6. እግዚአብሔር ለይስሐቅ ሚስት አዘጋጀለት

አብርሃም በጣም ባረጀ ጊዜ ይስሐቅ ዕድሜው ለአቅመ አዳም ደረሰ። ስለዚህ አብርሃም ከአገልጋዮቹ አንዱን ወደ ዘመዶቹ ምድር ሄዶ ለልጁ ለይስሐቅ ሚስት እንዲያመጣለት ላከው።

አገልጋዩም የአብርሃም ዘመዶች ወደሚኖሩበት ምድር ከረጅም ጒዞ በኋላ ደረሰ። እግዚአብሔርም የተላከውን የአብርሃምን አገልጋይ ወደ ርብቃ መራው። ርብቃ የአብርሃም ወንድም የልጅ ልጅ ነበረች።

ርብቃ ቤተ ሰቦቿን ትታ ከአገልጋዩ ጋር ወደ ይስሐቅ ቤት ለመሄድ ተስማማች። እንደ ደረሰችም ይስሐቅ አገባት።

ከረጅም ጊዜ በኋላ አብርሃም ሲሞት እግዚአብሔር ከአብርሃም ጋር የገባው የተስፋ ቃል ኪዳን ሁሉም ወደ ይስሐቅ ተላለፈ። እግዚአብሔር ለአብርሃም ማንም ሊቆጥር የማይችል ዘር እንደሚኖረው ተስፋ ሰጥቶት ነበር። ይሁን እንጂ የይስሐቅ ሚስት ርብቃ ልጅ ልትወልድ አልቻለችም።

ይስሐቅ እግዚአብሔርን ለመነ፣ እግዚአብሔርም ርብቃ መንታ ልጆችን እንድታረግዝ ፈቀደ። ሁለቱ ልጆች በርብቃ ማኅፀን ሳሉ እርስ በርሳቸው ይታገሉ ነበር። ርብቃም በማኅፀንዋ እየሆነ ያለው ምን እንደሆነ እግዚአብሔርን ጠየቀች።

እግዚአብሔርም ርብቃን አላት፣ ‹‹በማኅፀንሽ ካሉት ከሁለቱ ልጆችሽ ሁለት ሕዝቦች ይወጣሉ። እነርሱም እርስ በርሳቸው ይታገላሉ። ታላቁም ታናሹን ያገለግላል›› አላት።

የርብቃ ልጆች በተወለዱ ጊዜ ታላቁ ልጅ ቀይና ፀጉራም ሆኖ ወጣ፤ ‹ኤሳው› ሲሉትም ስም አወጡለት፤ ታናሹም ልጅ የኤሳውን ተረከዝ ይዞ ወጣ፤ ስሙንም ‹ያዕቆብ› ሲሉ አወጡለት።
የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከዘፍጥረት 24፡1-25፤ 26፡፡