32. ኢየሱስ ርኵስ መንፈስ የያዘውን ሰውና የታመመችውን ሴት ፈወሰ

አንድ ቀን ኢየሱስና ደቀ መዛሙርቱ በጀልባ ሐይቁን አቋርጠው የጌርጌሴኖን ሰዎች ወደሚኖሩበት አካባቢ ሄዱ፡፡

ወደ ሐይቁ ማዶ በደረሱ ጊዜ ርኵስ መንፈስ የያዘው ሰው ሮጦ ወደ ኢየሱስ መጣ፡፡

ይህ ሰው ማንም ሊቈጣጠረው የማይችል እጅግ ብርቱ ነበረ፡፡ እንዲያውም ሰዎች እጆቹንና እግሮቹን በሰንሰለት አስረውት ነበር፣ ነገር ግን ሰንሰለቱን ይበጣጥስ ነበር፡፡

ሰውዬው በአካባቢው ባሉ መቃብሮች መካከል ይኖር ነበር፡፡ ይህ ሰው ቀኑንና ሌሊቱን ሁሉ ይጮኽ ነበር፡፡ ልብስም አይለብስም ነበር፣ ሰውነቱንም በተደጋጋሚ በድንጋይ ይቧጭር ነበር፡፡

ሰውዬው ወደ ኢየሱስ በመጣ ጊዜ፣ በፊቱ በጉልበቱ ወድቆ ሰገደለት፡፡ ኢየሱስ ርኵስ መንፈሱን፣ ‹‹ከዚህ ሰው ውጣ!›› አለው፡፡

ርኵስ መንፈሱ ያለበት ሰው ከፍ ባለ ድምፅ ‹‹የልዑል እግዚአብሔር ልጅ ኢየሱስ ሆይ፣ ከእኔ ምን ትፈልጋለህ? እባክህን አታሠቃየኝ!›› ብሎ ከፍ ባለ ድምፅ ጮኸ፡፡ ከዚያም ኢየሱስ ርኵስ መንፈሱን፣ ‹‹ስምህ ማን ነው?›› ብሎ ጠየቀው፡፡ እርሱም፣ ‹‹ብዙዎች ነንና ስሜ ሌጌዎን ነው›› ብሎ መለሰ፡፡ (‹ሌጌዎን› በሮማ ጦር ሠራዊት ብዙ ሺህ ወታደሮችን የያዘ ክፍል ነበር፡፡)

ርኵሳን መናፍስቱ፣ ‹‹እባክህን ከዚህ አካባቢ አታርቀን!›› ብለው ኢየሱስን ለመኑት፡፡ በአቅራቢያው ባለ ኮረብታ ላይ የእሪያ መንጋ ተሰማርቶ ነበር፡፡ ስለዚህ ርኵሳን መናፍስቱ ኢየሱስን፣ ‹‹እባክህን በዚህ ፈንታ ወደ እሪያዎቹ እንድንገባ ስደደን!›› ብለው ለመኑት፡፡ ኢየሱስ፣ ‹‹ሂዱ!›› አላቸው፡፡

ርኵሳን መናፍስቱ ከሰውዬው ወጡና ወደ እሪያዎቹ ገቡ፡፡ እሪያዎቹ ከአፋፉ ቊልቊል ሮጡና በሐይቁ ሰጠሙ፡፡ በመንጋው 2,000 ያህል እሪያዎች ነበሩ፡፡

እሪያዎቹን ይጠብቁ የነበሩት ሰዎች የሆነውን ነገር ባዩ ጊዜ ወደ ከተማ ሮጡና ኢየሱስ ያደረገውን ነገር ላገኙት ሰው ሁሉ ተናገሩ፡፡ የከተማው ሰዎች መጡና ርኵሳን መናፍስት የነበሩበትን ሰው ዐዩ፡፡ ልብሱን ለብሶ ጤናማ ሰው ሆኖ በጸጥታ ተቀምጦ ነበር፡፡

ሰዎቹ በጣም ፈርተው ነበርና ኢየሱስን እንዲሄድ ጠየቁት፡፡ ስለዚህ ኢየሱስ ጀልባ ውስጥ ገባና ለመሄድ ተዘጋጀ፡፡ ርኵሳን መናፍስት የነበሩበት ሰውዬም ከኢየሱስ ጋር ለመሄድ ለመነው፡፡

ነገር ግን ኢየሱስ፣ ‹‹አይደለም፣ ወደ ቤትህ ሄደህ እግዚአብሔር ስላደረገልህ ነገር ሁሉና እንዴት እንደ ማረህ ለወዳጆችህና ለቤተ ሰብህ እንድትነግር እፈልጋለሁ›› አለው፡፡

ስለዚህ ሰውዬው ሄደና ኢየሱስ ስላደረገለት ነገር ለሁሉም ሰው ተናገረ፡፡ ታሪኩን የሰማ ሰው ሁሉ በአድናቆትና በአግራሞት ተሞላ፡፡

ኢየሱስ ወደ ሐይቁ ማዶ ተመለሰ፡፡ እዚያ በደረሰ ጊዜ ብዙ ሕዝብ በዙሪያው ተሰበሰቡና አጨናነቁት፡፡ በሕዝቡ መካከል ለዐሥራ ሁለት ዓመት ደም ሲፈስባት የነበረች ሴት ነበረች፡፡ እንዲፈውሱአት ገንዘብዋን ሁሉ ለሐኪሞች ከፍላ ነበር፣ ነገር ግን ባሰባት እንጂ አልተፈወሰችም፡፡

ኢየሱስ ብዙ በሽተኞችን እንደ ፈወሰ ሰምታ ነበርና፣ ‹‹የኢየሱስን ልብስ ብቻ ብዳስስ ያኔ እኔም እንደምፈወስ እርግጠኛ ነኝ!›› ብላ ዐሰበች፡፡ ስለዚህ ከኢየሱስ ኋላ መጣችና ልብሱን ዳሰሰች፡፡ ልብሱን እንደ ዳሰሰች ወዲያውኑ ደምዋ ቆመ!

ወዲያውኑ፣ ኢየሱስ ኃይል ከእርሱ እንደ ወጣ ዐወቀ፡፡ ስለዚህ ወደ ኋላ ዞረና፣ ‹‹ማን ነው የዳሰሰኝ?›› ብሎ ጠየቀ፡፡ ደቀ መዛሙርቱ፣ ‹‹በዙሪያህ የተሰበሰቡና የሚያጋፉህ ብዙ ሰዎች አሉ፡፡ ለምን ‹ማን ዳሰሰኝ› ብለህ ትጠይቃለህ?›› ብለው መለሱለት፡፡

ሴቲቱ በጣም ፈርታ እየተንቀጠቀጠች በኢየሱስ ፊት ተደፋች፡፡ ከዚያም ምን እንዳደረገችና እንደ ተፈወሰች ነገረችው፡፡ ኢየሱስም፣ ‹‹እምነትሽ አድኖሻል፡፡በሰላም ሂጂ›› አላት፡፡
የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከማቴዎስ 8፡28-34፤ 9፡20-22፤ ማርቆስ 5፡1-20፤ 5፡24-34፤ ሉቃስ 8፡26-39፤ 8፡42-48፡፡