45. እስጢፋኖስ እና ፊሊጶስ

በጥንትዋ ቤተ ክርስቲያን ከነበሩት መሪዎች አንዱ እስጢፋኖስ ተብሎ የሚጠራ ሰው ነበር። እርሱ መልካም ስም ያለውና መንፈስ ቅዱስና ጥበብ የሞላበት ሰው ነበር። እስጢፋኖስ ብዙ ተአምራትን ያደረገና ሰዎች በኢየሱስ እንዲያምኑ በደንብ አስረድቶ ያሳምናቸው ነበር።

አንድ ቀን እስጢፋኖስ ስለ ኢየሱስ በሚያስተምርበት ጊዜ፣ በኢየሱስ ያላመኑ አንዳንድ አይሁዶች ከእስጢፋኖስ ጋር መከራከር ጀመሩ። በጣም ተቈጡና ስለ እስጢፋኖስ ለሃይማኖት መሪዎች ዋሽተው ተናገሩ። ‹‹ስለ ሙሴና ስለ እግዚአብሔር ክፉ ነገሮችን ሲናገር ሰምተነዋል!›› አሉ። ስለዚህ የሃይማኖት መሪዎቹ እስጢፋኖስን ያዙትና ወደ ሊቀ ካህናቱና ወደ ሌሎቹ የአይሁድ መሪዎች አምጥተው ሌሎች ተጨማሪ የሐሰት ምስክሮች ስለ እስጢፋኖስ ዋሽተው እንዲመሰክሩ አደረጉ።

ሊቀ ካህናቱ እስጢፋኖስን፣ ‹‹እነዚህ ነገሮች እውነት ናቸውን?›› ብሎ ጠየቀው፡፡ እስጢፋኖስ ከአብርሃም ዘመን ጀምሮ እስከ ኢየሱስ ዘመን ድረስ እግዚአብሔር ስላደረጋቸው ብዙ ታላላቅ ነገሮች፣ እንዲሁም የእግዚአብሔር ሕዝብ በተከታታይ በእርሱ ላይ ስለ ማመፃቸው በማስታወስ መልስ ሰጠ፡፡ ከዚያም እንዲህ አለ፣ ‹‹እናንተ አንገተ ደንዳኖችና ዓመፀኞች ልክ ቅድመ አያቶቻችሁ እግዚአብሔርን እንደ ተቃወሙትና ነቢያቱን እንደ ገደሉ ሁልጊዜ መንፈስ ቅዱስን ትቃወማላችሁ፡፡ እናንተ ግን ከእነርሱ ይልቅ የባሰ ክፉ ነገር አድርጋችኋል፡፡ መሲሑን ገድላችኋል!››

የሃይማኖት መሪዎቹ ይህንን በሰሙ ጊዜ፣ በጣም ተናደው ጆሮአቸውን ደፈኑና ከፍ ባለ ድምፅ ጮኹ። እስጢፋኖስን ከከተማይቱ ውጪ ጐተቱትና ሊገድሉት በድንጋይ ወገሩት።

እስጢፋኖስ በመሞት ላይ እያለ፣ ‹‹ኢየሱስ ሆይ፣ ነፍሴን ተቀበላት›› ብሎ ጮኸ። ከዚያም በጉልበቱ ተንበረከከና፣ ‹‹ጌታ ሆይ፣ ይህንን ኃጢአት አትቊጠርባቸው›› ብሎ እንደ ገና ጮኸ። ከዚያ በኋላ ሞተ።

ሳውል የተባለ አንድ ወጣት እስጢፋኖስን ከሚገድሉት ሰዎች ጋር ተስማምቶ በእርሱ ላይ ድንጋይ በሚወረውሩበት ጊዜ ልብሳቸውን ይጠብቅ ነበር። በዚያን ዕለት በኢየሩሳሌም የነበሩ ብዙ ሰዎች የኢየሱስን ተከታዮች ማሳደድ ጀመሩ፣ ስለዚህ አማኞቹ ወደ ሌሎች ስፍራዎች ሸሹ። ነገር ግን ስደቱ ቢኖርም እንኳ፣ በሄዱበት ስፍራ ሁሉ ስለ ኢየሱስ ሰበኩ።

ፊልጶስ የተባለ የኢየሱስ ደቀ መዝሙር በስደቱ ጊዜ ከኢየሩሳሌም ከሸሹት አማኞች አንዱ ነበር። ወደ ሰማርያ ሄዶ ስለ ኢየሱስ ሰበከና ብዙ ሰዎች ዳኑ። ከዚያ በኋላ አንድ ቀን ከእግዚአብሔር የተላከ መልአክ በምድረ በዳ ወዳለ አንድ መንገድ እንዲሄድ ለፊልጶስ ነገረው። ፊልጶስ በመንገዱ በመሄድ ላይ እያለ አንድ ትልቅ ኢትዮጵያዊ ባለ ሥልጣን በሰረገላው ሲሄድ ዐየ። ወደዚህ ሰው ሄዶ እንዲያነጋግረው መንፈስ ቅዱስ ለፊልጶስ ነገረው።

ፊልጶስ ወደ ሰረገለው በቀረበ ጊዜ፣ ኢትዮጵያዊው ነቢዩ ኢሳይያስ ከጻፈው ውስጥ አንዱን ክፍል ሲያነብ ሰማ፡፡ ሰውዬው እንዲህ ብሎ ሲያነብ ነበር፣ ‹‹እንደ በግ ወደ መታረድ ተነዳ፣ የበግ ጠቦትም በሸላቹ ፊት ዝም እንደሚል እንዲሁ አፉን አልከፈተም፡፡ በፍርድ ተወሰደ፣ አላከበሩትምም፡፡ ከሕያዋን ምድር አስወገዱት፡፡››

ፊልጶስ ኢትዮጵያዊውን፣ ‹‹የምታነበውን ታስተውለዋለህን?›› ብሎ ጠየቀው። ኢትዮጵያዊውም፣ ‹‹አይደለም። የሚያስረዳኝ ሰው ሳይኖር እንዴት ልረዳ እችላለሁ። እባክህን ናና ከጐኔ ተቀመጥ። ኢሳይያስ የጻፈው ስለ ራሱ ነውን ወይስ ስለ ሌላ ሰው?›› ብሎ መለሰ።

ኢሳይያስ የጻፈው ስለ ኢየሱስ መሆኑን ፊልጶስ ለኢትዮጵያዊው አብራራለት። ደግሞም ፊልጶስ ስለ ኢየሱስ የሚናገረውን የምሥራች ሲያስረዳው ሌሎች የእግዚአብሔር ቃል ክፍሎችን ተጠቀመ።

ፊልጶስና ኢትዮጵያዊው ሲጓዝ ሳለ፣ ውሃ ወዳለበት ስፍራ ደረሱ፡፡ ኢትዮጵያዊውም፣ ‹‹እነሆ፣ በዚያ ቦታ ውሃ አለ! ልጠመቅን?›› አለ፡፡ ለነጂውም ሰረገላውን እንዲያቆመው ነገረው፡፡

ስለዚህ ወደ ውሃው ወረዱ፣ ፊልጶስም ኢትዮጵያዊውን አጠመቀው። ከውሃው ከወጡ በኋላ መንፈስ ቅደስ በድንገት ፊልጶስን ወደ ሌላ ስፍራ ወሰደው፤ ስለ ኢየሱስ ለሰዎች መናገሩንም ቀጠለ።

ኢትዮጵያዊው ኢየሱስን በማወቁ እየተደሰተ ወደ አገሩ ለመመለስ ጕዞውን ቀጠለ።
የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከሐዋርያት ሥራ 6፡8-8፡5፤ 8፡26-40።