11. ፋሲካ

ፈርዖን እስራኤላውያንን ካልለቀቀ የግብፃውያን ሰዎችና የእንስሳቶቻቸውን መጀመሪያ የተወለዱትን ወንዶች ሁሉ እንደሚገድል እግዚአብሔር ፈርዖንን አስጠነቀቀው። ፈርዖን ይህን ቢሰማም እንኳ፣ አሁንም ማመንና ለእግዚአብሔር መታዘዝ እምቢ አለ።

እግዚአብሔር በእርሱ ያመነ የማንኛውንም ሰው የመጀመሪያ ወንድ ልጅን ለማዳን መንገድ አዘጋጀ። እያንዳንዱ ቤተ ሰብ ፍጹም የሆነ የበግ ጠቦት መርጦ እንዲያርድ አዘዘ።

እግዚአብሔር ለእስራኤላውያን የጠቦቱን ደም በቤታቸው በር ላይ እንዲቀቡት፣ ሥጋውንም ጠብሰው ያለ እርሾ ከተጋገረው ቂጣ ጋር በፍጥነት እንዲበሉት ነገራቸው። ደግሞ በበሉት ጊዜ ከግብፅ ለመውጣት እንዲዘጋጁ ነገራቸው።

እስራኤላውያን ልክ እግዚአብሔር እንዲያደርጉ እንዳዘዛቸው ሁሉንም ነገር አደረጉ። እኩለ ሌሊት ላይ እግዚአብሔር በመላው ግብፅ አልፎ መጀመሪያ የተወለደውን ወንድ ሁሉ ገደለ።

የእስራኤላውያን ቤቶች ሁሉ በሮቻቸው ደም ተቀብተው ነበር፣ ስለዚህ እግዚአብሔር በቤቶቹ አለፈ። በቤቶቹ ውስጥ የነበረው ሁሉ ከሞት ተረፈ። እስራኤላውያን በጠቦቱ ደም ምክንያት ዳኑ።

ግብፃውያን ግን በእግዚአብሔር አላመኑም፣ ትእዛዛቱንም አልፈጸሙም። ስለዚህ እግዚአብሔር በቤቶቻቸው አላለፈም። እግዚአብሔር የግብፃውያንን በመጀመሪያ የተወለዱ ወንዶችን በሙሉ ገደለ።

በእስር ቤት ካለው በኵር ልጅ ጀምሮ እስከ ፈርዖን በኩር ልጅ ድረስ የግብፃዊያን የመጀመሪያ ወንድ ልጅ በሙሉ ሞተ። ከጥልቅ ሐዘናቸው የተነሣ በግብፅ የነበሩ ሰዎች ሁሉ ያለቅሱና ይጮኹ ነበር።

በዚያው ሌሊት ፈርዖን ሙሴንና አሮንን ጠርቶ፣ “እስራኤላውያንን ይዛችሁ አሁኑኑ ከግብፅ ውጡ” አላቸው። ግብፃውያንም እስራኤላውያን በፍጥነት ከግብፅ እንዲወጡ አስቸኰሉአቸው።
የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከዘጸአት 11፡1-12፡32፡፡