አማርኛ: Open Bible Stories

Updated ? hours ago # views See on DCS

23. የኢየሱስ ልደት

Image

ማርያም ዮሴፍ ለተባለ ጻድቅ ሰው ታጭታ ነበር። እጮኛዋ ዮሴፍ ማርያም መፀነስዋን በሰማ ጊዜ፣ ሕፃኑ የእርሱ እንዳልሆነ ዐወቀ። ስለዚህ ማርያምን ለማሳፈር ስላልፈለገ፣ዝም ብሎ ሊተዋት ዐሰበ። ያንን ከማድረጉ በፊት የእግዚአብሔር መልአክ መጣና በሕልም ተናገረው።

Image

መልአኩ እንዲህ አለ፡- “ዮሴፍ፣ እጮኛህን ማርያምን ሚስትህ አድርገህ ለመውሰድ አትፍራ። በውስጥዋ ያለው ሕፃን ከመንፈስ ቅዱስ ነው። ወንድ ልጅ ትወልዳለች። ስሙን ኢየሱስ ብለህ ጥራው (ትርጕሙም፣ ያሕዌ ያድናል ማለት ነው)፣ ምክንያቱም ሕዝቡን ከኃጢአታቸው ያድናቸዋልና።”

Image

ስለዚህ ዮሴፍ ማርያምን ወሰዳት፣ ነገር ግን እስክትወልድ ድረስ ከእርስዋ ጋር አልተኛም፡፡

Image

ማርያም የምትወልድበት ጊዜ እንደ ደረሰ፣ የሮማ መንግሥት ሁሉም ሰው ለቈጠራ ቅድመ አያቶቹ ወደ ኖሩበት ከተማ እንዲሄድ ተናገረ። ዮሴፍና ማርያም ከሚኖሩበት ከናዝሬት ወደ ቤትልሔም ረጅም ጕዞ ተጓዙ፤ ምክንያቱም የቅድመ አያቶቻቸው የዳዊት ከተማ ቤትልሔም ነበር።

Image

ወደ ቤትልሔም በደረሱ ጊዜ ማረፊያ ስፍራ አልነበራቸውም። ሊያገኙ የቻሉት ብቸኛ ክፍል እንስሶች የሚያድሩበት ስፍራ ነበረ። ሕፃኑ በተወለደ ጊዜ የሚያስተኙበት አልጋ ስላልነበረ እናቱ በከብቶች መመገቢያ ገንዳ አስተኛችው። ስሙንም ኢየሱስ አሉት።

Image

በዚያ ሌሊት በአቅራቢያው ባለ ሜዳ ላይ መንጎቻቸውን የሚጠብቁ ጥቂት እረኞች ነበሩ። በድንገት የሚያበራ መልአክ ታያቸው፣ እነርሱም ፈሩ። መልአኩ፣ ‹‹አትፍሩ፣ ምክንያቱም ለእናንተ የምነግራችሁ የምሥራች አለኝ። መሲሑ ጌታ በቤተልሔም ተወልዶአል!››።

Image

“ሄዳችሁ ሕፃኑን ፈልጉ፣ በጨርቅ ተጠቅልሎና በእንስሶች መመገቢያ ገንዳ ተኝቶ ታገኙታላችሁ።” አለ። ድንገትም ሰማያት ‹‹ክብር ለእግዚአብሔር በሰማይ ይሁን! ሰላምም እግዚአብሔር ለሚወደው ሕዝብ በምድር ላይ ይሁን!›› እያሉ እግዚአብሔርን በሚያመሰግኑ መላእክት ተሞሉ።

Image

እረኞች ኢየሱስ ወደ ነበረበት ስፍራ ፈጥነው ደረሱና ልክ መልአኩ እንደ ነገራቸው በእንስሶች መመገቢያ ገንዳ ተኝቶ አገኙት፡፡ በጣም ደስ አላቸው፡፡ እረኞቹ ስለ ሰሙትና ስላዩት ሁሉ እግዚአብሔርን እያመሰገኑ፣ በጎቻቸው ወደ ነበሩባቸው ሜዳዎች ተመለሱ፡፡Image

ከጥቂት ጊዜ በኋላ ከሩቅ ምሥራቅ አገሮች የሆኑ ጠቢባን በሰማይ አንድ ያልተለመደ ኮከብ ዐዩ፡፡ ዐዲስ የአይሁድ ንጉሥ የተወለደ መሆኑን እንደሚያመለክትም ተገነዘቡ፡፡ ስለዚህ ይህንን ንጉሥ ለማየት በጣም ረጅም ርቀት ተጓዙ፡፡ ወደ ቤተ ልሔም መጡና ኢየሱስና ወላጆቹ የነበሩበትን ቤት አገኙት፡፡

Image

ጠቢባኑ ኢየሱስን ከእናቱ ጋር ባዩት ጊዜ ወድቀው ሰገዱለት፡፡ ለኢየሱስም ውድ ስጦታዎች ሰጡት፡፡ ከዚያም ወደ አገራቸው ተመለሱ፡፡

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከማቴዎስ 1፤ ሉቃስ 2፡፡