19. ነቢያቱ

እግዚአብሔር በእስራኤላውያን ታሪክ በሙሉ ነቢያትን ይልክላቸው ነበር፡፡ ነቢያቱም መልእክትን ከእግዚአብሔር ሰምተው ለሕዝቡ ይነግሩ ነበር፡፡

አክአብ በእስራኤል መንግሥት ላይ በነገሠ ጊዜ ኤልያስ ነቢይ ነበረ፡፡ አክዓብ በኣል ተብሎ የሚጠራ የሐሰት አምላክ እንዲያመልኩ ሕዝቡን ያደፋፈረ ክፉ ሰው ነበር፡፡ ኤልያስ ለአክዓብ፣ ‹‹እኔ እንዲዘንብ እስከምናገር ድረስ በእስራኤል ዝናብ ወይም ጠል አይኖርም›› አለው፡፡ ይህ አክዓብን በጣም አስቈጣው፡፡

አክዓብ ኤልያስን ሊገድለው ይፈልግ ስለ ነበር እግዚአብሔር ኤልያስን ይሸሸግ ዘንድ በምድረ በዳ ወዳለ ምንጭ እንዲሄድ ነገረው። በየጠዋቱና በየምሽቱ ወፎች እንጀራና ሥጋ ያመጡለት ነበር። አክዓብና ጦር ሠራዊቱ ኤልያስን ፈለጉት፣ ነገር ግን ሊያገኙት አልቻሉም። ድርቁ በጣም ከባድ ስለነበር በመጨረሻ ምንጩ ደረቀ።

ስለዚህ ኤልያስ ወደ አንድ ጐረቤት አገር ሄደ። በዚያችም አገር በድርቁ ምክንያት ረሃብ ስለነበር አንዲት መበለትና ወንድ ልጅዋ ምግብ ሊያልቅባቸው ተቃርበው ነበር። ነገር ግን ኤልያስን ተንከባከቡት፣ ስለሆነም እግዚአብሔር ዱቄቱ ከማድጋ ዘይቱም ከማሰሮ እንዳይጐድል አድርጎ መገባቸው። በረሀቡ ጊዜ ሁሉ ምግብ ነበራቸው። ኤልያስ በዚያ ለረዥም ጊዜ ተቀመጠ።

ከሦስት ዓመት ተኩል በኋላ ኤልያስ ወደ እስራኤል መንግሥት ተመልሶ ዝናብ እንደሚዘንብ ለአክዓብ እንዲነግረው እግዚአብሔር ለኤልያስ ነገረው። አክዓብ ኤልያስን ባየው ጊዜ፣ ‹‹አንተ ችግር ፈጣሪ፣ አለህ እንዴ!›› አለው። ኤልያስ እንዲህ ብሎ መለሰት፣ ‹‹ችግር ፈጣሪ አንተ ነህ እንጂ እኔ አይደለሁም! እውነተኛውን አምላክ፣ ያህዌን ትተህ፣ በኣልን አምልከሃል፤ የእስራኤልን መንግሥት ሕዝብ ሁሉ በቀርሜሎስ ተራራ ላይ ሰብስብ።››

450ዎቹ የበኣል ነቢያትን ጨምሮ የእስራኤል መንግሥት ሕዝብ ሁሉ ወደ ቀርሜሎስ ተራራ መጡ፡፡ ኤልያስም ለሕዝቡ፣ ‹‹ስንት ጊዜ ዐሳባችሁን ትለውጣላችሁ? እግዚአብሔር አምላክ ከሆን እርሱን አገልግሉ! በኣል አምላክ ከሆን እርሱን አገልግሉ!›› አላቸው፡፡

ከዚያም ኤልያስ ለበኣል ነቢያት፣ ‹‹አንድ ወይፈን እረዱና መሥዋዕት አድርጋችሁ አቅርቡት፣ ነገር ግን እሳት አታንድዱ፡፡ እኔም እንደዚሁ አደርጋለሁ፡፡ በእሳት የሚመልስ አምላክ እርሱ እውነተኛ አምላክ ነው›› አላቸው፡፡ ስለዚህ የበኣል ካህናት መሥዋዕት አዘጋጁ፤ ነገር ግን እሳት አላነደዱም፡፡

ከዚያ በኋላ የበኣል ነቢያት ‹‹በኣል ሆይ፣ ስማን!›› ብለው ወደ በኣል ጸለዩ። ቀኑን ሙሉ ጸለዩ፣ ጮኹ፣ እንዲሁም ሰውነታቸውን በቢላዋ ቈረጡ፣ ነገር ግን መልስ አልነበረም።

በቀኑ መጨረሻ፣ ኤልያስ ለእግዚአብሔር መሥዋዕት አዘጋጀ፡፡ ከዚያም ሥጋው፣ እንጨቱ፣ እንዲሁም በመሠዊያው ዙሪያ ያለው መሬት እንኳ ሳይቀር ፍጹም እስኪረጥብ ድረስ ዐሥራ ሁለት ጋን ሙሉ ውሃ በመሥዋዕቱ ላይ እንዲያፈሱ ለሕዝብ ነገራቸው፡፡

ከዚያም ኤልያስ እንዲህ ብሎ ጸለየ፣ ‹‹ያህዌ፣ የአብርሃም፣ የይስሐቅና የያዕቆብ አምላክ፣ አንተ የእስራኤል አምላክ እንደ ሆንክና እኔም አገልጋይህ እንደ ሆንኩ ዛሬ ዐሳየን። አንተ እውነተኛ አምላክ እንደ ሆንክ ይህ ሕዝብ ያውቅ ዘንድ መልስልኝ›› አለ።

ወዲያውኑ፣ እሳት ከሰማይ ወደቀና ሥጋውን፣ እንጨቱን፣ ድንጋዩን፣ ቈሻሻውን፣ እንዲሁም በመሠዊያው ዙሪያ የነበረውን ውሃ እንኳ ሳይቀር አቃጠለ፡፡ ሕዝቡ ይህን ባዩ ጊዜ መሬት ላይ ወደቁና ‹‹ያህዌ አምላክ ነው! ያህዌ አምላክ ነው!›› አሉ፡፡

ከዚያም ኤልያስ፣ ‹‹ከበኣል ነቢያት አንድም እንዳያመልጥ!›› አለ። ስለዚህ ሕዝቡ የበኣልን ነቢያት ያዙና ወስደው ገደሉአቸው።

ከዚያ በኋላ ኤልያስ ለንጉሥ አክዓብ፣ ‹‹ዝናብ መጥቶአልና ፈጥነህ ወደ ከተማ ተመለስ›› አለው፡፡ ወዲያውኑ ሰማዩ ጠቈረ፣ ከባድ ዝናብም መዝነብ ጀመረ፡፡ ያህዌ ድርቁን አቆመው፤ እውተኛ አምላክ መሆኑንም አረጋገጠ፡፡

ከኤልያስ ዘመን በኋላ፣ እግዚአብሔር ነቢይ እንዲሆን ኤልሳዕ የተባለ ሰውን መረጠ። እግዚአብሔር በኤልሳዕ በኩል ብዙ ተአምራትን አደረገ። ከተአምራቱ አንዱ አስከፊ የቆዳ በሽታ በያዘው የጠላት ጦር ሠራዊት አዛዥ በነበረው ንዕማን ላይ ተከሠተ። ስለ ኤልሳዕ ሰምቶ ነበርና ስለዚህ እንዲፈውሰው ኤልሳዕን ሄዶ ጠየቀው። ኤልሳዕ በዮርዳኖስ ወንዝ ሰባት ጊዜ ብቅ ጥልቅ እንዲል ለንዕማን ነገረው።

በመጀመሪያ ንዕማን ተቈጣና ሞኝነት ስለ መሰለው ኤልሳዕ የነገረውን ነገር አላደረገውም። በኋላ ግን ዐሳቡን ለወጠና በዮርዳኖስ ወንዝ ሰባት ጊዜ ብቅ ጥልቅ አለ። በመጨረሻ ከውሃው በወጣ ጊዜ ቆዳው ፍጹም ተፈወሰ! እግዚአብሔር ፈወሰው።

እግዚአብሔር ሌሎች ብዙ ነቢያትን ላከ፡፡ ሁላቸውም ለሕዝቡ ጣዖታትን ማምለክ እንዲያቆሙና ለሌሎች ፍትሕንና ምሕረትን ማሳየት እንዲጀምሩ ነገሩአቸው፡፡ ነቢያቱ ሕዝቡ ክፉ መሥራትን ባያቆሙና ለእግዚአብሔር መታዘዝ ባይጀምሩ፣ እግዚአብሔር በበደለኝነት እንደሚፈርድባቸውና፣ እንደሚቀጣቸውም አስጠነቀቁአቸው፡፡

አብዛኛውን ጊዜ ሕዝቡ ለእግዚአብሔር አልታዘዙም። ብዙውን ጊዜ ለነቢያት የነበራቸው አያያዝ መጥፎ ነበረ፣ አንዳንድ ጊዜ እንዳውም ይገድሉአቸው ነበር። በአንድ ወቅት፣ ነቢዩ ኤርምያስ ደረቅ በሆነ የውሃ ጕድጓድ ውስጥ ተጥሎ በዚያ እንዲሞት ተትቶ ነበር። በጕድጓዱ መጨረሻ በነበረው ጭቃ ውስጥ እየሰመጠ ነበር፣ ነገር ግን ንጉሡ ራራለትና ከመሞቱ በፊት ከጕድጓዱ ጐትተው እንዲያወጡት አገልጋዮቹን አዘዛቸው።

ነቢያቱ ሕዝቡ ቢጡሉአቸውም እንኳ ስለ እግዚአብሔር መናራቸውን ቀጠሉ፡፡ ንስሐ ባይገቡ እግዚአብሔር እንደሚያጠፋቸው ሕዝቡን አስጠነቀቁአቸው፡፡ ደግሞም የእግዚአብሔር መሲሕ እንደሚመጣ ስለተሰጠው ተስፋ ሕዝቡን አስታወቋቸው፡፡
የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከ1ኛ ነገሥት 16-18፤ 2ኛ ነገሥት 5፤ ኤርምያስ 38፡፡