49. ዐዲሱ የእግዚአብሔር ቃል ኪዳን

አንድ መልአክ ማርያም ለተባለች ድንግል የእግዚአብሔርን ልጅ እንደምትወልድ ነገራት፡፡ ስለዚህ እርስዋ ገና ድንግል እያለች መንፈስ ቅዱስ ጸለለላትና አረገዘች። ወንድ ልጅም ወለደችና ስሙን ኢየሱስ ብላ ጠራችው፡፡ ስለሆነም ኢየሱስ አምላክም ሰውም ሆነ፡፡

ኢየሱስ የእግዚብሔር ልጅ መሆኑን የሚያረጋግጡ ብዙ ተአምራትን አደረገ፡፡ በውሃ ላይ ተራመደ፣ ማዕበልን ጸጥ አደረገ፣ ብዙ በሽተኞችን ፈወሰ፣ አጋንንትን አወጣ፣ ሙታንን ሕያው አድርጎ አስነሣ፣ እንዲሁም አምስት እንጀራና ሁለት ትንንሽ ዓሣ ከ5,000 ለበለጡ ሰዎች እንዲበቃ አደረገ፡፡

ደግሞም ኢየሱስ ታላቅ መምህር ነው፣ የእግዚአብሔር ልጅ ስለሆነም በሥልጣን ተናገረ፡፡ ራሳችሁን እንደምትወዱ ሌሎች ሰዎችንም ውደዱ ብሎ አስተማረ፡፡

ደግደግሞም እርሱ ሀብታችሁን ጨምሮ ማንኛውንም ነገር ከምትወዱት አብልጣችሁ እግዚአብሔርን መውደድ አለባችሁ ብሎ አስተማረ፡፡

ኢየሱስ የእግዚአብሔር መንግሥት በዓለም ካለ ከማንኛውም ነገር ይልቅ የከበረች ነች አለ፡፡ ለማንኛውም ሰው እጅግ በጣም አስፈላጊው ነገር የእግዚአብሔር መንግሥት ዜጋ መሆን ነው፡፡ ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ለመግባት ከኃጢአታችሁ መንጻት አለባችሁ፡፡

ኢየሱስ አንዳንድ ሰዎች እርሱን ተቀብለውት እንደሚድኑ፣ ሌሎች ግን እንደማይቀበሉት አስተማረ፡፡ አንዳንድ ሰዎች እንደ መልካም መሬት ናቸው አለ፡፡ የኢየሱስን የምሥራች ተቀብለው ይድናሉ፡፡ ሌሎች ሰዎች ደግሞ የእግዚአብሔር ቃል እንደማይገባበትና ምንም ፍሬ እንደማያፈራ መንገድ ዳር እንዳለ መሬት ናቸው፡፡ እነዚያ ሰዎች ስለ ኢየሱስ የሚናገረውን መልእክት የማይቀበሉና ወደ መንግሥቱ የማይገቡ ናቸው፡፡

ኢየሱስ፣ እግዚአብሔር ኃጢአተኞችን በጣም እንደሚወድ አስተማረ፡፡ ይቅር ሊላቸውና ልጆቹም ሊያደርጋቸው ይፈልጋል፡፡

ደግሞም ኢየሱስ እግዚአብሔር ኃጢአትን እንደሚጠላ ነግሮናል፡፡ አዳምና ሔዋን ኃጢአት በሠሩ ጊዜ፣ ኃጢአቱ ዝርያዎቻቸውን ሁሉ አበላሸ፡፡ ከዚህ የተነሣ በዓለም ላይ ያለ ሁሉም ሰው ኃጢአት ሠርቶአል፤ ከእግዚአብሔርም ተለይቶአል፡፡ ስለዚህ ሁሉም ሰው የእግዚአብሔር ጠላት ሆኖአል፡፡

ነገር ግን በእርሱ የሚያምን ሁሉ የዘላለም ሕይወት እንዲኖረው እንጂ እንዳይጠፋ እግዚአብሔር አንድያ ልጁን እስኪሰጥ ድረስ ዓለሙን እንዲሁ ወዶአል፡፡

በኃጢአታችሁ ምክንያት በደለኞች ናችሁና መሞት ይገባችኋል፡፡ እግዚአብሔር በእናንተ ላይ መቈጣት ነበረበት፣ ነገር ግን ቊጣውን በእናንተ ላይ በማድረግ ፈንታ በኢየሱስ ላይ አፈሰሰው፡፡ ኢየሱስ በመስቀል ላይ በሞተ ጊዜ፣ የእናንተን ቅጣት ተቀበለ፡፡፡

ኢየሱስ በፍጹም ኃጢአት አላደረገም፣ ነገር ግን የእናንተን ኃጢአትና በዓለም ያለውን የእያንዳንዱን ሰው ኃጢአት ለማስወገድ መቀጣትንና ፍጹም መሥዋዕት ሆኖ መሞትን መረጠ፡፡ ኢየሱስ ራሱን መሥዋዕት አድርጎ አቀረበ፡፡ ኢየሱስ ራሱን መሥዋዕት አድርጎ ስላቀረበ እግዚአብሔር ማንኛውንም ኃጢአት፣ አስከፊ የሆነውን ኃጢአት እንኳ ይቅር ማለት ይችላል፡፡

መልካም ሥራዎች ሊያድኑአችሁ አይችሉም፡፡ ከእግዚአብሔር ጋር ግንኙነት እንዲኖራችሁ ልታደርጉ የምትችሉበት ሌላ ምንም ነገር የለም፡፡ ኢየሱስ ብቻ ኃጢአታችሁን ሊያጥብ ይችላል፡፡ ኢየሱስ የእግዚአብሔር ልጅ መሆኑን፣ በእናንተ ፈንታ በመስቀል ላይ መሞቱን እግዚአብሔርም ከሙታን እንዳስነሣው ብቻ ማመን አለባችሁ፡፡

እግዚአብሔር በኢየሱስ የሚያምነውንና ጌታው አድርጎ የሚቀበለውን ማንኛውንም ሰው ያድናል፡፡ ነገር ግን በእርሱ የማያምነውን ማንኛውንም ሰው አያድንም። ባለ ጠጎች ብትሆኑ ወይም ድሆች፣ ወንድ ወይም ሴት፣ ሽማግሌ ወይም ወጣት ብትሆኑ፣ ወይም የትም ብትኖሩ እግዚአብሔር ይወዳችኋል፤ በኢየሱስ እንድታምኑና ከእርሱ ጋር የቅርብ ግንኙነት እንዲኖራችሁም ይፈልጋል፡፡

ኢየሱስ በእርሱ እንድታምኑና እንድትጠመቁ ይጋብዛችኋል፡፡ ኢየሱስ መሲሕና ብቸኛው የእግዚአብሔር ልጅ መሆኑን ታምናላችሁ? ኃጢአተኞች መሆናችሁንና እግዚአብሔርም እናንተን መቅጣት እንዳለበት ታምናላችሁ? ኢየሱስ ኃጢአታችሁን ለማስወገድ በመስቀል ላይ መሞቱን ታምናላችሁ?

በኢየሱስና እርሱ ለእናንተ በሠራው ሥራ ብታምኑ፣ እናንተ ክርስቲያኖች ናችሁ! እግዚአብሔርም ከሰይጣንና ከጨለማ መንግሥት አውጥቶአችሁ በእግዚአብሔር የብርሃን መንግሥት ውስጥም አድርጎአችኋል፡፡ እግዚአብሔር ታደርጉት የነበረውን አሮጌውንና ኃጢአተኛውን መንገዳችሁን አስወግዶ ዐዲስና የጽድቅ መንገድ እንድትኖሩ ዐዲስ ሕይወትን ሰጥቶአችኋል፡፡

እናንተ ክርስቲያኖች ከሆናችሁ፣ ኢየሱስ በሠራው ሥራ ምክንያት እግዚአብሔር ኃጢአታችሁን ይቅር ብሏችኋል። አሁን እግዚአብሔር የእርሱ ጠላቶች ሳትሆኑ የቅርብ ወዳጆቹ አድርጎ ይቈጥራችኋል።

እናንተ የእግዚአብሔር ወዳጆችና የጌታ ኢየሱስ አገልጋዮች ከሆናችሁ፣ ኢየሱስ ለሚያስተምራችሁ ነገር ትታዘዛላችሁ። ክርስቲያኖች ብትሆኑም እንኳ፣ አሁንም ኃጢአት ለመሥራት ትፈተናላችሁ። ነገር ግን እግዚአብሔር የታመነ ነውና ‹‹ኃጢአታችሁን ብትናዘዙ ይቅር እላችኋለሁ›› ይላል። ኃጢአትን የምትቃወሙበትንም ኃይል ይሰጣችኋል።

እግዚአብሔር እንድትጸልዩ፣ ቃሉን እንድታጠኑ፣ ከሌሎች ክርስቲያኖች ጋር እንድታመልኩ፣ ያደረገላችሁንም ለሌሎች እንድትነግሩ ይጠይቃችኋል። እነዚህ ነገሮች ሁሉ ከእርሱ ጋር የጠበቀ ግንኙነት እንዲኖራችሁ ይረዱአችኋል።
የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከሮሜ 3፡21-26፤ 5፡1-11፤ ዮሐንስ 3፡16፤ ማርቆስ 16፡16፤ ቈላስይስ 1፡13-14፤ 2ኛ ቆሮንቶስ 5፡17-21፤ 1ኛ ዮሐንስ 1፡5-10፡፡