23. የኢየሱስ ልደት

ማርያም ዮሴፍ ለተባለ ጻድቅ ሰው ታጭታ ነበር። እጮኛዋ ዮሴፍ ማርያም መፀነስዋን በሰማ ጊዜ፣ ሕፃኑ የእርሱ እንዳልሆነ ዐወቀ። ስለዚህ ማርያምን ለማሳፈር ስላልፈለገ፣ዝም ብሎ ሊተዋት ዐሰበ። ያንን ከማድረጉ በፊት የእግዚአብሔር መልአክ መጣና በሕልም ተናገረው።

መልአኩ እንዲህ አለ፡- “ዮሴፍ፣ እጮኛህን ማርያምን ሚስትህ አድርገህ ለመውሰድ አትፍራ። በውስጥዋ ያለው ሕፃን ከመንፈስ ቅዱስ ነው። ወንድ ልጅ ትወልዳለች። ስሙን ኢየሱስ ብለህ ጥራው (ትርጕሙም፣ ያሕዌ ያድናል ማለት ነው)፣ ምክንያቱም ሕዝቡን ከኃጢአታቸው ያድናቸዋልና።”

ስለዚህ ዮሴፍ ማርያምን ወሰዳት፣ ነገር ግን እስክትወልድ ድረስ ከእርስዋ ጋር አልተኛም፡፡

ማርያም የምትወልድበት ጊዜ እንደ ደረሰ፣ የሮማ መንግሥት ሁሉም ሰው ለቈጠራ ቅድመ አያቶቹ ወደ ኖሩበት ከተማ እንዲሄድ ተናገረ። ዮሴፍና ማርያም ከሚኖሩበት ከናዝሬት ወደ ቤትልሔም ረጅም ጕዞ ተጓዙ፤ ምክንያቱም የቅድመ አያቶቻቸው የዳዊት ከተማ ቤትልሔም ነበር።

ወደ ቤትልሔም በደረሱ ጊዜ ማረፊያ ስፍራ አልነበራቸውም። ሊያገኙ የቻሉት ብቸኛ ክፍል እንስሶች የሚያድሩበት ስፍራ ነበረ። ሕፃኑ በተወለደ ጊዜ የሚያስተኙበት አልጋ ስላልነበረ እናቱ በከብቶች መመገቢያ ገንዳ አስተኛችው። ስሙንም ኢየሱስ አሉት።

በዚያ ሌሊት በአቅራቢያው ባለ ሜዳ ላይ መንጎቻቸውን የሚጠብቁ ጥቂት እረኞች ነበሩ። በድንገት የሚያበራ መልአክ ታያቸው፣ እነርሱም ፈሩ። መልአኩ፣ ‹‹አትፍሩ፣ ምክንያቱም ለእናንተ የምነግራችሁ የምሥራች አለኝ። መሲሑ ጌታ በቤተልሔም ተወልዶአል!››።

“ሄዳችሁ ሕፃኑን ፈልጉ፣ በጨርቅ ተጠቅልሎና በእንስሶች መመገቢያ ገንዳ ተኝቶ ታገኙታላችሁ።” አለ። ድንገትም ሰማያት ‹‹ክብር ለእግዚአብሔር በሰማይ ይሁን! ሰላምም እግዚአብሔር ለሚወደው ሕዝብ በምድር ላይ ይሁን!›› እያሉ እግዚአብሔርን በሚያመሰግኑ መላእክት ተሞሉ።

እረኞች ኢየሱስ ወደ ነበረበት ስፍራ ፈጥነው ደረሱና ልክ መልአኩ እንደ ነገራቸው በእንስሶች መመገቢያ ገንዳ ተኝቶ አገኙት፡፡ በጣም ደስ አላቸው፡፡ እረኞቹ ስለ ሰሙትና ስላዩት ሁሉ እግዚአብሔርን እያመሰገኑ፣ በጎቻቸው ወደ ነበሩባቸው ሜዳዎች ተመለሱ፡፡
ከጥቂት ጊዜ በኋላ ከሩቅ ምሥራቅ አገሮች የሆኑ ጠቢባን በሰማይ አንድ ያልተለመደ ኮከብ ዐዩ፡፡ ዐዲስ የአይሁድ ንጉሥ የተወለደ መሆኑን እንደሚያመለክትም ተገነዘቡ፡፡ ስለዚህ ይህንን ንጉሥ ለማየት በጣም ረጅም ርቀት ተጓዙ፡፡ ወደ ቤተ ልሔም መጡና ኢየሱስና ወላጆቹ የነበሩበትን ቤት አገኙት፡፡

ጠቢባኑ ኢየሱስን ከእናቱ ጋር ባዩት ጊዜ ወድቀው ሰገዱለት፡፡ ለኢየሱስም ውድ ስጦታዎች ሰጡት፡፡ ከዚያም ወደ አገራቸው ተመለሱ፡፡
የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከማቴዎስ 1፤ ሉቃስ 2፡፡