አማርኛ: Open Bible Stories

Updated ? hours ago # views See on DCS

44. ጴጥሮስና ዮሐንስ ይለምን የነበረውን ሰው ፈወሱ

Image

አንድ ቀን ጴጥሮስና ዮሐንስ ወደ ቤተ መቅደስ እየሄዱ ሳሉ፣ ወደ ቤተ መቅደሱ ደጃፍ እንደ ቀረቡ፣ ገንዘብ ይለምን የነበረ ሽባ ሰው ዐዩ።

Image

ጴጥሮስ ሽባውን ተመለከተውና፣ ‹‹የምሰጥህ ምንም ገንዘብ የለኝም። ያለኝን ግንእሰጥሃለሁ። በኢየሱስ ስም ተነሣና ተመላለስ!›› አለው።

Image

ወዲያውኑ እግዚአብሔር ሽባውን ሰው ፈወሰው፣ እርሱም መራመድና መዝለል፣ እግዚአብሔርንም ማመስገን ጀመረ። በቤተ መቅደሱ አጥር ግቢ የነበሩት ሰዎችም ተደነቁ።

Image

ሕዝቡም የተፈወሰውን ሰው ለማየት ፈጥነው ተሰበሰቡ፡፡ ጴጥሮስ እንዲህ አላቸው፣ ‹‹ይህ ሰው ስለ ተፈወሰ ለምን ትደነቃላችሁ? በገዛ ኃይላችን ወይም በበጎነታችን አልፈወስነውም፡፡ ይህንን ሰው የፈወሰው የኢየሱስ ኃይልና ኢየሱስ የሚሰጠው እምነት ነው፡፡››

Image

‹‹ኢየሱስን እንዲገድለው ለሮማው ገዥ የነገራችሁት እናንተ ናችሁ። የሕይወትን ራስ ገደላችሁት፣ እግዚአብሔር ግን ከሙታን አስነሣው። ታደርጉት የነበረውን ነገር ባትረዱም እንኳ፣ መሲሑ መከራ እንደሚቀበልና እንደሚሞት የተነገሩትን ትንቢቶች ለመፈጸም እግዚአብሔር በድርጊቶቻችሁ ተጠቀመ። ስለዚህ ኃጢአታችሁ ይታጠብላችሁ ዘንድ አሁን ንስሐ ግቡና ወደ እግዚአብሔር ተመለሱ።››

Image

የቤተ መቅደሱ መሪዎች ጴጥሮስና ዮሐንስ ይናገሩት በነበረው ነገር በጣም ተበሳጩ። ስለዚህ ያዙአቸውና እስር ቤት አስገቡአቸው። ነገር ግን ብዙ ሰዎች የጴጥሮስን መልእክት አመኑ፣ በኢየሱስ ያመኑት ሰዎች ቊጥርም ወደ 5,000 ገደማ ዐደገ።

Image

በማግስቱ፣ የአይሁድ መሪዎች ጴጥሮስንና ዮሐንስን ወደ ሊቀ ካህናቱና ወደ ሌሎቹ የሃይማኖት መሪዎች አመጡአቸው። ጴጥሮስንና ዮሐንስን፣ ‹‹ይህንን ሽባ ሰው በምን ኃይል ፈወሳችሁት?›› ብለው ጠየቁአቸው።

Image

ጴጥሮስ እንዲህ ብሎ መለሰላቸው፣ ‹‹ይህ ሰው በመሲሑ በኢየሱስ ኃይል ተፈውሶ በፊታችሁ ቆሞአል። እናንተ ኢየሱስን ሰቀላችሁት፣ እግዚአብሔር ግን እንደ ገና ሕያው አድርጎ ከሙታን አስነሣው! እናንተ አልተቀበላችሁትም፣ ነገር ግን በኢየሱስ ኃይል ካልሆነ በቀር ሌላ የመዳን መንገድ የለም!››

Image

ጴጥሮስና ዮሐንስ በጣም በድፍረት በመናገራቸው እነዚህ መሪዎች ደነገጡ፣ ምክንያቱም እነዚህ ሰዎች ያልተማሩ ተራ ሰዎች መሆናቸውን አይተው ነበር። ነገር ግን እነዚህ ሰዎች ከኢየሱስ ጋር እንደ ነበሩ አስታወሱ። ጴጥሮስንና ዮሐንስን ካስጠነቀቁአቸው በኋላ፣ እንዲሄዱ አሰናበቱአቸው።

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከሐዋርያት ሥራ 3፡1-4፡22።