አማርኛ: Open Bible Stories

Updated ? hours ago # views See on DCS

38. ኢየሱስ ተላልፎ ተሰጠ

Image

አይሁድ በያመቱ የፋሲካን በዓል ያከብሩ ነበር፡፡ ይህም በዓል ከብዙ ምእት ዓመታት በፊት እግዚአብሔር ቅድመ አያቶቻቸውን ከግብፅ ባርነት እንዴት እንዳዳናቸው ለማስታወስ የሚከበር ነበር፡፡ ኢየሱስ በይፋ መስበኩንና ማስተማሩን ከጀመረ ከሦስት ዓመት ገደማ በኋላ፣ ይህን ፋሲካ በኢየሩሳሌም ከእነርሱ ጋር ሊያከብር እንደ ፈለገ፣ በዚያም እንደሚገደል ለደቀ መዛሙርቱ ነገራቸው፡፡

Image

ከኢየሱስ ደቀ መዛሙርት አንዱ ይሁዳ ተብሎ ይጠራ ነበር፡፡ ይሁዳ የሐዋርያቱ ገንዘብ ያዥ ነበር፣ ነገር ግን ገንዘብ ይወድ ነበርና ብዙ ጊዜ ከከረጢቱ ውስጥ ገንዘብ ይሰርቅ ነበር፡፡ ኢየሱስና ደቀ መዛሙርቱ ወደ ኢየሩሳሌም ከደረሱ በኋላ፣ ይሁዳ ወደ አይሁድ መሪዎች ሄደና ገንዘብ ከሰጡት ኢየሱስን አሳልፎ ሊሰጣቸው እንደሚችል ነገራቸው፡፡ ኢየሱስ መሲሕ መሆኑን የአይሁድ መሪዎች እንደ ካዱና ሊገድሉት ያሤሩ እንደ ነበር ያውቅ ነበር፡፡

Image

የአይሁድ መሪዎችም በሊቀ ካህናቱ ተመርተው፣ ኢየሱስን አሳልፎ እንዲሰጣቸው ለይሁዳ ሠላሳ ጥሬ ብር ከፈሉት፡፡ ልክ ነቢያት እንደ ተነበዩት ይህ ሆነ፡፡ ይሁዳም ተስማማ፣ ገንዘቡንም ተቀብሎ ሄደ፡፡ ኢየሱስን እንዲይዙት ሊረዳቸው አጋጣሚ መፈለግ ጀመረ፡፡

Image

በኢየሩሳሌም፣ ኢየሱስ ከደቀ መዛሙርቱ ጋር ፋሲካን አከበረ፡፡ በፋሲካው ምግብ ጊዜ ኢየሱስ እንጀራን አንሥቶ ቈረሰ፡፡ እንዲህም አለ፣ ‹‹እንካችሁ ይህንን ብሉ፡፡ ይህ ስለ እናንተ የተሰጠ ሥጋዬ ነው፡፡ ይህንን ለመታሰቢያዬ አድርጉት፡፡›› በዚህ ዓይነት ኢየሱስ ሥጋው ስለ እነርሱ እንደሚሠዋ ነገራቸው፡፡

Image

ከዚያም ኢየሱስ ጽዋን አንሣና፣ ‹‹ይህንን ጠጡ፡፡ ለኃጢአት ይቅርታ የሚፈስ የዐዲስ ኪዳን ደሜ ነው፡፡ ይህንን በጠጣችሁ ጊዜ ሁሉ ለመታሰቢያዬ አድርጉት፡፡››

Image

ከዚያም ኢየሱስ ደቀ መዛሙርቱን፣ ‹‹ከእናንተ አንዱ እኔን አሳልፎ ይሰጠኛል›› አላቸው፡፡ ደቀ መዛሙርቱ ደንግጠው፣ እንዲህ ያለ ነገር ማን ያደርጋል ብለውም ጠየቁት፡፡ ኢየሱስ፣ ‹‹ይህንን ቊራሽ እንጀራ የምሰጠው ሰው እኔን አሳልፎ የሚሰጠኝ እርሱ ነው›› አለ፡፡ ከዚያ በኋላ እንጀራውን ለይሁዳ ሰጠው፡፡

Image

ይሁዳ እንጀራውን ከተቀበለ በኋላ፣ ሰይጣን ገባበት፡፡ ይሁዳ ኢየሱስን እንዲይዙት የአይሁድ መሪዎችን ሊረዳቸው ሄደ፡፡ ጊዜው ማታ ነበር፡፡

Image

ኢየሱስና ደቀ መዛሙርቱ እራት ከበሉ በኋላ ወደ ደብረ ዘይት ሄዱ፡፡ ኢየሱስ፣ ‹‹ዛሬ ማታ ሁላችሁም እኔን ብቻዬን ትተዉኛላችሁ፡፡ ‹እረኛውን እመታለሁ፤ በጎቹም ሁሉ ይበተናሉ› ተብሎ ተጽፎአል›› አለ፡፡

Image

ጴጥሮስ፣ ‹‹ሌሎቹ ሁሉ ቢተዉህ እንኳ፣ እኔ ግን አላደርገውም!›› ብሎ መለሰ፡፡ በዚያን ጊዜ ኢየሱስ ጴጥሮስን እንዲህ አለው፣ ‹‹ሰይጣን ሁላችሁንም እንደ ስንዴ ሊያበጥራችሁ፥ ይፈልጋል፣ ነገር ግን ጴጥሮስ እምነትህ እንዳይደክም ጸልዬልሃለሁ፡፡ እንደዚያም ሆኖ ግን ዛሬ ማታ ዶሮ ከመጮኹ በፊት እንደውም አላውቀውም ብለህ ሦስት ጊዜ ትክደኛለህ፡፡››

Image

በዚያን ጊዜ ጴጥሮስ ለኢየሱስ፣ ‹‹የምሞት እንኳ ቢሆን፣ ከቶ አልክድህም›› አለው፡፡ ሌሎቹም ደቀ መዛሙርት ሁሉ ይህንኑ አሉ፡፡

Image

ከዚያ በኋላ ኢየሱስ ከደቀ መዛሙርቱ ጋር ጌቴሴማኒ ወደሚባል ቦታ ሄደ፡፡ ኢየሱስ ወደ ፈተና እንዳይገቡ እንዲጸልዩ ለደቀ መዛሙርቱ ነገራቸው፡፡ ከዚያም ኢየሱስ ብቻውን ሊጸልይ ሄደ፡፡

Image

ኢየሱስ፣ ‹‹አባቴ ሆይ፣ ቢቻልስ ይህን የመከራ ጽዋ እንዳልጠጣው አድርግ፡፡ ነገር ግን ፈቃድህ ይሁን›› ብሎ ሦስት ጊዜ ጸለየ። ኢየሱስ በጣም ታወከ፤ ላቡም እንደ ደም ነጠብጣብ ነበረ፡፡ እግዚአብሔርም እንዲያበረታታው መልአክ ላከ፡፡

Image

ከእያንዳንዱ የጸሎት ጊዜ በኋላ ኢየሱስ ወደ ደቀ መዛሙርቱ ተመልሶ ይመጣ ነበር። እነርሱ ግን ተኝተው ነበር፡፡ ሦስተኛ ተመልሶ በመጣ ጊዜ ግን፣ ‹‹ተነሡ! አሳልፎ የሚሰጠኝ ደርሷል›› አለ፡፡

Image

ይሁዳ ከአይሁድ መሪዎች፣ ከወታደሮችና ከብዙ ሕዝብ ጋር መጣ፡፡ ሰይፍና ዱላ ይዘው ነበር፡፡ ይሁዳ ወደ ኢየሱስ መጣና፣ ‹‹መምህር ሆይ፣ ሰላም ለአንተ ይሁን›› ብሎ ሳመው፡፡ ይህም የአይሁድ መሪዎች ማንን እንደሚይዙ ምልክት ነበር፡፡ ከዚያም ኢየሱስ፣ ‹‹ይሁዳ፣ በመሳም አሳልፈህ ትሰጠኛለህን?›› አለ፡፡

Image

ወታደሮቹ ኢየሱስን ሲይዙት፣ ጴጥሮስ ሰይፉን መዘዘና የሊቀ ካህናቱን አገልጋይ ጆሮ ቈረጠ፡፡ ኢየሱስ፣ ‹‹ሰይፍህን ወደ ስፍራው መልስ! ይከላከሉልኝ ዘንድ የመላእክት ሠራዊት እንዲልክልኝ አባቴን መጠየቅ እችል ነበር፤ ነገር ግን አባቴን መታዘዝ አለብኝ›› አለው፡፡ ከዚያም ኢየሱስ የሰውዬውን ጆሮ ፈወሰው፡፡ ኢየሱስ ከተያዘ በኋላ ደቀ መዛሙርቱ ሁሉ ሸሹ፡፡

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከማቴዎስ 26፡14-56፤ ማርቆስ 14፡10-50፤ ሉቃስ 22፡1-53፤ ዮሐንስ 12፡6፤ 18፡1-11፡፡