት ምስክሮች ስለ እስጢፋኖስ ዋሽተው እንዲመሰክሩ አደረጉ።

Image

ሊቀ ካህናቱ እስጢፋኖስን፣ ‹‹እነዚህ ነገሮች እውነት ናቸውን?›› ብሎ ጠየቀው፡፡ እስጢፋኖስ ከአብርሃም ዘመን ጀምሮ እስከ ኢየሱስ ዘመን ድረስ እግዚአብሔር ስላደረጋቸው ብዙ ታላላቅ ነገሮች፣ እንዲሁም የእግዚአብሔር ሕዝብ በተከታታይ በእርሱ ላይ ስለ ማመፃቸው በማስታወስ መልስ ሰጠ፡፡ ከዚያም እንዲህ አለ፣ ‹‹እናንተ አንገተ ደንዳኖችና ዓመፀኞች ልክ ቅድመ አያቶቻችሁ እግዚአብሔርን እንደ ተቃወሙትና ነቢያቱን እንደ ገደሉ ሁልጊዜ መንፈስ ቅዱስን ትቃወማላችሁ፡፡ እናንተ ግን ከእነርሱ ይልቅ የባሰ ክፉ ነገር አድርጋችኋል፡፡ መሲሑን ገድላችኋል!››

Image

የሃይማኖት መሪዎቹ ይህንን በሰሙ ጊዜ፣ በጣም ተናደው ጆሮአቸውን ደፈኑና ከፍ ባለ ድምፅ ጮኹ። እስጢፋኖስን ከከተማይቱ ውጪ ጐተቱትና ሊገድሉት በድንጋይ ወገሩት።

Image

እስጢፋኖስ በመሞት ላይ እያለ፣ ‹‹ኢየሱስ ሆይ፣ ነፍሴን ተቀበላት›› ብሎ ጮኸ። ከዚያም በጉልበቱ ተንበረከከና፣ ‹‹ጌታ ሆይ፣ ይህንን ኃጢአት አትቊጠርባቸው›› ብሎ እንደ ገና ጮኸ። ከዚያ በኋላ ሞተ።

Image

ሳውል የተባለ አንድ ወጣት እስጢፋኖስን ከሚገድሉት ሰዎች ጋር ተስማምቶ በእርሱ ላይ ድንጋይ በሚወረውሩበት ጊዜ ልብሳቸውን ይጠብቅ ነበር። በዚያን ዕለት በኢየሩሳሌም የነበሩ ብዙ ሰዎች የኢየሱስን ተከታዮች ማሳደድ ጀመሩ፣ ስለዚህ አማኞቹ ወደ ሌሎች ስፍራዎች ሸሹ። ነገር ግን ስደቱ ቢኖርም እንኳ፣ በሄዱበት ስፍራ ሁሉ ስለ ኢየሱስ ሰበኩ።

Image

ፊልጶስ የተባለ የኢየሱስ ደቀ መዝሙር በስደቱ ጊዜ ከኢየሩሳሌም ከሸሹት አማኞች አንዱ ነበር። ወደ ሰማርያ ሄዶ ስለ ኢየሱስ ሰበከና ብዙ ሰዎች ዳኑ። ከዚያ በኋላ አንድ ቀን ከእግዚአብሔር የተላከ መልአክ በምድረ በዳ ወዳለ አንድ መንገድ እንዲሄድ ለፊልጶስ ነገረው። ፊልጶስ በመንገዱ በመሄድ ላይ እያለ አንድ ትልቅ ኢትዮጵያዊ ባለ ሥልጣን በሰረገላው ሲሄድ ዐየ። ወደዚህ ሰው ሄዶ እንዲያነጋግረው መንፈስ ቅዱስ ለፊልጶስ ነገረው።

Image

ፊልጶስ ወደ ሰረገለው በቀረበ ጊዜ፣ ኢትዮጵያዊው ነቢዩ ኢሳይያስ ከጻፈው ውስጥ አንዱን ክፍል ሲያነብ ሰማ፡፡ ሰውዬው እንዲህ ብሎ ሲያነብ ነበር፣ ‹‹እንደ በግ ወደ መታረድ ተነዳ፣ የበግ ጠቦትም በሸላቹ ፊት ዝም እንደሚል እንዲሁ አፉን አልከፈተም፡፡ በፍርድ ተወሰደ፣ አላከበሩትምም፡፡ ከሕያዋን ምድር አስወገዱት፡፡››

Image

ፊልጶስ ኢትዮጵያዊውን፣ ‹‹የምታነበውን ታስተውለዋለህን?›› ብሎ ጠየቀው። ኢትዮጵያዊውም፣ ‹‹አይደለም። የሚያስረዳኝ ሰው ሳይኖር እንዴት ልረዳ እችላለሁ። እባክህን ናና ከጐኔ ተቀመጥ። ኢሳይያስ የጻፈው ስለ ራሱ ነውን ወይስ ስለ ሌላ ሰው?›› ብሎ መለሰ።

Image

ኢሳይያስ የጻፈው ስለ ኢየሱስ መሆኑን ፊልጶስ ለኢትዮጵያዊው አብራራለት። ደግሞም ፊልጶስ ስለ ኢየሱስ የሚናገረውን የምሥራች ሲያስረዳው ሌሎች የእግዚአብሔር ቃል ክፍሎችን ተጠቀመ።

Image

ፊልጶስና ኢትዮጵያዊው ሲጓዝ ሳለ፣ ውሃ ወዳለበት ስፍራ ደረሱ፡፡ ኢትዮጵያዊውም፣ ‹‹እነሆ፣ በዚያ ቦታ ውሃ አለ! ልጠመቅን?›› አለ፡፡ ለነጂውም ሰረገላውን እንዲያቆመው ነገረው፡፡

Image

ስለዚህ ወደ ውሃው ወረዱ፣ ፊልጶስም ኢትዮጵያዊውን አጠመቀው። ከውሃው ከወጡ በኋላ መንፈስ ቅደስ በድንገት ፊልጶስን ወደ ሌላ ስፍራ ወሰደው፤ ስለ ኢየሱስ ለሰዎች መናገሩንም ቀጠለ።

Image

ኢትዮጵያዊው ኢየሱስን በማወቁ እየተደሰተ ወደ አገሩ ለመመለስ ጕዞውን ቀጠለ።

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከሐዋርያት ሥራ 6፡8-8፡5፤ 8፡26-40።