12. የእስራኤላውያን ከግብፅ መውጣት

እስራኤላውያን ከግብፅ በመውጣታቸው በጣም ደስ አላቸው። ከእንግዲህ ባሪያዎች አይደሉም፣ ወደ ተስፋዪቱ ምድርም በመጓዝ ላይ ናቸው። ግብፃውያን ለእስራኤላውያን ወርቅና ብር ሌሎችም የከበሩ ነገሮች ሳይቀሩ የጠየቁትን ማንኛውንም ነገር ሰጡአቸው። እስሬላውያን ከግብፅ ሲወጡ ከሌሎች ብሔሮች የሆኑ አንዳንድ ሰዎች በእግዚአብሔር አምነው ከእስራኤላውያን ጋር ከግብፅ ወጡ።

እግዚአብሔርም ቀን ረጅም በሆነ የደመና ዓምድ፣ ማታ ደግሞ ረጅም የሆነ የእሳት ዓምድ ከፊት ከፊታቸው እንዲሄድ እያደረገ መራቸው። እግዚአብሔር ሁልጊዜ ከእነርሱ ጋር በመሆን ሲጓዙ መራቸው።እነርሱ ማድረግ ያለባቸው ነገር ቢኖር እርሱን መከተል ብቻ ነበር።

ከጥቂት ጊዜ በኋላ፣ ፈርዖንና ሕዝቡ ዐሳባቸውን ቀይረው እስራኤላውያን እንደ ገና የእነርሱ ባሪያዎች እንዲሆኑ ፈለጉ። እግዚአብሔር ብቸኛው እውነተኛ አምላክ መሆኑን ሕዝቡ እንዲያዩ፣ እንዲሁም እርሱ፣ ያሕዌ፣ ከፈርዖንና ከአማልክቱ የበለጠ ኃያል እንደ ሆነ ይረዱ ዘንድ የፈርዖንን ልብ አደነደነው።

ስለዚህ ፈርዖንና ጦር ሠራዊቱ እንደ ገና ባሪያዎቻቸው ሊያደርጉአቸው እስራኤላውያንን አሳደዱአቸው። እስራኤላውያን የግብፅ ጦር ሠራዊት ሲመጣ ባዩ ጊዜ፣ በፈርዖን ጦር ሠራዊትና በቀይ ባሕር መካከል እንደ ተጠመዱ ዐወቁ። በጣም ፈርተው ስለ ነበር፣ ‹‹ከግብፅ ለምን ወጣን? መሞታችን ነው!›› ብለው ጮኹ።

ሙሴ እስራኤላውያንን፣ ‹‹አትፍሩ! ዛሬ እግዚአብሔር ስለ እናንተ ተዋግቶ ያድናችኋል›› ብሎ ነገራቸው። ከዚያም እግዚአብሔር፣ለሙሴ ‹‹ሕዝቡ ወደ ቀይ ባሕር እንዲንቀሳቀሱ ንገራቸው››አለ።

ከዚያም ግብፃውያን እስራኤላውያንን ማየት እንዳይችሉ እግዚአብሔር የደመናውን ዓምድ በእስራኤላውያንና በግብፃውያን መካከል አደረገው።

እግዚአብሔርም ለሙሴ በባሕሩ ላይ እጁን እንዲዘረጋና ውሃውን እንዲከፍለው ነገረው። ከዚያም እግዚአብሔር በባሕሩ መካከል መተላለፊያ መንገድ ይኖር ዘንድ ነፋስ ውሃውን ወደ ግራና ወደ ቀኝ እንዲገፋ አደረገ።

እስራኤላውያንም ውሃው በግራና በቀኛቸው እንደ ግድግዳ ሆኖላቸው በባሕሩ መካከል በደረቅ መሬት ላይ ተጓዙ።

ከዚያም እግዚአብሔር እስራኤላውያን እያመለጡ መሆናቸውን ግብፃውያኑ ያዩ ዘንድ የደመናውን አምድ ከመንገዱ ወደ ላይ አነሳው። ግብፃውያንም ከኋላቸው ሊያሳድዱአቸው ወሰኑ።

ስለዚህ በባሕሩ መካከል ውስጥ ባለው መንገድ እስራኤላውያንን ተከተሉአቸው፣ ነገር ግን እግዚአብሔር ግብፃውያን እንዲርበተበቱና ሰረገሎቻቸውም እንዳይንቀሳቀሱ አደረገ።ግብፃውያንም “ለነፍሳቸው ሽሹ! እግዚአብሔር ለእስራኤላውያን እየተዋጋላቸው ነው!” ብለው ጮኹ።

እስራኤላውያን ሁሉ ባሕሩን በደኅና ከተሻገሩ በኋላ፣ እግዚአብሔር እንደ ገና እጁን እንዲዘረጋ ለሙሴ ነገረው። እርሱም እግዚአብሔር እንዳዘዘ ባደረገ ጊዜ፣ ውሃው በግብፃውያን ሠራዊት ላይ ተገለበጠና ወደ ድሮው ቦታ ተመለሰ።የግብፃውያን ጦር ሠራዊት በሙሉ ሰጠመ።

እስራኤላውያን ግብፃውያን እንደ ሞቱ ባዩ ጊዜ በእግዚአብሔር አመኑ፤ ሙሴም የእግዚአብሔር ነቢይ መሆኑን አመኑ።

ደግሞም እስራኤላውያን እግዚአብሔር ከሞትና ከባርነት ስለ አዳናቸው እጅግ በጣም ደስ አላቸው! አሁን እግዚአብሔርን ለማገልገል ነጻ ሆኑ። እስራኤላውያንም እግዚአብሔር ከግብፃውያን ጦር ሠራዊት ስለ አዳናቸው ዐዲሱን ነጻነታቸውን ለማክበርና እግዚአብሔርን ለማመስገን ብዙ መዝሙሮችን ዘመሩ።

እግዚአብሔር እንዴት በግብፃውያን ላይ ድልን እንደ ሰጣቸውና ከባርነት እንዳዳናቸው ያስታውሱ ዘንድ በያመቱ ፋሲካን እንዲያከብሩ እስራኤላውያንን አዘዛቸው። እንከን በፍጹም የሌለበትን ጠቦት አርደው ካልቦካ ቂጣ ጋር በመብላት ተደሰቱ።፡፡
የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከዘጸአት 12፡33-15፡21፡፡