35. የርኅሩኁ አባት ታሪክ

አንድ ቀን ኢየሱስ ብዙ ቀረጥ ሰብሳቢዎችንና ሊሰሙት የተሰበሰቡ ሌሎች ኃጢአተኞችን ያስተምር ነበር፡፡

በዚያ የነበሩ አንዳንድ የሃይማኖት መሪዎች ኢየሱስ ኃጢአተኞችን ወዳጆች አድርጎ ሲቀበላቸው ዐዩ፣ እርስ በርሳቸውም ይነቅፉት ጀመር፡፡ ስለዚህ ኢየሱስ ይህንን ምሳሌ ነገራቸው፡፡

ሁለት ልጆች ያሉት አንድ ሰው ነበር፡፡ ታናሹ ልጅ አባቱን፣ ‹አባቴ ሆይ፣ ከገንዘብህ የሚደርሰኝን ድርሻ አሁን እንድትሰጠኝ እፈልጋለሁ!› አለው፡፡ ስለዚህ አባትዬው ገንዘቡን ለሁለቱ ልጆቹ አካፈላቸው፡፡››

‹‹ታናሹ ልጅ ወዲያውኑ ያለውን ሁሉ ሰበሰበና ሩቅ አገር ሄዶ በኃጢአት የተሞላ ኑሮ እየኖረ ገንዘቡን አጠፋ፡፡

‹‹ከዚያ በኋላ ታናሹ ልጅ በነበረበት አገር ጽኑ ረሀብ ሆነ፣ ምግብ የሚገዛበት ገንዘብም አልነበረውም፡፡ ስለዚህ የተገኘው ሥራ እሪያዎችን የመመገብ ሥራ ብቻ ስለ ነበር በዚያ ሥራ ገባ፡፡ በጣም ተጐሳቊሎና ተርቦ ስለ ነበር የእሪያዎችን ምግብ እንኳ ለመብላት ይመኝ ነበር፡፡››

‹‹በመጨረሻ፣ ታናሹ ልጅ ለራሱ እንዲህ አለ፣ ‹እዚህ ምን እያደረግሁ ነው ያለሁት? የአባቴ አገልጋዮች ሁሉ እንኳ የሚበሉት ብዙ ምግብ አላቸው፣ እኔ ግን እዚህ በረሃብ እሞታለሁ፡፡ ወደ አባቴ ተመልሼ እሄድና ከአገልጋዮቹ እንደ አንዱ እንዲያደርገኝ እለምነዋለሁ፡፡›››

ስለዚህ ታናሹ ልጅ ወደ አባቱ ቤት ተመልሶ መሄድ ጀመረ፡፡ ገና በሩቅ እያለ አባቱ ዐየውና አዘነለት፡፡ ወደ ልጁ ሮጠና አቀፈው ሳመውም፡፡››

ልጁም፣ ‹አባቴ ሆይ፣ እግዚአብሔርንና አንተን በድዬአለሁ፡፡ ከእንግዲህ ልጅህ ልባል አይገባኝም› አለ፡፡

‹‹ነገር ግን አባቱ ከአገልጋዮቹ ለአንዱ እንዲህ ብሎ ነገረው፣ ‹ፈጥነህ ሂድና ምርጥ ልብስ አምጥተህ ለልጄ አልብሰው! ለጣቱም ቀለበት፤ ለእግሩም ጫማ አድርግለት፡፡ ከዚያም በልተን ፈንጠዝያ እናደርግ ዘንድ የሰባ ፍሪዳ አምጥተህ እረድ፣ ምክንያቱም ይህ ልጄ ሞቶ ነበር፣ አሁን ሕያው ሆኖአል! ጠፍቶ ነበር፣ አሁን ግን ተገኝቶአል!›››

‹‹ስለዚህ ሰዎቹ ፈንጠዝያ ማድረግ ጀመሩ፡፡ ብዙም ሳይቆይ፣ ታላቅ ወንድሙ ይሠራበት ከነበረው እርሻ ወደ ቤት መጣ፡፡ የሙዚቃና የዘፈን ድምፅም ሰማ፣ ምን እየሆነ ነው ብሎም ተገረመ፡፡››

‹‹ታላቁ ልጅም ታናሽ ወንድሙ ስለ መጣ ሰዎች እየተደሰቱ መሆናቸውን ባወቀ ጊዜ፣ በጣም ስለ ተቈጣ ወደ ቤት ለመግባት ፈቃደኛ አልሆነም፡፡ አባቱ ወጣና ገብቶ ከእነርሱ ጋር እንዲደሰት ለመነው፣ እርሱ ግን እምቢ አለ፡፡››

ታላቁ ልጅ አባቱን እንዲህ አለው፣ ‹እነዚህን ዓመታት ሁሉ በታማኝነት ለአንተ ሠርቼአለሁ! አንድም ቀን ስታዘኝ እምቢ ብዬህ አላውቅም። ይሁን እንጂ ከጓደኞቼ ጋር እንድደሰት አንድ ጥቦት ፍየል እንኳ እስከ አሁን ሰጥተኸኝ አታውቅም። ነገር ግን አሁን ይህ ኃጢአት በመሥራት ገንዘብህን ያባከነው ልጅህ ወደ ቤትህ በመጣ ጊዜ፣ የሰባ ፍሪዳ አረድህለት!›

‹‹አባቱ እንዲህ ብሎ መለሰለት፣ ‹ልጄ፣ አንተ ሁልጊዜ ከእኔ ጋር ነህ፣ ያለኝም ነገር ሁሉ የአንተ ነው፡፡ ነገር ግን ይህ ወንድምህ ሞቶ ነበር፣ አሁን ግን ሕያው ሆኖአል፡፡ ጠፍቶ ነበር፣ አሁን ግን ተገኝቶአል! ስለዚህ እኛ መደሰታችን ትክክል ነው›› አለው።
የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከሉቃስ 15፡11-32፡፡