13. እግዚአብሔር ከእስራኤል ጋር ያደረገው ቃል ኪዳን

እግዚአብሔር እስራኤላውያንን በቀይ ባሕር ውስጥ ካሳለፋቸው በኋላ በምድረ በዳ ውስጥ ሲና ተብሎ ወደሚጠራ ተራራ ወሰዳቸው። ይህም ሙሴ የሚቃጠለውን ቊጥቋጦ ያየበት ተራራ ነው። ሕዝቡ በተራራው ሥር ድንኳኖቻቸውን ተከሉ።

እግዚአብሔርም፣ ‹‹ለእኔ ብትታዘዙና ቃል ኪዳኔን ብትጠብቁ፣ የከበረ ርስት፣ የካህናት መንግስት፣ እንዲሁም ቅዱስ ሕዝብ ትሆኑኛላችሁ›› ብሎ ለሙሴና ለእስራኤል ሕዝብ ተናገረ።

ሕዝቡ በመንፈሳዊነት ራሳቸውን ካዘጋጁ ከሦስት ቀን በኋላ፣ እግዚአብሔር በነጐድጓድ፣ በመብረቅ፣ በጢስ እንዲሁም ከፍ ባለ የመለከት ድምፅ በሲና ተራራ ላይ ወረደ። ወደ ተራራው እንዲወጣ የተፈቀደለት ሙሴ ብቻ ነበር።

ከዚያም እግዚአብሔር ቃል ኪዳን ገባላቸውና እንዲህ አለ፣ ‹‹እኔ ከግብፅ ባርነት ያዳንኳችሁ፣ አምላካችሁ፣ ያህዌ ነኝ። ሌሎችን አማልክት አታምልኩ።››

‹‹ጣዖታትን አትሥሩ አታምልኳቸውም፣ ምክንያቱም እኔ፣ ያህዌ ቀናተኛ አምላከ ነኝ። ስሜንም በከንቱ አትጥሩ፣ የሰንበትን ቀን ትቀድሰው ዘንድ ዐስብ። ይኸውም ሥራህን ሁሉ በስድስት ቀን ሥራ፣ ሰባተኛው ቀን ግን የምታርፍበትና እኔን የምታስታውስበት ዕለት ነው።››

‹‹አባትህንና እናትህን አክብር። አትግደል። አታመንዝር። አትስረቅ። አትዋሽ። የባልንጀራህን ሚስት፣ ቤቱን፣ ወይም የእርሱ የሆነውን ማንኛውም ነገር አትመኝ።››

ከዚያም እግዚአብሔር እነዚህን ዐሥር ትእዛዛት በሁለት ጠፍጣፋ ድንጋዮች ላይ ጽፎ ለሙሴ ሰጠው። ደግሞ እግዚአብሔር የሚከተሉአቸውን ሌሎች ብዙ ሕግጋትንና ደንቦችን ሰጣቸው። ሕዝቡ እነዚህን ሕግጋት ከታዘዙ እግዚአብሔር እንደሚባርካቸውና እንደሚጠብቃቸው ተስፋ ሰጣቸው። ሕግጋቱን ካልታዘዙ ግን እግዚአብሔር ይቀጣቸዋል።

ደግሞም እግዚአብሔር ለእስራኤላውያን እንዲሠሩለት ስለሚፈልገው ድንኳን ዝርዝር መግለጫ ሰጣቸው። እርሱ የመገናኛው ድንኳ ተብሎ ይጠራ ነበር፣ በትልቅ መጋረጃ የተከፈሉ ሁለት ክፍሎችም ነበሩት። እግዚአብሔር በዚያ ይኖር ስለ ነበረ፣ ከመጋረጃ በስተጀርባ ወዳለው ክፍል እንዲገባ የተፈቀደለት ሊቀ ካህን ብቻ ነበር።

የእግዚአብሔርን ሕግ ያልታዘዘ ማንኛውም ሰው በመገናኛው ድንኳ ፊት ለፊት ወዳለው መሠዊያ ለእግዚአብሔር መሥዋዕት የሚሆን እንስሳ ያመጣ ነበር። ካህኑ እንስሳውን ያርድና በመሠዊያው ላይ ያቃጥለው ነበር። የተሠዋው እንስሳ ደም የሰውዬውን ኃጢአት ይሸፍንና ሰውዬውን በእግዚአብሔር ፊት ያነጻው ነበር። እግዚአብሔር ካህናቱ ይሆኑ ዘንድ የሙሴን ወንድም አሮንንና፣የአሮንን ዝርያዎች መረጠ።

ሕዝቡ ሁላቸውም እግዚአብሔር የሰጣቸውን ትእዛዛት ለመፈጸም፣ እግዚአብሔርን ብቻ ለማምለክ፣ እንዲሁም የተለዩ ሕዝቡ ለመሆን ተስማሙ። ነገር ግን ለእግዚአብሔር ለመታዘዝ ቃል ከገቡ ከጥቂት ጊዜ በኋላ ክፉኛ ኃጢአት ሠሩ።

ሙሴ ለብዙ ቀናት በሲና ተራራ ጫፍ ላይ ሆኖ ከእግዚአብሔር ጋር ይነጋገር ነበር። ሕዝቡ እርሱ እስኪመለስ ድረስ መጠበቅ ሰለቻቸው። ስለዚህ ወደ አሮን ወርቅ አመጡና ጣዖት እንዲሠራላቸው ጠየቁት!

አሮንም በጥጃ ቅርፅ የወርቅ ጣዖት ሠራ። ሕዝቡም ልቅ በሆነ ሁኔታ ጣዖቱን ማምለክ ጀመሩ፣ መሥዋዕትም ሠዉለት! በኃጢአታቸው ምክንያት እግዚአብሔር በጣም ተቈጣቸው፣ ሊያጠፋቸውም ፈለገ። ነገር ግን ሙሴ ጸለየላቸው፣ እግዚአብሔርም ጸሎቱን ሰማና አላጠፋቸውም።

ሙሴ ከተራራው ወርዶ ጣዖቱን ስያምልኩ ባየ ጊዜ በጣም ተቈጥቶ እግዚአብሔር ዐሥሩን ትእዛዛት የጻፈባቸውን ድንጋዮች ሰባበረ።

ከዚያም ሙሴ ጣዖቱን ፈጨው፣ በውሃውም ላይ በተነው፣ ለሕዝቡም አጠጣቸው። እግዚአብሔር በሕዝቡ ላይ መቅሠፍት ላከና ብዙዎቻቸው ሞቱ።

ሙሴ እንደ ገና ተራራው ላይ ወጣና እግዚአብሔር ሕዝቡን ይቅር እንዲላቸው ጸለየ። እግዚአብሔር ሙሴን ሰማውና ይቅር አላቸው። ሙሴ የሰባበራቸውን ለመተካት በዐዲስ ጠፍጣፋ ድንጋዮች ላይ የተጻፉትን ዐሥሩን ትእዛዛት ይዞ ከተራራ ወረደ። ከዚያ በኋላ እግዚአብሔር እስራኤላውያንን ከሲና ተራራ ወደ ተስፋዪቱ ምድር መራቸው።
የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከዘጸአት 19-34፡፡