አማርኛ: Open Bible Stories

Updated ? hours ago # views See on DCS

18. ለሁለት የተከፈለው መንግሥት

Image

ከብዙ ዓመታት በኋላ፣ ዳዊት ሞተ፣ ልጁ ሰሎሞንም እስራኤልን ይገዛ ጀመር፡፡ እግዚአብሔር ሰሎሞንን ተናገረውና ከሁሉ በላይ ምን እንደሚፈልግ ጠየቀው፡፡ ሰሎሞን ጥበብን እንዲሰጠው በለመነ ጊዜ፣እግዚዘብሔር ደስ አለውና በዓለም ላይ ካሉ ሰዎች ሁሉ በላይ እጅግ በጣም ጠቢብ ሰው አደረገው፡፡ ሰሎሞን ብዙ ነገሮችን የሚያውቅ በጣም ጠቢብ ፈራጅ ሆነ፡፡ ደግሞም እግዚአብሔር በጣም ባለ ጠጋ አደረገው፡፡

Image

ሰሎሞን በኢየሩሳሌም አባቱ ዳዊት ሊሠራ ያቀደውንና ለግንባታው የሚያስፈልጉ ነገሮች የሰበሰበለትን ቤተ መቅደስ ሠራ፡፡ አሁን ሕዝቡ በመገናኛው ድንኳ ፈንታ በቤተ መቅደስ እግዚአብሔርን አመለኩ መሥዋዕትንም አቀረቡለት፡፡ እግዚአብሔር መጥቶ በቤተ መቅደሱ ሆነ፣ በዚያም ከሕዝቡ ጋር ኖረ፡፡

Image

ነገር ግን ሰሎሞን የሌሎች አገሮች ዜጎች የሆኑ ሴቶችን ወደደ። ከሞላ ጐደል 1000 የሚሆኑ ብዙ ሴቶችን በማግባት ለእግዚአብሔር አልታዘዘም! ከእነዚህ ሴቶች ብዙዎቹ ከሌላ አገሮች የመጡ ነበሩ፣ እነርሱም ጣዖቶቻቸውን አምጥተው ማምለካቸውን ቀጠሉ። ሰሎሞንም በሸመገለ ጊዜ፣ እርሱም ደግሞ የእነርሱን አማልክት አመለከ።

Image

እግዚአብሔር በሰሎሞን ላይ ተቈጣ፣ ሰሎሞን ባለመታመኑ እንደ መቀጣጫ እንዲሆን ከእርሱ ሞት በኋላ የእስራኤልን ሕዝብ ወደ ሁለት መንግሥታት እንደሚከፍል ተናገረ።

Image

ሰሎሞን ከሞተ በኋላ ልጁ ሮብዓም ነገሠ፡፡ ሮብዓም ሞኝ ነበረ፡፡ የእስራኤል ሕዝብ በሙሉ ንጉሥነቱን ሊያጸድቁለት ተሰብስበው መጡ፡፡ ሰሎሞን ብዙ ከባድ ሥራ እንዳሠራቸውና ብዙ ግብር እንዳስከፈላቸው ለሮብዓም ቅሬታቸውን ተናገሩ፡፡

Image

ሮብዓም በሞኝነት እንዲህ ብሎ መለሰላቸው፣ ‹‹አባቴ ሰሎሞን ከባድ ሥራ አሠርቶናል ብላችሁ ዐስባችኋል፣ ነገር ግን እኔ ከእርሱ የባሰ ከባድ ሥራ አሠራችኋለሁ፣ ከእርሱ የባሰም በኃይል እቀጣችኋለሁ፡፡››

Image

ስለዚህ ዐሥሩ የእስራኤል ሕዝብ ነገዶች በሮብዓም ላይ ዓመፁ፡፡ ሁለት ነገዶች ብቻ ለእርሱ ባላቸው ታማኝነት ቀጠሉ፡፡ እነዚህ ሁለት ነገዶች የይሁዳ መንግሥት ሆኑ፡፡

Image

በሮብዓም ላይ ያመፁት ሌሎቹ ዐሥር የእስራኤል ሕዝብ ነገዶች ኢዮርብዓም የተባለውን ሰው ንጉሣቸው አድርገው ሾሙት፡፡ በምድሪቱ ሰሜናዊ ክፍል መንግሥታቸውን አቋቋሙ፤ የእስራኤል መንግሥት ተብለውም ተጠሩ፡፡

Image

ኢዮርብዓም በእግዚአብሔር ላይ ዓመፀና ሕዝቡ ኃጢአት እንዲሠሩ አደረገ፡፡ በይሁዳ መንግሥት ባለው ቤተ መቅደስ እግዚአብሔርን በማምለክ ፈንታ ሕዝቡ ያመልኩአቸው ዘንድ ሁለት ጣዖታትን ሠራላቸው፡፡

Image

የይሁዳና የእስራኤል መንግሥታት ጠላቶች ሆኑና ብዙ ጊዜ እርስ በርስ ተዋጉ።

Image

በዐዲሲቱ የእስራኤል መንግሥት የነገሡት ነገሥታቱ ሁሉ ክፉዎች ነበሩ። ከእነዚህ ነገሥታት አብዛኞቹ፣ በእነርሱ ቦታ መንገሥ በፈለጉ ሌሎች እስራኤላውያን ተገደሉ።

Image

ነገሥታቱ ሁሉና አብዛኞቹ የእስራኤል መንግሥት ሕዝብ ጣዖትን አመለኩ፡፡ የጣዖት አምልኮአቸው ብዙውን ጊዜ ግብረ ገብነት የጐደለው የግብረ ሥጋ ግንኙነትና አንዳንድ ጊዜ እንደውም ልጆችን መሠዋትንም ያካተተ ነበር፡፡

Image

የይሁዳ ነገሥታት የዳዊት ዝርያዎች ነበሩ፡፡ ከእነዚህ ነገሥታት አንዳንዶቹ በቅንነት የገዙና እግዚአብሔርን ያመለኩ ጥሩ ሰዎች ነበሩ፡፡ ነገር ግን አብዛኞቹ የይሁዳ ነገሥታት ክፉዎችና ብልሹዎች ነበሩ፣ ጣዖታትንም ያመልኩ ነበር፡፡ አንዳንዶቹ ነገሥታት ልጆቻቸውን እንኳ ለሐሰት አማልክት ሠውተዋል፡፡ ደግሞም አብዛኞቹ የይሁዳ ሕዝብ በእግዚአብሔር ላይ ዓመፁ፤ ሌሎች አማልክትንም አመለኩ፡፡

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከ1ኛ ነገሥት 1-6፤ 11-12፡፡