24. ዮሐንስ ኢየሱስን አጠመቀ

የዘካርያስና የኤልሳቤጥ ልጅ ዮሐንስ አድጎ ነቢይ ሆነ፡፡ የሚኖረውም በምድረበዳ ነበር የሚበላውም፣ የበረሐ ማርና አንበጣ ነበር፣የሚለብሰውም ከግመል ፀጉር የተሠራ ልብስ ነበር፡፡

ብዙ ሕዝብ ዮሐንስን ለመስማት ወደ ምድረ በዳ መጡ፡፡ እርሱም፣ ‹‹የእግዚአብሔር መንግሥት ቀርባለችና ንስሐ ግቡ›› እያለ ሰበከላቸው፡፡

ሕዝቡ የዮሐንስን መልእክት በሰሙ ጊዜ፣ ብዙዎች ኃጢአታቸውን ተናዘዙ፣ ዮሐንስም አጠመቃቸው፡፡ ብዙ የሃይማኖት መሪዎችም ደግሞ በዮሐንስ ሊጠመቁ መጡ፣ ነገር ግን ንስሐ አልገቡም ወይም ኃጢአታቸውን አልተናዘዙም፡፡

ዮሐንስ ለሃይማኖት መሪዎቹ እንዲህ አላቸው፣ ‹‹እናንተ መርዛማ እባቦች! ንስሐ ግቡና ባሕሪያችሁን ለውጡ። መልካም ፍሬ የማያፈራ ዛፍ ሁሉ ይቈረጥና ወደ እሳት ይጣላል።›› ነቢያት ‹‹እነሆ፣ መንገድህን የሚያዘጋጅ መልእክተኛዬን በፊትህ እልካለሁ።›› በማለት የተናገሩት ትንቢት በሐንስ ተፈጸመ።

አንዳንድ አይሁዶች መሲሕ ስለ መሆኑ ዮሐንስን ጠየቁት፡፡ ዮሐንስ እንዲህ ብሎ መለሰ፣ ‹‹እኔ መሲሑ አይደለሁም፣ ነገር ግን ከእኔ በኋላ የሚመጣ አንድ ሰው አለ፡፡እርሱ እጅግ ታላቅ ስለሆነ እኔ የጫማውን ማሰሪያ እንኳ ልፈታ እንኳ አይገባኝም፡፡››

በቀጣዩ ቀን፣ ኢየሱስ በዮሐንስ ለመጠመቅ መጣ፡፡ ዮሐንስ ባየው ጊዜ፣ ‹‹ተመልከቱ! እነሆ፣ የዓለምን ኃጢአት የሚያስወግድ የእግዚአብሔር በግ›› አለ፡፡

ዮሐንስ ኢየሱስን፣ ‹‹እኔ አንተን ለማጥመቅ ተገቢ ሰው አይደለሁም። ይልቁን አንተ እኔን ማጥመቅ አለብህ›› አለው። ኢየሱስ ግን፣ ‹‹ ይህ መደረግ ያለበት ትክክለኛ ነገር ስለሆነ አንተ እኔን ማጥመቅ አለብህ›› አለው። ስለዚህ ኢየሱስ ከቶ ኃጢአት ባይሠራም እንኳ ዮሐንስ ኢየሱስን አጠመቀው።

ኢየሱስ ከተጠመቀ በኋላ ከውኃው እንደ ወጣ፣ የእግዚአብሔር መንፈስ በርግብ አምሳል ታየና ወርዶ በእርሱ ላይ ዐረፈ፡፡ በዚሁ ጊዜ የእግዚአብሔር ድምፅ ከሰማይ፣ ‹‹አንተ እኔ የምወድህ ልጄ ነህ፣ በአንተም በጣም ደስ ብሎኛል›› ብሎ ተናገረ፡፡

እግዚአብሔር ለዮሐንስ፣ ‹‹መንፈስ ቅዱስ ይወርድና አንተ በምታጠምቀው በአንድ ሰውዬ ላይ ያርፋል።ያ ሰያውዬ የእግዚአብሔር ልጅ ነው›› ብሎ ተናግሮት ነበር። አንድ አምላክ ብቻ አለ። ነገር ግን ዮሐንስ ኢየሱስን ባጠመቀው ጊዜ፣ እግዚአብሔር አብ ሲናገር ሰማ፣ እግዚአብሔር ወልድን ዐየ፣ እርሱም ኢየሱስ ነው፣ እንዲሁም መንፈስ ቅዱስን ዐየ።
የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከማቴዎስ 3፤ ማርቆስ 1፡9-11፤ ሉቃስ 3፡1-23፡፡