44. ጴጥሮስና ዮሐንስ ይለምን የነበረውን ሰው ፈወሱ

አንድ ቀን ጴጥሮስና ዮሐንስ ወደ ቤተ መቅደስ እየሄዱ ሳሉ፣ ወደ ቤተ መቅደሱ ደጃፍ እንደ ቀረቡ፣ ገንዘብ ይለምን የነበረ ሽባ ሰው ዐዩ።

ጴጥሮስ ሽባውን ተመለከተውና፣ ‹‹የምሰጥህ ምንም ገንዘብ የለኝም። ያለኝን ግንእሰጥሃለሁ። በኢየሱስ ስም ተነሣና ተመላለስ!›› አለው።

ወዲያውኑ እግዚአብሔር ሽባውን ሰው ፈወሰው፣ እርሱም መራመድና መዝለል፣ እግዚአብሔርንም ማመስገን ጀመረ። በቤተ መቅደሱ አጥር ግቢ የነበሩት ሰዎችም ተደነቁ።

ሕዝቡም የተፈወሰውን ሰው ለማየት ፈጥነው ተሰበሰቡ፡፡ ጴጥሮስ እንዲህ አላቸው፣ ‹‹ይህ ሰው ስለ ተፈወሰ ለምን ትደነቃላችሁ? በገዛ ኃይላችን ወይም በበጎነታችን አልፈወስነውም፡፡ ይህንን ሰው የፈወሰው የኢየሱስ ኃይልና ኢየሱስ የሚሰጠው እምነት ነው፡፡››

‹‹ኢየሱስን እንዲገድለው ለሮማው ገዥ የነገራችሁት እናንተ ናችሁ። የሕይወትን ራስ ገደላችሁት፣ እግዚአብሔር ግን ከሙታን አስነሣው። ታደርጉት የነበረውን ነገር ባትረዱም እንኳ፣ መሲሑ መከራ እንደሚቀበልና እንደሚሞት የተነገሩትን ትንቢቶች ለመፈጸም እግዚአብሔር በድርጊቶቻችሁ ተጠቀመ። ስለዚህ ኃጢአታችሁ ይታጠብላችሁ ዘንድ አሁን ንስሐ ግቡና ወደ እግዚአብሔር ተመለሱ።››

የቤተ መቅደሱ መሪዎች ጴጥሮስና ዮሐንስ ይናገሩት በነበረው ነገር በጣም ተበሳጩ። ስለዚህ ያዙአቸውና እስር ቤት አስገቡአቸው። ነገር ግን ብዙ ሰዎች የጴጥሮስን መልእክት አመኑ፣ በኢየሱስ ያመኑት ሰዎች ቊጥርም ወደ 5,000 ገደማ ዐደገ።

በማግስቱ፣ የአይሁድ መሪዎች ጴጥሮስንና ዮሐንስን ወደ ሊቀ ካህናቱና ወደ ሌሎቹ የሃይማኖት መሪዎች አመጡአቸው። ጴጥሮስንና ዮሐንስን፣ ‹‹ይህንን ሽባ ሰው በምን ኃይል ፈወሳችሁት?›› ብለው ጠየቁአቸው።

ጴጥሮስ እንዲህ ብሎ መለሰላቸው፣ ‹‹ይህ ሰው በመሲሑ በኢየሱስ ኃይል ተፈውሶ በፊታችሁ ቆሞአል። እናንተ ኢየሱስን ሰቀላችሁት፣ እግዚአብሔር ግን እንደ ገና ሕያው አድርጎ ከሙታን አስነሣው! እናንተ አልተቀበላችሁትም፣ ነገር ግን በኢየሱስ ኃይል ካልሆነ በቀር ሌላ የመዳን መንገድ የለም!››

ጴጥሮስና ዮሐንስ በጣም በድፍረት በመናገራቸው እነዚህ መሪዎች ደነገጡ፣ ምክንያቱም እነዚህ ሰዎች ያልተማሩ ተራ ሰዎች መሆናቸውን አይተው ነበር። ነገር ግን እነዚህ ሰዎች ከኢየሱስ ጋር እንደ ነበሩ አስታወሱ። ጴጥሮስንና ዮሐንስን ካስጠነቀቁአቸው በኋላ፣ እንዲሄዱ አሰናበቱአቸው።
የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከሐዋርያት ሥራ 3፡1-4፡22።