4. የእግዚአብሔር ቃል ኪዳን ከአብርሃም ጋር

ከጥፋት ውሃው ከብዙ ዓመታት በኋላ ሕዝቦች በዓለም ላይ እንደገና በዙ። ሁሉም አንድ አይነት ቋንቋ ይናገሩ ነበር። እግዚአብሔር እንዳዘዛቸው ምድርን በመሙላት ፋንታ በአንድነት ተሰብስበው ከተማ ሠሩ።

እነርሱም በጣም ትምክህተኞችና እግዚአብሔር የተናገራቸውን ነገር የማይሰሙ ነበሩ። እንዲያውም ወደ ሰማይ ሊደርሱ ረጅም ሕንጻ መገንባት ጀመሩ። እግዚአብሔርም እነዚህ ሰዎች በአንድ ላይ ሆነው ክፉ መሥራታቸውን ከቀጠሉ ከዚህም የከፋ ብዙ ኃጢአት ማድረግ እንደሚችሉ አየ።

ስለዚህም እግዚአብሔር ቋንቋቸውን ወደ ብዙ የተለያዩ ቋንቋዎች ደበላለቀና ሕዝቡን በዓለም ሁሉ በተናቸው። ሊሠሩት የጀመሩት ከተማ ስም ባቤል ይባላል። የስሙም ትርጓሜ የተደባለቀ ወይም ግራ የተጋባ ማለት ነው።

ከመቶ ዓመታት በኋላ እግዚአብሔር አብራም የተባለውን ሰው ተናገረው። እግዚአብሔርም እንዲህ አለው “አገርህንና ቤተ ሰብህን ትተህ እኔ ወደማሳይህ ምድር ሂድ። በዚያም እባርክሃለሁ፣ ታላቅ ሕዝብም አደርግሃለሁ፤ ስምህንም ታላቅ አደርገዋለሁ፣ የሚባርኩህን እባርካለሁ፣ የሚረግሙህንም እረግማለሁ፤ የምድር ሰዎች ሁሉ ባንተ ይባረካሉ።”

አብራምም እግዚአብሔርን ታዘዘ፤ ሚስቱን ሦራንና አገልጋዮቹን ሁሉና ንብረቱንም ሁሉ ይዞ እግዚአብሔር ወዳሳየው የከነዓን ምድር ሄደ።

አብራም ከነዓን በደረሰ ጊዜ እግዚአብሔር ‹‹በዙሪያህ ያለውን ሁሉ ተመልከት፤ይህን የምታየውን ምድር ሁሉ ለአንተና ለዘሮችህ ውርስ አድርጌ እሰጣችኋለሁ›› አለው። አብራምም በምድሪቱ ተቀመጠ።

ከዕለታት አንድ ቀን አብራም መልከ ጼዴቅ የተባለውን የልዑል እግዚአብሔር ሊቀ ካህን ተገናኘው። መልከ ጻዴቅም አብራምን ባረከው፤ እንዲህም አለው ‹‹የሰማይና የምድር ጌታ ልዑል እግዚአብሔር አብራምን ይባርክ››። አብራምም ለመልከ ጼዴቅ ካለው ሁሉ አሥራት ሰጠው።

አብራምና ሦራ አሁንም ያለ ልጅ ብዙ ዓመታት ኖሩ። እግዚአብሔር ለአብራም እንደ ገና ተናገረውና ልጅ እንደሚወልድና ዘሮቹ እንደ ሰማይ ክዋክብት እንደሚበዙ ተስፋ ሰጠው። አብራምም በእግዚአብሔር ተስፋ አመነ። አብራምም በእግዚአብሔር ተስፋ በማመኑ ምክንያት ጻድቅ ሆኖ ተቈጠረ።

እግዚአብሔርም ከአብራም ጋር ቃል ኪዳን ገባ። ቃል ኪዳን በሁለት ወገኖች መካከል የሚደረግ ስምምነት ነው። እግዚአብሔርም አብራምን ‹‹ከገዛ አብራክህ ልጅ እሰጥሃለሁ። የከነዓንንም ምድር ለዘሮችህ እሰጣለሁ›› አለው። አብራም ግን በዚያን ጊዜ ልጅ አልነበረውም።
የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከዘፍጥረት 11-15