አማርኛ: Open Bible Stories

Updated ? hours ago # views See on DCS

32. ኢየሱስ ርኵስ መንፈስ የያዘውን ሰውና የታመመችውን ሴት ፈወሰ

Image

አንድ ቀን ኢየሱስና ደቀ መዛሙርቱ በጀልባ ሐይቁን አቋርጠው የጌርጌሴኖን ሰዎች ወደሚኖሩበት አካባቢ ሄዱ፡፡

Image

ወደ ሐይቁ ማዶ በደረሱ ጊዜ ርኵስ መንፈስ የያዘው ሰው ሮጦ ወደ ኢየሱስ መጣ፡፡

Image

ይህ ሰው ማንም ሊቈጣጠረው የማይችል እጅግ ብርቱ ነበረ፡፡ እንዲያውም ሰዎች እጆቹንና እግሮቹን በሰንሰለት አስረውት ነበር፣ ነገር ግን ሰንሰለቱን ይበጣጥስ ነበር፡፡

Image

ሰውዬው በአካባቢው ባሉ መቃብሮች መካከል ይኖር ነበር፡፡ ይህ ሰው ቀኑንና ሌሊቱን ሁሉ ይጮኽ ነበር፡፡ ልብስም አይለብስም ነበር፣ ሰውነቱንም በተደጋጋሚ በድንጋይ ይቧጭር ነበር፡፡

Image

ሰውዬው ወደ ኢየሱስ በመጣ ጊዜ፣ በፊቱ በጉልበቱ ወድቆ ሰገደለት፡፡ ኢየሱስ ርኵስ መንፈሱን፣ ‹‹ከዚህ ሰው ውጣ!›› አለው፡፡

Image

ርኵስ መንፈሱ ያለበት ሰው ከፍ ባለ ድምፅ ‹‹የልዑል እግዚአብሔር ልጅ ኢየሱስ ሆይ፣ ከእኔ ምን ትፈልጋለህ? እባክህን አታሠቃየኝ!›› ብሎ ከፍ ባለ ድምፅ ጮኸ፡፡ ከዚያም ኢየሱስ ርኵስ መንፈሱን፣ ‹‹ስምህ ማን ነው?›› ብሎ ጠየቀው፡፡ እርሱም፣ ‹‹ብዙዎች ነንና ስሜ ሌጌዎን ነው›› ብሎ መለሰ፡፡ (‹ሌጌዎን› በሮማ ጦር ሠራዊት ብዙ ሺህ ወታደሮችን የያዘ ክፍል ነበር፡፡)

Image

ርኵሳን መናፍስቱ፣ ‹‹እባክህን ከዚህ አካባቢ አታርቀን!›› ብለው ኢየሱስን ለመኑት፡፡ በአቅራቢያው ባለ ኮረብታ ላይ የእሪያ መንጋ ተሰማርቶ ነበር፡፡ ስለዚህ ርኵሳን መናፍስቱ ኢየሱስን፣ ‹‹እባክህን በዚህ ፈንታ ወደ እሪያዎቹ እንድንገባ ስደደን!›› ብለው ለመኑት፡፡ ኢየሱስ፣ ‹‹ሂዱ!›› አላቸው፡፡

Image

ርኵሳን መናፍስቱ ከሰውዬው ወጡና ወደ እሪያዎቹ ገቡ፡፡ እሪያዎቹ ከአፋፉ ቊልቊል ሮጡና በሐይቁ ሰጠሙ፡፡ በመንጋው 2,000 ያህል እሪያዎች ነበሩ፡፡

Image

እሪያዎቹን ይጠብቁ የነበሩት ሰዎች የሆነውን ነገር ባዩ ጊዜ ወደ ከተማ ሮጡና ኢየሱስ ያደረገውን ነገር ላገኙት ሰው ሁሉ ተናገሩ፡፡ የከተማው ሰዎች መጡና ርኵሳን መናፍስት የነበሩበትን ሰው ዐዩ፡፡ ልብሱን ለብሶ ጤናማ ሰው ሆኖ በጸጥታ ተቀምጦ ነበር፡፡

Image

ሰዎቹ በጣም ፈርተው ነበርና ኢየሱስን እንዲሄድ ጠየቁት፡፡ ስለዚህ ኢየሱስ ጀልባ ውስጥ ገባና ለመሄድ ተዘጋጀ፡፡ ርኵሳን መናፍስት የነበሩበት ሰውዬም ከኢየሱስ ጋር ለመሄድ ለመነው፡፡

Image

ነገር ግን ኢየሱስ፣ ‹‹አይደለም፣ ወደ ቤትህ ሄደህ እግዚአብሔር ስላደረገልህ ነገር ሁሉና እንዴት እንደ ማረህ ለወዳጆችህና ለቤተ ሰብህ እንድትነግር እፈልጋለሁ›› አለው፡፡

Image

ስለዚህ ሰውዬው ሄደና ኢየሱስ ስላደረገለት ነገር ለሁሉም ሰው ተናገረ፡፡ ታሪኩን የሰማ ሰው ሁሉ በአድናቆትና በአግራሞት ተሞላ፡፡

Image

ኢየሱስ ወደ ሐይቁ ማዶ ተመለሰ፡፡ እዚያ በደረሰ ጊዜ ብዙ ሕዝብ በዙሪያው ተሰበሰቡና አጨናነቁት፡፡ በሕዝቡ መካከል ለዐሥራ ሁለት ዓመት ደም ሲፈስባት የነበረች ሴት ነበረች፡፡ እንዲፈውሱአት ገንዘብዋን ሁሉ ለሐኪሞች ከፍላ ነበር፣ ነገር ግን ባሰባት እንጂ አልተፈወሰችም፡፡

Image

ኢየሱስ ብዙ በሽተኞችን እንደ ፈወሰ ሰምታ ነበርና፣ ‹‹የኢየሱስን ልብስ ብቻ ብዳስስ ያኔ እኔም እንደምፈወስ እርግጠኛ ነኝ!›› ብላ ዐሰበች፡፡ ስለዚህ ከኢየሱስ ኋላ መጣችና ልብሱን ዳሰሰች፡፡ ልብሱን እንደ ዳሰሰች ወዲያውኑ ደምዋ ቆመ!

Image

ወዲያውኑ፣ ኢየሱስ ኃይል ከእርሱ እንደ ወጣ ዐወቀ፡፡ ስለዚህ ወደ ኋላ ዞረና፣ ‹‹ማን ነው የዳሰሰኝ?›› ብሎ ጠየቀ፡፡ ደቀ መዛሙርቱ፣ ‹‹በዙሪያህ የተሰበሰቡና የሚያጋፉህ ብዙ ሰዎች አሉ፡፡ ለምን ‹ማን ዳሰሰኝ› ብለህ ትጠይቃለህ?›› ብለው መለሱለት፡፡

Image

ሴቲቱ በጣም ፈርታ እየተንቀጠቀጠች በኢየሱስ ፊት ተደፋች፡፡ ከዚያም ምን እንዳደረገችና እንደ ተፈወሰች ነገረችው፡፡ ኢየሱስም፣ ‹‹እምነትሽ አድኖሻል፡፡በሰላም ሂጂ›› አላት፡፡

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከማቴዎስ 8፡28-34፤ 9፡20-22፤ ማርቆስ 5፡1-20፤ 5፡24-34፤ ሉቃስ 8፡26-39፤ 8፡42-48፡፡