26. ኢየሱስ አገልግሎቱን ጀመረ

ኢየሱስ የሰይጣንን ፈተና ካሸፈነ በኋላ፣ ይኖርበት ወደ ነበረው ወደ ገሊላ አውራጃ በመንፈስ ቅዱስ ኃይል ተሞልቶ ተመለሰ። ከቦታ ወደ ቦታም እየሄደ አስተማረ። ሁሉም ሰው ስለ እርሱ መልካም ይናገር ነበር።

ኢየሱስ በልጅነቱ ይኖረበት ወደ ነበረው ወደ ናዝሬት ከተማ ተመለሰ። በሰንበት ቀንም አይሁድ እግዚአብሔርን ወደሚያመልኩበት ስፈራ ሄደ። ያነብ ዘንድ የነቢዩን የኢሳይያስን ጥቅልል መጽሐፍ ሰጡት። ኢየሱስ ጥቅልል መጽሐፉን ከፍቶ በከፊል ለሕዝቡ አነበበላቸው።

ኢየሱስ፣ ‹‹ለድሆች የምሥራችን፣ ለተማረኩት ነጻትን፣ ለዕውሮች ማየትን፣ ለታሰሩትም መፈታትን እሰብክ ዘንድ እግዚአብሔር መንፈሱን ሰጥቶኛል፡፡ ይህች የተወደደችው የጌታ ዓመት ነች›› ብሎ አነበበ፡፡

ከዚያም ኢየሱስ ተቀመጠ፡፡ ሁላቸውም ቀርበው ተመለከቱት፡፡አሁን ያነበበው የእግዚአብሔር ቃል ስለ መሲሑ የሚናገር መሆኑን ያውቁ ነበር፡፡ ኢየሱስ፣ ‹‹ይህ ያነበብኩላችሁ ቃል ልክ አሁን እየተፈጸመ ነው ›› አለ፡፡ ሕዝቡ ሁሉ ተደነቁ፡፡ ‹‹ይህ የዮሴፍ ልጅ አይደለምን?›› አሉ፡፡

ከዚያም ኢየሱስ፣ ‹‹ነቢይ በገዛ አገሩ እንደማይከበር የታወቀ ነው፣ በነቢዩ ኤልያስ ዘመን፣ በእስራኤል ብዙ መበለቶች ነበሩ፡፡ ነገር ግን ለሦስት ዓመት ተኩል ዝናብ ባልዘነበ ጊዜ መበለት የሆነችውን ሴት እንዲረዳ እግዚአብሔር ኤልያስ ከሌላ አገር ወደ ሆነችው መበለት ላከ እንጂ ከእስራኤል የሆነች መበለትን እንዲረዳ አልላከውም፡፡››

ኢየሱስ መናገሩን በቀጠል፣ ‹‹በነቢዩ ኤልሳዕ ዘመንም በእስራኤል የቆዳ ሕመም የያዛቸው ብዙ ሰዎች ነበሩ፡፡ ነገር ግን ኤልሳዕ አንዳቸውንም አልፈወሰም፡፡ ነገር ግን የእስራኤል ጠላቶች አዛዥ የነበረውን የንዕማንን ቆዳ በሽታ ብቻ ፈወሰ፡፡›› ኢየሱስን ይሰሙ የነበሩት ሕዝብ አይሁዳውያን ነበሩ፡፡ ስለዚህ ይህን ሲናገር በሰሙት ጊዜ ተናደዱበት፡፡

የናዝሬት ሕዝብ ኢየሱስን ከአምልኮው ቦታ ጐተቱትና ወርውረው ሊገድሉት ወደ ገደል አፋፍ ወሰዱት፡፡ ነገር ግን ኢየሱስ በሕዝቡ መካከል ተራመደና ወደ ናዝሬት ከተማ ሄደ፡፡

ከዚያም ኢየሱስ በገሊላ አውራጃ ሁሉ ተዘዋወረ፣ ብዙ ሕዝብም ወደ እርሱ መጡ፡፡ ማየት፣ መራመድ፣ መስማት፣ ወይም መናገር የማይችሉትን ጨምሮ ብዙ የታመሙ ወይም የአካል ጕዳተኞች የሆኑ ሰዎችን ወደ እርሱ አመጡ ኢየሱስም ፈወሳቸው፡፡

አጋንንት የነበሩባቸው ብዙ ሰዎችን ወደ ኢየሱስ አመጡ፡፡ በኢየሱስ ትእዛዝ አጋንንቱ ከሰዎቹ ወጡ፣ ብዙ ጊዜም፣ ‹‹አንተ የእግዚአብሔር ልጅ ነህ!›› ብለው ይጮኹ ነበር፡፡ ሕዝቡ ተደነቁና እግዚአብሔርን አመለኩ፡፡

ከዚያም ኢየሱስ የእርሱ ሐዋርያት ተብለው የተጠሩትን ዐሥራ ሁለት ሰዎች መረጠ፡፡ ሐዋርያቱ ከኢየሱስ ጋር እየተጓዙ ከእርሱ ተማሩ፡፡
የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከማቴዎስ 4፡12-25፤ ማርቆስ 1፡14-15፣ 35-39፤ 3፡13-21፤ ሉቃስ 4፡14-30፣ 38-44፡፡