አማርኛ: Open Bible Stories

Updated ? hours ago # views See on DCS

12. የእስራኤላውያን ከግብፅ መውጣት

Image

እስራኤላውያን ከግብፅ በመውጣታቸው በጣም ደስ አላቸው። ከእንግዲህ ባሪያዎች አይደሉም፣ ወደ ተስፋዪቱ ምድርም በመጓዝ ላይ ናቸው። ግብፃውያን ለእስራኤላውያን ወርቅና ብር ሌሎችም የከበሩ ነገሮች ሳይቀሩ የጠየቁትን ማንኛውንም ነገር ሰጡአቸው። እስሬላውያን ከግብፅ ሲወጡ ከሌሎች ብሔሮች የሆኑ አንዳንድ ሰዎች በእግዚአብሔር አምነው ከእስራኤላውያን ጋር ከግብፅ ወጡ።

Image

እግዚአብሔርም ቀን ረጅም በሆነ የደመና ዓምድ፣ ማታ ደግሞ ረጅም የሆነ የእሳት ዓምድ ከፊት ከፊታቸው እንዲሄድ እያደረገ መራቸው። እግዚአብሔር ሁልጊዜ ከእነርሱ ጋር በመሆን ሲጓዙ መራቸው።እነርሱ ማድረግ ያለባቸው ነገር ቢኖር እርሱን መከተል ብቻ ነበር።

Image

ከጥቂት ጊዜ በኋላ፣ ፈርዖንና ሕዝቡ ዐሳባቸውን ቀይረው እስራኤላውያን እንደ ገና የእነርሱ ባሪያዎች እንዲሆኑ ፈለጉ። እግዚአብሔር ብቸኛው እውነተኛ አምላክ መሆኑን ሕዝቡ እንዲያዩ፣ እንዲሁም እርሱ፣ ያሕዌ፣ ከፈርዖንና ከአማልክቱ የበለጠ ኃያል እንደ ሆነ ይረዱ ዘንድ የፈርዖንን ልብ አደነደነው።

Image

ስለዚህ ፈርዖንና ጦር ሠራዊቱ እንደ ገና ባሪያዎቻቸው ሊያደርጉአቸው እስራኤላውያንን አሳደዱአቸው። እስራኤላውያን የግብፅ ጦር ሠራዊት ሲመጣ ባዩ ጊዜ፣ በፈርዖን ጦር ሠራዊትና በቀይ ባሕር መካከል እንደ ተጠመዱ ዐወቁ። በጣም ፈርተው ስለ ነበር፣ ‹‹ከግብፅ ለምን ወጣን? መሞታችን ነው!›› ብለው ጮኹ።

Image

ሙሴ እስራኤላውያንን፣ ‹‹አትፍሩ! ዛሬ እግዚአብሔር ስለ እናንተ ተዋግቶ ያድናችኋል›› ብሎ ነገራቸው። ከዚያም እግዚአብሔር፣ለሙሴ ‹‹ሕዝቡ ወደ ቀይ ባሕር እንዲንቀሳቀሱ ንገራቸው››አለ።

Image

ከዚያም ግብፃውያን እስራኤላውያንን ማየት እንዳይችሉ እግዚአብሔር የደመናውን ዓምድ በእስራኤላውያንና በግብፃውያን መካከል አደረገው።

Image

እግዚአብሔርም ለሙሴ በባሕሩ ላይ እጁን እንዲዘረጋና ውሃውን እንዲከፍለው ነገረው። ከዚያም እግዚአብሔር በባሕሩ መካከል መተላለፊያ መንገድ ይኖር ዘንድ ነፋስ ውሃውን ወደ ግራና ወደ ቀኝ እንዲገፋ አደረገ።

Image

እስራኤላውያንም ውሃው በግራና በቀኛቸው እንደ ግድግዳ ሆኖላቸው በባሕሩ መካከል በደረቅ መሬት ላይ ተጓዙ።

Image

ከዚያም እግዚአብሔር እስራኤላውያን እያመለጡ መሆናቸውን ግብፃውያኑ ያዩ ዘንድ የደመናውን አምድ ከመንገዱ ወደ ላይ አነሳው። ግብፃውያንም ከኋላቸው ሊያሳድዱአቸው ወሰኑ።

Image

ስለዚህ በባሕሩ መካከል ውስጥ ባለው መንገድ እስራኤላውያንን ተከተሉአቸው፣ ነገር ግን እግዚአብሔር ግብፃውያን እንዲርበተበቱና ሰረገሎቻቸውም እንዳይንቀሳቀሱ አደረገ።ግብፃውያንም “ለነፍሳቸው ሽሹ! እግዚአብሔር ለእስራኤላውያን እየተዋጋላቸው ነው!” ብለው ጮኹ።

Image

እስራኤላውያን ሁሉ ባሕሩን በደኅና ከተሻገሩ በኋላ፣ እግዚአብሔር እንደ ገና እጁን እንዲዘረጋ ለሙሴ ነገረው። እርሱም እግዚአብሔር እንዳዘዘ ባደረገ ጊዜ፣ ውሃው በግብፃውያን ሠራዊት ላይ ተገለበጠና ወደ ድሮው ቦታ ተመለሰ።የግብፃውያን ጦር ሠራዊት በሙሉ ሰጠመ።

Image

እስራኤላውያን ግብፃውያን እንደ ሞቱ ባዩ ጊዜ በእግዚአብሔር አመኑ፤ ሙሴም የእግዚአብሔር ነቢይ መሆኑን አመኑ።

Image

ደግሞም እስራኤላውያን እግዚአብሔር ከሞትና ከባርነት ስለ አዳናቸው እጅግ በጣም ደስ አላቸው! አሁን እግዚአብሔርን ለማገልገል ነጻ ሆኑ። እስራኤላውያንም እግዚአብሔር ከግብፃውያን ጦር ሠራዊት ስለ አዳናቸው ዐዲሱን ነጻነታቸውን ለማክበርና እግዚአብሔርን ለማመስገን ብዙ መዝሙሮችን ዘመሩ።

Image

እግዚአብሔር እንዴት በግብፃውያን ላይ ድልን እንደ ሰጣቸውና ከባርነት እንዳዳናቸው ያስታውሱ ዘንድ በያመቱ ፋሲካን እንዲያከብሩ እስራኤላውያንን አዘዛቸው። እንከን በፍጹም የሌለበትን ጠቦት አርደው ካልቦካ ቂጣ ጋር በመብላት ተደሰቱ።፡፡

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከዘጸአት 12፡33-15፡21፡፡