አማርኛ: Open Bible Stories

Updated ? hours ago # views See on DCS

8. እግዚአብሔር ዮሴፍንና ቤተ ሰቡን አዳነ

Image

ከብዙ ዓመታት በኋላ ያዕቆብ ባረጀ ጊዜ የከብቶቹን መንጋ የሚጠብቁት ልጆቹ እንዴት እንዳሉ እንዲያያቸው የሚወደው ልጁን ዮሴፍን ወደ ወንድሞቹ ላከው።

Image

አባታቸው ያዕቆብ ዮሴፍን ከወንድሞቹ ሁሉ አብዝቶ ይወድደው ስለ ነበረና አለቃቸው እንደሚሆንም ሕልም አልሞ ስለ ነበር ዮሴፍን ወንድሞቹ ጠሉት። ዮሴፍ ወደ ወንድሞቹ በመጣ ጊዜ ጠልፈው ለባሪያ ነጋዴዎች ሸጡት።

Image

የዮሴፍ ወንድሞች ወደ ቤት ከመመለሳቸው በፊት የዮሴፍን ልብስ ቀድደው በፍየል ደም ነከሩት። ከዚያም ዮሴፍን አውሬ በልቶታል ብለው በደም የተነከረውን የዮሴፍን ልብስ ለአባታቸው አሳዩት። ያዕቆብም በጣም አዘነ።

Image

የባሪያ ነጋዴዎቹ ዮሴፍን ወደ ግብፅ ወሰዱት። በዚያን ጊዜ ግብፅ በአባይ ወንዝ አጠገብ የምትገኝ ታላቅና ኃያል አገር ነበረች። የባሪያ ነጋዴዎቹ ዮሴፍን ባርያ አድርገው ለሀብታም የመንግሥት ባለ ሥልጣን ሸጡት። ዮሴፍ ጌታውን በደንብ አድርጎ አገለገለው። እግዚአብሔርም ዮሴፍን ባረከው።

Image

ነገር ግን የጌታው ሚስት ከዮሴፍ ጋር ለመተኛት ፈልጋ ሞከረች። ዮሴፍ ግን በእግዚአብሔር ፊት ኃጢአት አልሠራም ሲል እምቢ አላት። እሷም ስለ ተናደደችበት በሐሰት ከስሳው ተይዞ ወደ እሥር ቤት ተወሰደ። በእሥር ቤትም ቢሆን ለእግዚአብሔር ታማኝ ሆኖ ስለ ተገኘ እግዚአብሔር ባረከው።

Image

ምንም እንኳ ዮሴፍ ንጹሕ ሰው ቢሆንም ከሁለት ዓመት በኋላ አሁንም በእሥር ቤት ነበር። አንድ ሌሊት ግብፃውያን ‹ፈርዖን› የሚሉት ንጉሣቸው በጣም የታወከባቸውን ሁለት ሕልሞች አለመ። ከአማካሪዎቹ አንዳቸውም የሕልሙን ትርጕም ሊነግሩት አልቻሉም።

Image

እግዚአብሔር ለዮሴፍ ሕልም የመተርጐም ችሎታ ሰጥቶት ነበር። ስለዚህ ፈርዖን ዮሴፍን ከእሥር ቤት ወደ ራሱ አስመጣው። ዮሴፍ ሕልሞቹን ተረጐመለትና እንዲህ አለው። ‹‹እግዚአብሔር ሰባት የጥጋብ ዓመታትን ይልካል፣ ቀጥሎም ሰባት የረሀብ ዓመታት ይሆናሉ›› አለ።

Image

ፈርዖንም በዮሴፍ በጣም ስለተደሰተ በግብፅ ምድር ሁሉ ላይ ከእርሱ ቀጥሎ ሁለተኛ ባለ ሥልጣን አድርጎ ሾመው።

Image

ዮሴፍም ሕዝቡን በሰባቱ የመልካም ምርት ዓመታት በርካታ እህል በጎተራው እንዲያከማቹ ነገራቸው። የሰባቱ የረሀብ ዓመታት በመጡ ጊዜ ዮሴፍ ከጎተራው ለሕዝቡ እህል በመሸጡ በቂ የሚበላ ምግብ አገኙ።

Image

የረሀቡ አስከፊነት በግብፅ ብቻ ሳይሆን ያዕቆብና ቤተ ሰቡ በሚኖሩበት በከነዓን ምድርም ደግሞ ነበር።

Image

ስለዚህ ያዕቆብ ልጆቹ እህል እንዲሸምቱ ወደ ግብፅ ላካቸው። የዮሴፍ ወንድሞች ለእህል ሸመታ ሄደው በፊቱ በቆሙ ጊዜ ዮሴፍ መሆኑን አላስተዋሉትም። ዮሴፍ ግን አወቃቸው።

Image

ዮሴፍ ወንድሞቹን ተለውጠው እንደ ሆነ ለማየት ከፈተናቸው በኋላ እንዲህ አላቸው፣ ‹‹አትፍሩ እኔ ወንድማችሁ ዮሴፍ ነኝ። ለባርነት ስትሸጡኝ ክፉ ልታደርጉብኝ ሞከራችሁ፤ ነገር ግን እግዚአብሔር ክፉውን ለመልካም አደረገው። መጥታችሁ በግብፅ ኑሩ፤ እኔም ለእናንተና ለቤተ ሰቦቻችሁ የሚያስፈልጋችሁን አቀርብላችኋለሁ።››

Image

የዮሴፍ ወንድሞች ወደ አገራቸው ተመልሰው ዮሴፍ በሕይወት መኖሩን ለአባታቸው ለያዕቆብ በነገሩት ጊዜ ያዕቆብ በጣም ደስ አለው።

Image

ምንም እንኳ ያዕቆብ ሽማግሌ ቢሆንም ከመላው ቤተ ሰቡ ጋር ወደ ግብፅ ሄዶ በዚያ ኖሩ። ያዕቆብ ከመሞቱ በፊት ልጆቹን እያንዳንዳቸውን ባረካቸው።

Image

እግዚአብሔር ለአብርሃም የገባቸው የቃል ኪዳን ተስፋዎች ከአብርሃም ወደ ይስሐቅ ተላለፉ፤ ከዚያም ወደ ያዕቆብ፣ ቀጥሎም ወደ ዐሥራ ሁለቱ የያዕቆብ ልጆቹና ቤተ ሰቦቻቸው ተላለፈ። የዐሥራ ሁለቱ የያዕቆብ ልጆች ዘሮቻቸው ዐሥራ ሁለቱ የእስራኤል ነገዶች ሆኑ።

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከዘፍጥረት 37-50፡፡