16. ነፃ አውጪዎቹ

ኢያሱ ከሞተ በኋላ፣ እስራኤላውያን እግዚአብሔርን አልታዘዙም፤ የቀሩትንም ከነዓናውያን ከመካከላቸው አላስወጡም፤ ወይም የእግዚአብሔርን ሕግ አልታዘዙም። እስራኤላውያን እውነተኛ አምላክ የሆነውን ያህዌን ከማምለክ ይልቅ የከነዓናውያንን አማልክት ማምለክ ጀመሩ። እስራኤላውያን ንጉሥ አልነበራቸውም፣ ስለዚህ እያንዳንዱ ትክክል መስሎ የሚታየውን ሁሉ ያደርግ ነበር።

እስራኤላውያን እግዚአብሔርን አለመታዘዛቸውን በመቀጠላቸው፣ እግዚአብሔር ጠላቶቻቸው እንዲያሸንፏቸው አደረገ። እነዚህ ጠላቶቻቸው የእስራኤላውያንን ሀብት ሁሉ ዘረፉ፣ንብረታቸውንም አወደሙ፣ አብዛኞቻቸውንም ገደሉ። እስራኤላውያን እግዚአብሔርን ባለመታዘዝና በጠላቶቻቸው በመጨቆን ብዙ ዘመናትን ካሳለፉ በኋላ፣ ንስሐ ገቡ፤ እግዚአብሔርንም ከጠላቶቻቸው እንዲያድናቸው ጠየቁ።

ከዚያም እግዚአብሔር ከጠላቶቻቸው የሚያድናቸውን ነፃ አውጪ ላከላቸው፤ ለምድሪቱም ሰላምን አመጣ። ነገር ግን ሰዎቹ እግዚአብሔርን እንደገና ረሱ። ጣዖትንም ማምለክ ጀመሩ፤ ስለ ሆነም እግዚአብሔር በአቅራቢያቸው የሚገኙትን ጠላቶቻቸውን ምድያማውያንን አስንሣባቸው፣ አሸነፉአቸውም።

ምድያማውያን የእስራኤላውያንን ሰብል ሁሉ ለሰባት ዓመታት ወሰዱ። እስራኤላውያን በጣም ፈርተው ስለ ነበር ምድማውያን እንዳያገኙአቸው፣ በየሸለቆውና በየዋሻው ይሸሽጉ ነበር። በመጨረሻም እንዲያድናቸው ወደ እግዚአብሔር ጮኹ።፡

አንድ ቀን፣ ጌዴዎን የሚባል እስራኤላዊ ምድያማውያን ሰብሉን እንዳይወስዱበት ተደብቆ እህል ይወቃ ነበር። የእግዚአብሔርም መልአክ ወደ ጌዴዎን መጥቶ እንዲህ አለው ‹‹አንተ ብርቱ ተዋጊ ሰው እግዚአብሔር ከአንተ ጋር ነው። ሂድና እስራኤልን ከምድያማውያን አድን።››

የጌዴዎን አባት ለጣዖት አምልኮ የተዘጋጀ መሠዊያ ነበረው። እግዚአብሔርም ጌዴዎንን ያንን መሠዊያ እንዲያፈርስ ተናገረው። ነገር ግን ጌዴዎን ሕዝቡን ስለ ፈራ እስኪመሽ ድረስ ጠበቀ። ከዚያም መሠዊያውን አፈራረሰው፤ እስኪደቅቅ ድረስም ሰባበረው። በአጠገቡም ለእግዚአብሔር ዐዲስ መሠዊያን አዘጋጀ። ለእግዚአብሔርም መሥዋዕትን ሠዋበት።

በማግስቱ ጠዋት ሕዝቡ አንድ ሰው መሠዊያቸውን እንዳፈራረሰው ተመልክተው እጅግ ተበሳጩ። ጌዴዎንን ለመግደል ወደ ጌዴዎን ቤት ሄዱ። ነገር ግን የጌዴዎን አባት ‹‹ለምን አምላካችሁን ለማገዝ ትሞክራላችሁ? እርሱ አምላክ ከሆነ ራሱን ይከላከል!›› አላቸው። ይህንንም ስላለ ሕዝቡ ጌዴዎንን አልገደሉትም።

ምድያማውያን አስራኤላውያንን ለመዝረፍ እንደ ገና መጡ። ቊጥራቸው እጅግ ብዙ ስለ ነበር ማንም ሊቈጥራቸው አይችልም ነበር። ጌዴዎንም ምድያማውያንን ለመውጋት እስራኤላውያንን ጠራ። እግዚአብሔር እርሱን ተጠቅሞ እስራኤልን ያድን እንደ ሆነ ለማረጋገጥ ጌዴዎን ሁለት ምልክቶችን ከእግዚአብሔር ጠየቀ።

የመጀመሪያው ምልክት፦የበግ ፀጉር በምድር ላይ አድርጎ የጠዋቱ ጤዛ በበግ ፀጉር ላይ ብቻ እንጂ በምድር ላይ እንዳይሆን ጠየቀ። እግዚአብሔርም እንደዚያው አደረገ። በሚቀጥለው ምሽት ጌዴዎን እግዚአብሔርን ፤ መሬቱ በጠዋቱ ጤዛ እንዲረጥብ ጨርቁ ግን ደረቅ እንዲሆን ጠየቀ። እግዚአብሔርም እንደዚያው አደረገ። እነዚህ ሁለቱ ምልክቶች እግዚአብሔር እርሱን ተጠቅሞ እስራኤልን ከምድያም እንደሚያድን ለጌዴዎን ማስረጃ ሆኑለት።

32,000 እስራኤላውያን ወታደሮች ወደ ጌዴዎን መጡ፣ ነገር ግን እግዚአብሔር ቊጥራቸው ብዙ ነው አለው። ስለዚህ ጌዴዎን መዋጋት የፈሩትን 22,000 ወታደሮችን ወደ ቤታቸው መለሳቸው። እግዚአብሔር ጌዴዎንን አሁንም የወታደሩ ቊጥር ብዙ ነው አለው። ስለሆነም ጌዴዎን 300 ወታደሮችን አስቀርቶ ሌሎቹን ወደ ቤታቸው መለሳቸው።

በዚያን ሌሊት እግዚአብሔር ጌዴዎንን ‹‹ወደ ምድያማውያን ጦር ሠፈር ውረድ፣ የሚሉትንም ስትሰማ ከዚያ በኋላ ፈጽሞ አትፈራቸውም›› አለው። ስለ ሆነም ጌዴዎን ወደ ምድያማውያን ጦር ሠፈር በዚያው ሌሊት ወርዶ አንድ የምድያም ወታደር ለጓደኛው በሕልሙ ያየውን ነገር ሲነገረው ሰማ፤ ጓደኛውም መልሶ “ይህ ሕልም የሚለው የጌድዎን ጦር ምድያማውያንን እንደሚያሸንፍ ነው” አለ። ጌዴዎን ይህን በሰማ ጊዜ ለእግዚአብሔር ሰገደ።

ከዚያም ጌዴዎን ወደ ወታደሮቹ ተመልሶ ለእያንዳንዳቸው ቀንደ መለከት፣ ማሰሮ እና ችቦ ሰጣቸው።እነሱም የምድያም ሠራዊት ተኝቶ እያለ ሰፍሮ የነበረበትን የጦር ሠፈር ከበቡ። የጌድዎን 300 ወታደሮች ችቦ በማሰሮው ውስጥ ይዘው ስለነበር የምድያም ወታደሮች የችቦውን ብርሃን ማየት አልቻሉም።

ከዚያም የጌዴዎን ወታሮች በሙሉ በተመሳሳይ ጊዜ ማሰሮዎቻቸውን ሰበሩ፤ ወዲያው የችቦው ብርሃን በድንገት አበራ። ቀንደ መለከታቸውን እየነፉ ‹‹የእግዚአብሔርና የጌዴዎን ሰይፍ›› እያሉ ጮኹ።

እግዚአብሔርም ምድያማውያንን ግራ አጋባቸው፣ እርስ በርሳቸውም ተገዳደሉ። ወዲያው በየቤታቸው ያሉ እስራኤላውያን ምድያማውያንን ለማባረር እንዲረዱ ተጠሩ። ብዙዎችን ምድማውያንን ገደሉ የተቀሩቱንም ከእስራኤል ምድር አባረሩ። በዚያን ቀን 120,000 የምድያም ሰዎች ሞቱ። እግዚአብሔርም እስራኤልን አዳነ።

ሕዝቡም ጌዴዎንን ንጉሣቸው እንዲሆን ፈለጉ። ጌዴዎን ግን ይህን እንዲያደርጉ አልፈቀደላቸውም፤ ነገር ግን እያንዳንዳቸው ከምድያማውያን የወሰዱአቸውን የወርቅ ቀለበት እንዲያመጡ ጠየቃቸው። ሕዝቡም ለጌዴዎን እጅግ ብዙ ወርቅ ሰጡት።

ጌዴዎንም ወርቁን አቅልጦ ሊቀ ካህኑ እንደሚለብሰው ልዩ ልብስ አድርጎ አሠራው። ነገር ግን ሕዝቡ ያንን ልብስ እንደ ጣዖት ሊያመልኩት ጀመሩ። ከዚያም የተነሣ እግዚአብሔር ጠላቶቻቸው እንዲያሸንፉአቸው አድርጎ ቀጣቸው። በመጨረሻም ሕዝቡ አሁንም እግዚአብሔር እንዲያድናቸው ጠየቁ፣ እግዚአብሔርም ሌላ አዳኝ ላከላቸው።

እንዲህ ያለው ሁኔታ ብዙ ጊዜ ተደጋገመ። እስራኤላውያን ኃጢአትን ያደርጋሉ፣ እግዚአብሔር ይቀጣቸዋል፣ እንደ ገና ንስሐ ይገባሉ፣ እግዚአብሔርም ያድናቸው ዘንድ አዳኝን ይልክላቸዋል። ለብዙ ዓመታት እግዚአብሔር እስራኤልን ከጠላቶቻቸው ለማዳን ብዙ ነፃ አውጪዎችን ልኮላቸዋል።

በመጨረሻም፣ ሕዝቡ እንደሌሎቹ ሁሉ አሕዛብ ንጉሥን እንዲሰጣቸው እግዚአብሔርን ጠየቁ። በጦርነት የሚመራቸው፣ ረጅምና ጠንካራ የሆነ ንጉሥ እንዲኖራቸው ፈለጉ። እግዚአብሔር ግን ይህንን ጥያቄአቸውን አልወደደም፣ ሆኖም እንደ ፈለጉት ንጉሥን ሰጣቸው።
__የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- መሳፍንት 1-5፣ 6-8፡፡