8. እግዚአብሔር ዮሴፍንና ቤተ ሰቡን አዳነ

ከብዙ ዓመታት በኋላ ያዕቆብ ባረጀ ጊዜ የከብቶቹን መንጋ የሚጠብቁት ልጆቹ እንዴት እንዳሉ እንዲያያቸው የሚወደው ልጁን ዮሴፍን ወደ ወንድሞቹ ላከው።

አባታቸው ያዕቆብ ዮሴፍን ከወንድሞቹ ሁሉ አብዝቶ ይወድደው ስለ ነበረና አለቃቸው እንደሚሆንም ሕልም አልሞ ስለ ነበር ዮሴፍን ወንድሞቹ ጠሉት። ዮሴፍ ወደ ወንድሞቹ በመጣ ጊዜ ጠልፈው ለባሪያ ነጋዴዎች ሸጡት።

የዮሴፍ ወንድሞች ወደ ቤት ከመመለሳቸው በፊት የዮሴፍን ልብስ ቀድደው በፍየል ደም ነከሩት። ከዚያም ዮሴፍን አውሬ በልቶታል ብለው በደም የተነከረውን የዮሴፍን ልብስ ለአባታቸው አሳዩት። ያዕቆብም በጣም አዘነ።

የባሪያ ነጋዴዎቹ ዮሴፍን ወደ ግብፅ ወሰዱት። በዚያን ጊዜ ግብፅ በአባይ ወንዝ አጠገብ የምትገኝ ታላቅና ኃያል አገር ነበረች። የባሪያ ነጋዴዎቹ ዮሴፍን ባርያ አድርገው ለሀብታም የመንግሥት ባለ ሥልጣን ሸጡት። ዮሴፍ ጌታውን በደንብ አድርጎ አገለገለው። እግዚአብሔርም ዮሴፍን ባረከው።

ነገር ግን የጌታው ሚስት ከዮሴፍ ጋር ለመተኛት ፈልጋ ሞከረች። ዮሴፍ ግን በእግዚአብሔር ፊት ኃጢአት አልሠራም ሲል እምቢ አላት። እሷም ስለ ተናደደችበት በሐሰት ከስሳው ተይዞ ወደ እሥር ቤት ተወሰደ። በእሥር ቤትም ቢሆን ለእግዚአብሔር ታማኝ ሆኖ ስለ ተገኘ እግዚአብሔር ባረከው።

ምንም እንኳ ዮሴፍ ንጹሕ ሰው ቢሆንም ከሁለት ዓመት በኋላ አሁንም በእሥር ቤት ነበር። አንድ ሌሊት ግብፃውያን ‹ፈርዖን› የሚሉት ንጉሣቸው በጣም የታወከባቸውን ሁለት ሕልሞች አለመ። ከአማካሪዎቹ አንዳቸውም የሕልሙን ትርጕም ሊነግሩት አልቻሉም።

እግዚአብሔር ለዮሴፍ ሕልም የመተርጐም ችሎታ ሰጥቶት ነበር። ስለዚህ ፈርዖን ዮሴፍን ከእሥር ቤት ወደ ራሱ አስመጣው። ዮሴፍ ሕልሞቹን ተረጐመለትና እንዲህ አለው። ‹‹እግዚአብሔር ሰባት የጥጋብ ዓመታትን ይልካል፣ ቀጥሎም ሰባት የረሀብ ዓመታት ይሆናሉ›› አለ።

ፈርዖንም በዮሴፍ በጣም ስለተደሰተ በግብፅ ምድር ሁሉ ላይ ከእርሱ ቀጥሎ ሁለተኛ ባለ ሥልጣን አድርጎ ሾመው።

ዮሴፍም ሕዝቡን በሰባቱ የመልካም ምርት ዓመታት በርካታ እህል በጎተራው እንዲያከማቹ ነገራቸው። የሰባቱ የረሀብ ዓመታት በመጡ ጊዜ ዮሴፍ ከጎተራው ለሕዝቡ እህል በመሸጡ በቂ የሚበላ ምግብ አገኙ።

የረሀቡ አስከፊነት በግብፅ ብቻ ሳይሆን ያዕቆብና ቤተ ሰቡ በሚኖሩበት በከነዓን ምድርም ደግሞ ነበር።

ስለዚህ ያዕቆብ ልጆቹ እህል እንዲሸምቱ ወደ ግብፅ ላካቸው። የዮሴፍ ወንድሞች ለእህል ሸመታ ሄደው በፊቱ በቆሙ ጊዜ ዮሴፍ መሆኑን አላስተዋሉትም። ዮሴፍ ግን አወቃቸው።

ዮሴፍ ወንድሞቹን ተለውጠው እንደ ሆነ ለማየት ከፈተናቸው በኋላ እንዲህ አላቸው፣ ‹‹አትፍሩ እኔ ወንድማችሁ ዮሴፍ ነኝ። ለባርነት ስትሸጡኝ ክፉ ልታደርጉብኝ ሞከራችሁ፤ ነገር ግን እግዚአብሔር ክፉውን ለመልካም አደረገው። መጥታችሁ በግብፅ ኑሩ፤ እኔም ለእናንተና ለቤተ ሰቦቻችሁ የሚያስፈልጋችሁን አቀርብላችኋለሁ።››

የዮሴፍ ወንድሞች ወደ አገራቸው ተመልሰው ዮሴፍ በሕይወት መኖሩን ለአባታቸው ለያዕቆብ በነገሩት ጊዜ ያዕቆብ በጣም ደስ አለው።

ምንም እንኳ ያዕቆብ ሽማግሌ ቢሆንም ከመላው ቤተ ሰቡ ጋር ወደ ግብፅ ሄዶ በዚያ ኖሩ። ያዕቆብ ከመሞቱ በፊት ልጆቹን እያንዳንዳቸውን ባረካቸው።

እግዚአብሔር ለአብርሃም የገባቸው የቃል ኪዳን ተስፋዎች ከአብርሃም ወደ ይስሐቅ ተላለፉ፤ ከዚያም ወደ ያዕቆብ፣ ቀጥሎም ወደ ዐሥራ ሁለቱ የያዕቆብ ልጆቹና ቤተ ሰቦቻቸው ተላለፈ። የዐሥራ ሁለቱ የያዕቆብ ልጆች ዘሮቻቸው ዐሥራ ሁለቱ የእስራኤል ነገዶች ሆኑ።
የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከዘፍጥረት 37-50፡፡