20. ምርኮና ከምርኮ መመለስ

የእስራኤል መንግሥትና የይሁዳ መንግሥት ሁለቱም በእግዚአብሔር ላይ ኃጢአት ሠሩ፡፡ እግዚአብሔር ከእነርሱ ጋር በሲና ተራራ ያደረገውን ቃል ኪዳን አፈረሱ፡፡ እግዚአብሔርም ንስሐ እንዲገቡና እንደገና እንዲያመልኩት ሊያስጠነቅቃቸው ነቢያቱን ላከ፣ እነርሱ ግን አንታዘዝም አሉ፡፡

ስለዚህ እግዚአብሔር ጠላቶቻቸው እንዲያጠፉአቸው በመፍቀድ ሁለቱንም መንግሥታት ቀጣቸው። ኃያልና ጨካኝ የሆነው የአሦር ንጉሠ ነገሥት ግዛት የእስራኤልን መንግሥት ደመሰሰው፣ ብዙ የእስራኤል መንግስት ሕዝብንም አዘርያውያን ገደሉ። ንብረቶቻቸውንም ሁሉ ወሰዱ፣ ከአገሪቱ አብዛኛውንም አቃጠሉ።

አሦርያውያንም መሪዎችን፣ ሀብታሞችን፣ እንዲሁም ሙያ የነበራቸውን ሰዎች ሁሉ ሰበሰቡና ወደ አሦር ወሰዱአቸው፡፡ ያልተገደሉት በጣም ድሆች የነበሩት እስራኤላውያን ብቻ በእስራኤል መንግሥት ቀሩ፡፡

ከዚያም አሦራውያን የእስራኤል መንግሥት በነበረባት ምድር እንዲኖሩ ባዕዳንን አመጡ፡፡ ባዕዳኑም የፈረሱትን ከተሞች እንደገና ሠሩና በዚያ ቀርተው የነበሩትን እስራኤላውያን አገቡ፡፡ ባዕዳንን ያገቡት የእስራኤላውያን ዝርያዎች ሳምራውያን ተብለው ይጠሩ ነበር፡፡

የእስራኤል መንግሥት ሕዝብ እግዚአብሔርን ስላላመኑበትና ስላልታዘዙት እንዴት እንደ ቀጣቸው በይሁዳ መንግሥት የነበሩት ሕዝብ ዐዩ። እንደዚያም ሆኖ ግን የይሁዳ መንግሥት ሕዝብ የከነዓናውያንን አማልክት ጨምሮ ጣዖታትን አመለኩ። እግዚአብሔርም እንዲያስጠነቅቁአቸው ነቢያትን ላከ፣ እነርሱ ግን አንሰማም አሉ።

አሦራውያን የእስራኤልን መንግሥት ካጠፉ ከ100 ዓመታት ገደማ በኋላ የይሁዳን መንግሥት እንዲወጉ እግዚአብሔር የባቢሎናውያንን ንጉሥ ናቡከደናፆርን ላከ፡፡ ባቢሎን ኃያል የንጉሠ ነገሥት ግዛት ነበረች፡፡ የይሁዳ ንጉሥም የናቡከደነፆር አገልጋይ ለመሆንና በያመቱ ብዙ ገንዘብ ሊከፍለው ተስማሙ፡፡

ነገር ግን ከጥቂት ዓመታት በኋላ የይሁዳ ንጉሥ በባቢሎን ላይ ዓመፀ፡፡ ስለዚህ ባቢሎናውያን ተመልሰው መጥተው የይሁዳን መንግሥት ወጉ፡፡ የኢየሩሳሌምን ከተማ ያዙ፣ ቤተ መቅደሱን አጠፉ፣ እንዲሁም የከተማይቱንና የቤተ መቅደሱን ንብረት ሁሉ ወሰዱ፡፡

የይሁዳ ንጉሥ ስላመፀበት ሊቀጡ የናቡከደነፆር ወታደሮች የይሁዳን ንጉሥ ወንድ ልጆች በፊቱ ገደሉ፤ እርሱንም ዓይኖቹን አሳወሩ፡፡ ከዚያ በኋላ በባቢሎን በእስር ቤት እንዲሞት ንጉሡን ወሰዱት፡፡

ናቡከደነፆርና ሠራዊቱ በእርሻ እንዲሠሩ እጅግ በጣም ድሆች የሆኑትን ሰዎች ብቻ በመተው ከሞላ ጐደል የይሁዳን መንግሥት ሕዝብ ሁሉ ወደ ባቢሎን ማርከው ወሰዱ፡፡ የእግዚአብሔር ሕዝብ የተስፋዪቱን ምድር እንዲለቁ የተገደዱበት ይህ ወቅት የባቢሎን ምርኮ ተብሎ ይጠራል፡፡

ምንም እንኳ እግዚአብሔር ወደ ምርኮ በመውሰድ ሕዝቡን ስለ ኃጢአታቸው ቢቀጣቸውም እነርሱንና ተስፋዎቹን አልረሳም። እግዚአብሔር ሕዝቡን መጠበቁንና በነቢያቱ በኩል እነርሱን ማነጋገሩን ቀጠለ። ከሰባ ዓመት በኋላ፣ ወደ ተስፋዪቱ ምድር እንደ ገና እንዲመለሱ ተስፋ ሰጠ።

ከሰባ ዓመታት ገደማ በኋላ፣ የፋርስ ንጉሥ ቂሮስ ባቢሎንን አሸነፈ፣ ስለዚህ የፋርስ ንጉሠ ነገሥት ግዛት የባቢሎንን ንጉሠ ነገሥት ግዛት ተካ፡፡ በዚያን ጊዜ እስራኤላውያን አይሁዶች ተብለው ይጠሩ ነበር። አብዛኞቻቸውም ሕይወታቸውን በሙሉ በባቢሎን የኖሩ ነበሩ፡፡ በጣም ያረጁ ጥቂት አይሁዶች ብቻ የይሁዳን ምድር አስታወሱ፡፡

የፋርስ ንጉሠ ነገሥት ኃይለኛ ቢሆንም ለማረካቸው ሕዝብ መሐሪ ነበር፡፡ ቂሮስ የፋርሳውያን ንጉሥ ከሆነ ከጥቂት ጊዜ በኋላ፣ ወደ ይሁዳ መመለስ የፈለገ ማንኛውም አይሁዳዊ ፋርስን ለቆ ወደ ይሁዳ መመለስ እንደሚችል ትእዛዝ ሰጠ፡፡ ቤተ መቅደሱን እንደገና እንዲሠሩም የገንዘብ ድጋፍ ሳይቀር አደረገላቸው! ስለዚህ በምርኮ ከቆዩባቸው ሰባ ዓመታት በኋላ፣ ጥቂት የአይሁዶች ቡድን በይሁዳ ወዳለችው ኢየሩሳሌም ከተማ ተመለሱ፡፡

ሕዝቡ ወደ ኢየሩሳሌም በደረሱ ጊዜ፣ ቤተ መቅደሱንና በከተማዪቱ ዙሪያ ያለውን ቅጥር እንደገና ሠሩ። ምንም እንኳ እስካሁን ድረስ በሌሎች ሕዝቦች የተገዙ ቢሆኑም፣ ዳግመኛ በተስፋዪቱ ምድር ኖሩና በቤተ መቅደሱ እግዚአብሔርን አመለኩ።
የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከ2ኛ ነገሥት 17፤ 24-25፤ 2ኛ ዜና 36፤ ዕዝራ 1-10፤ ነህምያ 1-13፡፡