31. ኢየሱስ በውሃ ላይ ተራመደ

ከዚያም ኢየሱስ ሕዝቡን እያሰናበተ እያለ ጀልባ ውስጥ ገብተው እየቀዘፉ ወደ ማዶ እንዲሻገሩ ለደቀ መዛሙርቱ ነገራቸው፡፡ ኢየሱስ ሕዝቡን ካሰናበተ በኋላ ለመጸለይ ወደ ተራራ ወጣ፡፡ በዚያ ኢየሱስ ብቻውን ነበር፣ እስከ እኩለ ሌሊትም ጸለየ፡፡

በዚያን ጊዜ፣ ደቀ መዛሙርቱ ጀልባቸውን እየቀዘፉ ነበር፣ ይሁን እንጂ በእኩለ ሌሊት የደረሱት ወደ ሐይቁ አጋማሽ ብቻ ነበር፡፡ ነፋሱ በእነርሱ ላይ በኃይል ይነፍስ ስለ ነበር የሚቀዝፉት በጣም በችግር ነበር፡፡

በዚያን ጊዜ ኢየሱስ መጸለዩን ጨረሰና ወደ ደቀ መዛሙርቱ ሄደ፡፡ በውሃው ላይ እየተራመደ ሐይቁን አቋርጦ ወደ ጀልባቸው መጣ!

ደቀ መዛሙርቱ ኢየሱስን ባዩ ጊዜ በጣም ፈሩ፣ ምክንያቱም ምትሐት ያዩ መሰላቸው፣ ኢየሱስም እንደ ፈሩ ዐወቀ፣ ስለዚህ ወደ እነርሱ ተጣራና፣ ‹‹አትፍሩ፡፡ እኔ ነኝ!›› አላቸው፡፡

በዚያን ጊዜ ጴጥሮስ ኢየሱስን፣ ‹‹መምህር ሆይ፣ አንተስ ከሆንክ በውሃው ላይ ወደ አንተ እንድመጣ እዘዝ›› አለው፡፡ ኢየሱስም ጴጥሮስን፣ ‹‹ና!›› አለው፡፡

ስለዚህ ጴጥሮስ ከጀልባው ወጣና በውሃው ላይ ወደ ኢየሱስ መራመድ ጀመረ፡፡ ነገር ግን ትንሽ እንደ ተራመደ ዓይኖቹን ከኢየሱስ ዞር አደረገና ማዕበሉን ማየትና ብርቱውን ነፋስም መስማት ጀመር፡፡

በዚያን ጊዜ ጴጥሮስ ፈራና በውሃው መስጠም ጀመረ፡፡ ‹‹መምህር ሆይ፣ አድነኝ!›› ብሎ ጮኸ፡፡ ኢየሱስ ወዲያው እጆቹን ዘረጋና ያዘው፡፡ ከዚያም ጴጥሮስን፣ ‹‹አንተ እምነት የጎደለህ፣ ለምን ተጠራጠርህ?›› አለው፡፡

ጴጥሮስና ኢየሱስ ወደ ጀልባው በገቡ ጊዜ፣ ነፋሱ ወዲያውኑ ቆመና ውሃው ጸጥ አለ፡፡ ደቀ መዛሙርቱ ተደነቁ፡፡ ‹‹በእውነት አንተ የእግዚአብሔር ልጅ ነህ›› እያሉ ለኢየሱስ ሰገዱለት፡፡
የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከማቴዎስ 14፡22-23፤ ማርቆስ 6፡45-52፤ ዮሐንስ 6፡16-21፡፡