አማርኛ: Open Bible Stories

Updated ? hours ago # views See on DCS

4. የእግዚአብሔር ቃል ኪዳን ከአብርሃም ጋር

Image

ከጥፋት ውሃው ከብዙ ዓመታት በኋላ ሕዝቦች በዓለም ላይ እንደገና በዙ። ሁሉም አንድ አይነት ቋንቋ ይናገሩ ነበር። እግዚአብሔር እንዳዘዛቸው ምድርን በመሙላት ፋንታ በአንድነት ተሰብስበው ከተማ ሠሩ።

Image

እነርሱም በጣም ትምክህተኞችና እግዚአብሔር የተናገራቸውን ነገር የማይሰሙ ነበሩ። እንዲያውም ወደ ሰማይ ሊደርሱ ረጅም ሕንጻ መገንባት ጀመሩ። እግዚአብሔርም እነዚህ ሰዎች በአንድ ላይ ሆነው ክፉ መሥራታቸውን ከቀጠሉ ከዚህም የከፋ ብዙ ኃጢአት ማድረግ እንደሚችሉ አየ።

Image

ስለዚህም እግዚአብሔር ቋንቋቸውን ወደ ብዙ የተለያዩ ቋንቋዎች ደበላለቀና ሕዝቡን በዓለም ሁሉ በተናቸው። ሊሠሩት የጀመሩት ከተማ ስም ባቤል ይባላል። የስሙም ትርጓሜ የተደባለቀ ወይም ግራ የተጋባ ማለት ነው።

Image

ከመቶ ዓመታት በኋላ እግዚአብሔር አብራም የተባለውን ሰው ተናገረው። እግዚአብሔርም እንዲህ አለው “አገርህንና ቤተ ሰብህን ትተህ እኔ ወደማሳይህ ምድር ሂድ። በዚያም እባርክሃለሁ፣ ታላቅ ሕዝብም አደርግሃለሁ፤ ስምህንም ታላቅ አደርገዋለሁ፣ የሚባርኩህን እባርካለሁ፣ የሚረግሙህንም እረግማለሁ፤ የምድር ሰዎች ሁሉ ባንተ ይባረካሉ።”

Image

አብራምም እግዚአብሔርን ታዘዘ፤ ሚስቱን ሦራንና አገልጋዮቹን ሁሉና ንብረቱንም ሁሉ ይዞ እግዚአብሔር ወዳሳየው የከነዓን ምድር ሄደ።

Image

አብራም ከነዓን በደረሰ ጊዜ እግዚአብሔር ‹‹በዙሪያህ ያለውን ሁሉ ተመልከት፤ይህን የምታየውን ምድር ሁሉ ለአንተና ለዘሮችህ ውርስ አድርጌ እሰጣችኋለሁ›› አለው። አብራምም በምድሪቱ ተቀመጠ።

Image

ከዕለታት አንድ ቀን አብራም መልከ ጼዴቅ የተባለውን የልዑል እግዚአብሔር ሊቀ ካህን ተገናኘው። መልከ ጻዴቅም አብራምን ባረከው፤ እንዲህም አለው ‹‹የሰማይና የምድር ጌታ ልዑል እግዚአብሔር አብራምን ይባርክ››። አብራምም ለመልከ ጼዴቅ ካለው ሁሉ አሥራት ሰጠው።

Image

አብራምና ሦራ አሁንም ያለ ልጅ ብዙ ዓመታት ኖሩ። እግዚአብሔር ለአብራም እንደ ገና ተናገረውና ልጅ እንደሚወልድና ዘሮቹ እንደ ሰማይ ክዋክብት እንደሚበዙ ተስፋ ሰጠው። አብራምም በእግዚአብሔር ተስፋ አመነ። አብራምም በእግዚአብሔር ተስፋ በማመኑ ምክንያት ጻድቅ ሆኖ ተቈጠረ።

Image

እግዚአብሔርም ከአብራም ጋር ቃል ኪዳን ገባ። ቃል ኪዳን በሁለት ወገኖች መካከል የሚደረግ ስምምነት ነው። እግዚአብሔርም አብራምን ‹‹ከገዛ አብራክህ ልጅ እሰጥሃለሁ። የከነዓንንም ምድር ለዘሮችህ እሰጣለሁ›› አለው። አብራም ግን በዚያን ጊዜ ልጅ አልነበረውም።

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከዘፍጥረት 11-15