18. ለሁለት የተከፈለው መንግሥት

ከብዙ ዓመታት በኋላ፣ ዳዊት ሞተ፣ ልጁ ሰሎሞንም እስራኤልን ይገዛ ጀመር፡፡ እግዚአብሔር ሰሎሞንን ተናገረውና ከሁሉ በላይ ምን እንደሚፈልግ ጠየቀው፡፡ ሰሎሞን ጥበብን እንዲሰጠው በለመነ ጊዜ፣እግዚዘብሔር ደስ አለውና በዓለም ላይ ካሉ ሰዎች ሁሉ በላይ እጅግ በጣም ጠቢብ ሰው አደረገው፡፡ ሰሎሞን ብዙ ነገሮችን የሚያውቅ በጣም ጠቢብ ፈራጅ ሆነ፡፡ ደግሞም እግዚአብሔር በጣም ባለ ጠጋ አደረገው፡፡

ሰሎሞን በኢየሩሳሌም አባቱ ዳዊት ሊሠራ ያቀደውንና ለግንባታው የሚያስፈልጉ ነገሮች የሰበሰበለትን ቤተ መቅደስ ሠራ፡፡ አሁን ሕዝቡ በመገናኛው ድንኳ ፈንታ በቤተ መቅደስ እግዚአብሔርን አመለኩ መሥዋዕትንም አቀረቡለት፡፡ እግዚአብሔር መጥቶ በቤተ መቅደሱ ሆነ፣ በዚያም ከሕዝቡ ጋር ኖረ፡፡

ነገር ግን ሰሎሞን የሌሎች አገሮች ዜጎች የሆኑ ሴቶችን ወደደ። ከሞላ ጐደል 1000 የሚሆኑ ብዙ ሴቶችን በማግባት ለእግዚአብሔር አልታዘዘም! ከእነዚህ ሴቶች ብዙዎቹ ከሌላ አገሮች የመጡ ነበሩ፣ እነርሱም ጣዖቶቻቸውን አምጥተው ማምለካቸውን ቀጠሉ። ሰሎሞንም በሸመገለ ጊዜ፣ እርሱም ደግሞ የእነርሱን አማልክት አመለከ።

እግዚአብሔር በሰሎሞን ላይ ተቈጣ፣ ሰሎሞን ባለመታመኑ እንደ መቀጣጫ እንዲሆን ከእርሱ ሞት በኋላ የእስራኤልን ሕዝብ ወደ ሁለት መንግሥታት እንደሚከፍል ተናገረ።

ሰሎሞን ከሞተ በኋላ ልጁ ሮብዓም ነገሠ፡፡ ሮብዓም ሞኝ ነበረ፡፡ የእስራኤል ሕዝብ በሙሉ ንጉሥነቱን ሊያጸድቁለት ተሰብስበው መጡ፡፡ ሰሎሞን ብዙ ከባድ ሥራ እንዳሠራቸውና ብዙ ግብር እንዳስከፈላቸው ለሮብዓም ቅሬታቸውን ተናገሩ፡፡

ሮብዓም በሞኝነት እንዲህ ብሎ መለሰላቸው፣ ‹‹አባቴ ሰሎሞን ከባድ ሥራ አሠርቶናል ብላችሁ ዐስባችኋል፣ ነገር ግን እኔ ከእርሱ የባሰ ከባድ ሥራ አሠራችኋለሁ፣ ከእርሱ የባሰም በኃይል እቀጣችኋለሁ፡፡››

ስለዚህ ዐሥሩ የእስራኤል ሕዝብ ነገዶች በሮብዓም ላይ ዓመፁ፡፡ ሁለት ነገዶች ብቻ ለእርሱ ባላቸው ታማኝነት ቀጠሉ፡፡ እነዚህ ሁለት ነገዶች የይሁዳ መንግሥት ሆኑ፡፡

በሮብዓም ላይ ያመፁት ሌሎቹ ዐሥር የእስራኤል ሕዝብ ነገዶች ኢዮርብዓም የተባለውን ሰው ንጉሣቸው አድርገው ሾሙት፡፡ በምድሪቱ ሰሜናዊ ክፍል መንግሥታቸውን አቋቋሙ፤ የእስራኤል መንግሥት ተብለውም ተጠሩ፡፡

ኢዮርብዓም በእግዚአብሔር ላይ ዓመፀና ሕዝቡ ኃጢአት እንዲሠሩ አደረገ፡፡ በይሁዳ መንግሥት ባለው ቤተ መቅደስ እግዚአብሔርን በማምለክ ፈንታ ሕዝቡ ያመልኩአቸው ዘንድ ሁለት ጣዖታትን ሠራላቸው፡፡

የይሁዳና የእስራኤል መንግሥታት ጠላቶች ሆኑና ብዙ ጊዜ እርስ በርስ ተዋጉ።

በዐዲሲቱ የእስራኤል መንግሥት የነገሡት ነገሥታቱ ሁሉ ክፉዎች ነበሩ። ከእነዚህ ነገሥታት አብዛኞቹ፣ በእነርሱ ቦታ መንገሥ በፈለጉ ሌሎች እስራኤላውያን ተገደሉ።

ነገሥታቱ ሁሉና አብዛኞቹ የእስራኤል መንግሥት ሕዝብ ጣዖትን አመለኩ፡፡ የጣዖት አምልኮአቸው ብዙውን ጊዜ ግብረ ገብነት የጐደለው የግብረ ሥጋ ግንኙነትና አንዳንድ ጊዜ እንደውም ልጆችን መሠዋትንም ያካተተ ነበር፡፡

የይሁዳ ነገሥታት የዳዊት ዝርያዎች ነበሩ፡፡ ከእነዚህ ነገሥታት አንዳንዶቹ በቅንነት የገዙና እግዚአብሔርን ያመለኩ ጥሩ ሰዎች ነበሩ፡፡ ነገር ግን አብዛኞቹ የይሁዳ ነገሥታት ክፉዎችና ብልሹዎች ነበሩ፣ ጣዖታትንም ያመልኩ ነበር፡፡ አንዳንዶቹ ነገሥታት ልጆቻቸውን እንኳ ለሐሰት አማልክት ሠውተዋል፡፡ ደግሞም አብዛኞቹ የይሁዳ ሕዝብ በእግዚአብሔር ላይ ዓመፁ፤ ሌሎች አማልክትንም አመለኩ፡፡
የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከ1ኛ ነገሥት 1-6፤ 11-12፡፡