አማርኛ: Open Bible Stories

Updated ? hours ago # views See on DCS

31. ኢየሱስ በውሃ ላይ ተራመደ

Image

ከዚያም ኢየሱስ ሕዝቡን እያሰናበተ እያለ ጀልባ ውስጥ ገብተው እየቀዘፉ ወደ ማዶ እንዲሻገሩ ለደቀ መዛሙርቱ ነገራቸው፡፡ ኢየሱስ ሕዝቡን ካሰናበተ በኋላ ለመጸለይ ወደ ተራራ ወጣ፡፡ በዚያ ኢየሱስ ብቻውን ነበር፣ እስከ እኩለ ሌሊትም ጸለየ፡፡

Image

በዚያን ጊዜ፣ ደቀ መዛሙርቱ ጀልባቸውን እየቀዘፉ ነበር፣ ይሁን እንጂ በእኩለ ሌሊት የደረሱት ወደ ሐይቁ አጋማሽ ብቻ ነበር፡፡ ነፋሱ በእነርሱ ላይ በኃይል ይነፍስ ስለ ነበር የሚቀዝፉት በጣም በችግር ነበር፡፡

Image

በዚያን ጊዜ ኢየሱስ መጸለዩን ጨረሰና ወደ ደቀ መዛሙርቱ ሄደ፡፡ በውሃው ላይ እየተራመደ ሐይቁን አቋርጦ ወደ ጀልባቸው መጣ!

Image

ደቀ መዛሙርቱ ኢየሱስን ባዩ ጊዜ በጣም ፈሩ፣ ምክንያቱም ምትሐት ያዩ መሰላቸው፣ ኢየሱስም እንደ ፈሩ ዐወቀ፣ ስለዚህ ወደ እነርሱ ተጣራና፣ ‹‹አትፍሩ፡፡ እኔ ነኝ!›› አላቸው፡፡

Image

በዚያን ጊዜ ጴጥሮስ ኢየሱስን፣ ‹‹መምህር ሆይ፣ አንተስ ከሆንክ በውሃው ላይ ወደ አንተ እንድመጣ እዘዝ›› አለው፡፡ ኢየሱስም ጴጥሮስን፣ ‹‹ና!›› አለው፡፡

Image

ስለዚህ ጴጥሮስ ከጀልባው ወጣና በውሃው ላይ ወደ ኢየሱስ መራመድ ጀመረ፡፡ ነገር ግን ትንሽ እንደ ተራመደ ዓይኖቹን ከኢየሱስ ዞር አደረገና ማዕበሉን ማየትና ብርቱውን ነፋስም መስማት ጀመር፡፡

Image

በዚያን ጊዜ ጴጥሮስ ፈራና በውሃው መስጠም ጀመረ፡፡ ‹‹መምህር ሆይ፣ አድነኝ!›› ብሎ ጮኸ፡፡ ኢየሱስ ወዲያው እጆቹን ዘረጋና ያዘው፡፡ ከዚያም ጴጥሮስን፣ ‹‹አንተ እምነት የጎደለህ፣ ለምን ተጠራጠርህ?›› አለው፡፡

Image

ጴጥሮስና ኢየሱስ ወደ ጀልባው በገቡ ጊዜ፣ ነፋሱ ወዲያውኑ ቆመና ውሃው ጸጥ አለ፡፡ ደቀ መዛሙርቱ ተደነቁ፡፡ ‹‹በእውነት አንተ የእግዚአብሔር ልጅ ነህ›› እያሉ ለኢየሱስ ሰገዱለት፡፡

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከማቴዎስ 14፡22-23፤ ማርቆስ 6፡45-52፤ ዮሐንስ 6፡16-21፡፡