40. ኢየሱስ ተሰቀለ

ወታደሮቹ በኢየሱስ ላይ ከዘበቱበት በኋላ፣ ሊሰቅሉት ወሰዱት። የሚሞትበትን መስቀል እንዲሸከም አደረጉት።

ወታደሮቹ ኢየሱስን ‹‹የራስ ቅል›› ተብሎ ወደሚጠራው ስፍራ አመጡትና እጆቹንና እግሮቹን በመስቀል ላይ ጠረቁአቸው። ኢየሱስ ግን፣ ‹‹አባት ሆይ፣ የሚያደርጉትን ዐያውቁምና ይቅር በላቸው›› አለ። ጲላጦስ፣ ‹‹የአይሁድ ንጉሥ›› ብለው ምልክት እንዲጽፉና ከኢየሱስ ራስ በላይ በመስቀሉ ላይ እንዲያኖሩት አዘዘ።

ወታደሮቹ በኢየሱስ ልብስ ላይ ዕጣ ተጣጣሉ። ይህንን ባደረጉበት ጊዜ፣ ‹‹ልብሶቼን ተከፋፈሉ፣ በእጀ ጠባቡም ላይ ዕጣ ተጣጣሉበት›› የሚለውን ትንቢት ፈጸሙ።

ኢየሱስ በሁለት ወንበዴዎች መካከል ተሰቀለ። አንደኛው በኢየሱስ ላይ ዘበተበት፣ ሌላኛው ግን፣ ‹‹አንተ እግዚአብሔርን አትፈራም? እኛ ወንጀለኞች ነን፣ ይህ ሰው ግን ወንጀል የለበትም›› አለ። ከዚያም ኢየሱስን፣ ‹‹እባክህን በመንግሥትህ ዐስበኝ›› አለው። ኢየሱስ፣ ‹‹ዛሬ ከእኔ ጋር በገነት ትሆናለህ›› ብሎ መለሰለት።

የአይሁድ መሪዎችና በሕዝቡ መካከል የነበሩ ሌሎች ሰዎች በኢየሱስ ላይ ዘበቱበት። ‹‹የእግዚአብሔር ልጅ ከሆንክ ከመስቀል ላይ ውረድና ራስህን አድን! ከዚያ በኋላ እናምንብሃለን›› አሉት።

በዚያ ሰዓት ጊዜው ገና እኩለ ቀን ቢሆንም፣ በምድር ሁሉ ላይ ጨለማ ሆነ፡፡ ጨለማውም ከእኩለ ቀን እስከ ዘጠኝ ሰዓት ድረስ ቆየ፡፡

ከዚያ በኋላ ኢየሱስ፣ ‹‹ተፈጸመ! አባት ሆይ፣ ነፍሴን በእጅህ እሰጣለሁ›› ብሎ ጮኸ፡፡ ከዚያም ራሱን አዘነበለና ነፍሱን አሳልፎ ሰጠ፡፡ በሞተ ጊዜ የምድር መንቀጥቀጥ ሆነ፣ በቤተ መቅደስ የነበረው ትልቁ መጋረጃም ከላይ እስከ ታች ለሁለት ተቀደደ፡፡

ኢየሱስ በሞቱ በኩል ወደ እግዚአብሔር እንዲመጡ ለሰዎች ሁሉ መንገድ ከፈተላቸው፡፡ ኢየሱስን ይጠብቅ የነበረው ወታደር የሆነውን ሁሉ ባየ ጊዜ፣ ‹‹በእርግጥ ይህ ሰው ወንጀል የለበትም፡፡ የእግዚአብሔር ልጅ ነው›› አለ፡፡

በዚያን ጊዜ ኢየሱስ መሲሕ መሆኑን ያመኑ ሁለት የአይሁድ መሪዎች፣ ዮሴፍና ኒቆዲሞስ የኢየሱስን ሥጋ እንዲሰጣቸው ጲላጦስን ለመኑት። ሥጋውን በጨርቅ ገነዙትና ከአለት በተወቀረ መቃብር አኖሩት። ከዚያም የመቃብሩን በር ትልቅ ድንጋይ አንከባልለው ዘጉት።
የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከማቴዎስ 27፡27-61፤ ማርቆስ 15፡16-47፤ ሉቃስ 23፡26-56፤ ዮሐንስ 19፡17-42።