አማርኛ: Open Bible Stories

Updated ? hours ago # views See on DCS

24. ዮሐንስ ኢየሱስን አጠመቀ

Image

የዘካርያስና የኤልሳቤጥ ልጅ ዮሐንስ አድጎ ነቢይ ሆነ፡፡ የሚኖረውም በምድረበዳ ነበር የሚበላውም፣ የበረሐ ማርና አንበጣ ነበር፣የሚለብሰውም ከግመል ፀጉር የተሠራ ልብስ ነበር፡፡

Image

ብዙ ሕዝብ ዮሐንስን ለመስማት ወደ ምድረ በዳ መጡ፡፡ እርሱም፣ ‹‹የእግዚአብሔር መንግሥት ቀርባለችና ንስሐ ግቡ›› እያለ ሰበከላቸው፡፡

Image

ሕዝቡ የዮሐንስን መልእክት በሰሙ ጊዜ፣ ብዙዎች ኃጢአታቸውን ተናዘዙ፣ ዮሐንስም አጠመቃቸው፡፡ ብዙ የሃይማኖት መሪዎችም ደግሞ በዮሐንስ ሊጠመቁ መጡ፣ ነገር ግን ንስሐ አልገቡም ወይም ኃጢአታቸውን አልተናዘዙም፡፡

Image

ዮሐንስ ለሃይማኖት መሪዎቹ እንዲህ አላቸው፣ ‹‹እናንተ መርዛማ እባቦች! ንስሐ ግቡና ባሕሪያችሁን ለውጡ። መልካም ፍሬ የማያፈራ ዛፍ ሁሉ ይቈረጥና ወደ እሳት ይጣላል።›› ነቢያት ‹‹እነሆ፣ መንገድህን የሚያዘጋጅ መልእክተኛዬን በፊትህ እልካለሁ።›› በማለት የተናገሩት ትንቢት በሐንስ ተፈጸመ።

Image

አንዳንድ አይሁዶች መሲሕ ስለ መሆኑ ዮሐንስን ጠየቁት፡፡ ዮሐንስ እንዲህ ብሎ መለሰ፣ ‹‹እኔ መሲሑ አይደለሁም፣ ነገር ግን ከእኔ በኋላ የሚመጣ አንድ ሰው አለ፡፡እርሱ እጅግ ታላቅ ስለሆነ እኔ የጫማውን ማሰሪያ እንኳ ልፈታ እንኳ አይገባኝም፡፡››

Image

በቀጣዩ ቀን፣ ኢየሱስ በዮሐንስ ለመጠመቅ መጣ፡፡ ዮሐንስ ባየው ጊዜ፣ ‹‹ተመልከቱ! እነሆ፣ የዓለምን ኃጢአት የሚያስወግድ የእግዚአብሔር በግ›› አለ፡፡

Image

ዮሐንስ ኢየሱስን፣ ‹‹እኔ አንተን ለማጥመቅ ተገቢ ሰው አይደለሁም። ይልቁን አንተ እኔን ማጥመቅ አለብህ›› አለው። ኢየሱስ ግን፣ ‹‹ ይህ መደረግ ያለበት ትክክለኛ ነገር ስለሆነ አንተ እኔን ማጥመቅ አለብህ›› አለው። ስለዚህ ኢየሱስ ከቶ ኃጢአት ባይሠራም እንኳ ዮሐንስ ኢየሱስን አጠመቀው።

Image

ኢየሱስ ከተጠመቀ በኋላ ከውኃው እንደ ወጣ፣ የእግዚአብሔር መንፈስ በርግብ አምሳል ታየና ወርዶ በእርሱ ላይ ዐረፈ፡፡ በዚሁ ጊዜ የእግዚአብሔር ድምፅ ከሰማይ፣ ‹‹አንተ እኔ የምወድህ ልጄ ነህ፣ በአንተም በጣም ደስ ብሎኛል›› ብሎ ተናገረ፡፡

Image

እግዚአብሔር ለዮሐንስ፣ ‹‹መንፈስ ቅዱስ ይወርድና አንተ በምታጠምቀው በአንድ ሰውዬ ላይ ያርፋል።ያ ሰያውዬ የእግዚአብሔር ልጅ ነው›› ብሎ ተናግሮት ነበር። አንድ አምላክ ብቻ አለ። ነገር ግን ዮሐንስ ኢየሱስን ባጠመቀው ጊዜ፣ እግዚአብሔር አብ ሲናገር ሰማ፣ እግዚአብሔር ወልድን ዐየ፣ እርሱም ኢየሱስ ነው፣ እንዲሁም መንፈስ ቅዱስን ዐየ።

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከማቴዎስ 3፤ ማርቆስ 1፡9-11፤ ሉቃስ 3፡1-23፡፡