አማርኛ: Open Bible Stories

Updated ? hours ago # views See on DCS

40. ኢየሱስ ተሰቀለ

Image

ወታደሮቹ በኢየሱስ ላይ ከዘበቱበት በኋላ፣ ሊሰቅሉት ወሰዱት። የሚሞትበትን መስቀል እንዲሸከም አደረጉት።

Image

ወታደሮቹ ኢየሱስን ‹‹የራስ ቅል›› ተብሎ ወደሚጠራው ስፍራ አመጡትና እጆቹንና እግሮቹን በመስቀል ላይ ጠረቁአቸው። ኢየሱስ ግን፣ ‹‹አባት ሆይ፣ የሚያደርጉትን ዐያውቁምና ይቅር በላቸው›› አለ። ጲላጦስ፣ ‹‹የአይሁድ ንጉሥ›› ብለው ምልክት እንዲጽፉና ከኢየሱስ ራስ በላይ በመስቀሉ ላይ እንዲያኖሩት አዘዘ።

Image

ወታደሮቹ በኢየሱስ ልብስ ላይ ዕጣ ተጣጣሉ። ይህንን ባደረጉበት ጊዜ፣ ‹‹ልብሶቼን ተከፋፈሉ፣ በእጀ ጠባቡም ላይ ዕጣ ተጣጣሉበት›› የሚለውን ትንቢት ፈጸሙ።

Image

ኢየሱስ በሁለት ወንበዴዎች መካከል ተሰቀለ። አንደኛው በኢየሱስ ላይ ዘበተበት፣ ሌላኛው ግን፣ ‹‹አንተ እግዚአብሔርን አትፈራም? እኛ ወንጀለኞች ነን፣ ይህ ሰው ግን ወንጀል የለበትም›› አለ። ከዚያም ኢየሱስን፣ ‹‹እባክህን በመንግሥትህ ዐስበኝ›› አለው። ኢየሱስ፣ ‹‹ዛሬ ከእኔ ጋር በገነት ትሆናለህ›› ብሎ መለሰለት።

Image

የአይሁድ መሪዎችና በሕዝቡ መካከል የነበሩ ሌሎች ሰዎች በኢየሱስ ላይ ዘበቱበት። ‹‹የእግዚአብሔር ልጅ ከሆንክ ከመስቀል ላይ ውረድና ራስህን አድን! ከዚያ በኋላ እናምንብሃለን›› አሉት።

Image

በዚያ ሰዓት ጊዜው ገና እኩለ ቀን ቢሆንም፣ በምድር ሁሉ ላይ ጨለማ ሆነ፡፡ ጨለማውም ከእኩለ ቀን እስከ ዘጠኝ ሰዓት ድረስ ቆየ፡፡

Image

ከዚያ በኋላ ኢየሱስ፣ ‹‹ተፈጸመ! አባት ሆይ፣ ነፍሴን በእጅህ እሰጣለሁ›› ብሎ ጮኸ፡፡ ከዚያም ራሱን አዘነበለና ነፍሱን አሳልፎ ሰጠ፡፡ በሞተ ጊዜ የምድር መንቀጥቀጥ ሆነ፣ በቤተ መቅደስ የነበረው ትልቁ መጋረጃም ከላይ እስከ ታች ለሁለት ተቀደደ፡፡

Image

ኢየሱስ በሞቱ በኩል ወደ እግዚአብሔር እንዲመጡ ለሰዎች ሁሉ መንገድ ከፈተላቸው፡፡ ኢየሱስን ይጠብቅ የነበረው ወታደር የሆነውን ሁሉ ባየ ጊዜ፣ ‹‹በእርግጥ ይህ ሰው ወንጀል የለበትም፡፡ የእግዚአብሔር ልጅ ነው›› አለ፡፡

Image

በዚያን ጊዜ ኢየሱስ መሲሕ መሆኑን ያመኑ ሁለት የአይሁድ መሪዎች፣ ዮሴፍና ኒቆዲሞስ የኢየሱስን ሥጋ እንዲሰጣቸው ጲላጦስን ለመኑት። ሥጋውን በጨርቅ ገነዙትና ከአለት በተወቀረ መቃብር አኖሩት። ከዚያም የመቃብሩን በር ትልቅ ድንጋይ አንከባልለው ዘጉት።

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከማቴዎስ 27፡27-61፤ ማርቆስ 15፡16-47፤ ሉቃስ 23፡26-56፤ ዮሐንስ 19፡17-42።