አማርኛ: Open Bible Stories

Updated ? hours ago # views See on DCS

28. ባለ ጠጋው ወጣት

Image

አንድ ቀን አንድ ባለጠጋ ወጣት ገዥ ወደ ኢየሱስ መጣና፣ ‹‹ቸር መምህር፣ የዘላለምን ሕይወት እንድወርስ ምን ላድርግ?›› ብሎ ጠየቀው፡፡ ኢየሱስ፣ ‹‹ስለ ምን ‹ቸር› ትለኛለህ? ቸር አንድ ብቻ አለ፣ እርሱም እግዚአብሔር ነው፡፡ ነገር ግን አንተ የዘላለም ሕይወት እንዲኖርህ ከፈለግህ ለእግዚአብሔር ሕግ ታዘዝ›› አለው፡፡

Image

‹‹የትኞቹን ልታዘዝ?›› ብሎ ጠየቀው፡፡ ኢየሱስ እንዲህ ብሎ መለሰለት፣ ‹‹አትግደል፡፡ አታመንዝር፡፡ አትስረቅ፡፡ አትዋሽ፡፡ አባትህንና እናትህን አክብር፣ ባልጀራህንም እንደ ራስህ ውደድ፡፡››

Image

ነገር ግን ወጣቱ፣ ‹‹ከልጅነቴ ጀምሮ እነዚህን ሕጎች ሁሉ ፈጽሜአለሁ፡፡ ለዘላለም ለመኖር ሌላስ ምን ማድረግ ያስፈልገኛል?›› አለ፡፡ ኢየሱስ ዐየውና ወደደው፡፡

Image

ኢየሱስ፣ ‹‹ፍጹም ለመሆን ብትፈልግ፣ ያለህን ንብረት ሁሉ ሽጥና ገንዘቡን ለድሆች ስጥ፣ በሰማይም የሀብት መዝገብ ታገኛለህ፡፡ ከዚያም በኋላ ናና ተከተለኝ›› ብሎ መለሰለት፡፡

Image

ወጣቱ፣ ኢየሱስ የተናገረውን በሰማ ጊዜ፣ በጣም ሀብታም ነበርና ያለውን ንብረት ሁሉ ለድኻ መስጠት ስላልፈለገ በጣም ዐዘነ፡፡ ከኢየሱስ ፊቱን አዞረና ሄደ፡፡

Image

በዚያን ጊዜ ኢየሱስ ደቀ መዛሙርቱን እንዲህ አላቸው፣ ‹‹ለሀብታሞች ወደ እግዚአብሔር መንግሥት መግባት እጅግ አስቸጋሪ ነው! አዎ፣ ሀብታም ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ከሚገባ ይልቅ ግመል በመርፌ ቀዳዳ ቢያልፍ ይቀላል፡፡››

Image

ደቀ መዛሙርቱ ኢየሱስ የተናገረውን በሰሙ ጊዜ ደነገጡና፣ ‹‹ታዲያ ማን ሊድን ይችላል?›› አሉ፡፡

Image

ኢየሱስ ደቀ መዛሙርቱን ተመለከተና፣ ‹‹ይህ በሰው ዘንድ አይቻልም፣ በእግዚአብሔር ዘንድ ግን ሁሉ ይቻላል›› አለ፡፡

Image

ጴጥሮስ ኢየሱስን፣ ‹‹እኛ ሁሉን ትተን ተከተልንህ፡፡ ዋጋችን ምን ይሆን?›› አለው፡፡

Image

ኢየሱስ እንዲህ ብሎ መለሰለት፣ ‹‹ስለ እኔ ቤቶችን፣ ወንድሞችን፣ እኅቶችን፣ አባትን፣ እናትን ወይም ንብረትን የተወ ሁሉ መቶ እጥፍ ይቀበላል፤ የዘላለምንም ሕይወት ይወርሳል፡፡ ነገር ግን ፊተኞች የሆኑ ብዙዎች ኋለኞች ይሆናሉ፣ ኋለኞችም የሆኑ ብዙዎች ፊተኞች ይሆናሉ፡፡››

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከማቴዎስ 19፡16-30፤ ማርቆስ 10፡17-31፤ ሉቃስ 18፡18-30፡፡