39. ኢየሱስ ለፍርድ ቀረበ

አሁን ጊዜው እኩለ ሌሊት ነው። ሊቀ ካህናቱ የምርመራ ጥያቄ ይጠይቀው ዘንድ ወታደሮቹ ኢየሱስን ወደ ሊቀ ካህናቱ ቤት ወሰዱት። ጴጥሮስ ራቅ ብሎ ከኋላ ተከተላቸው። ኢየሱስን ወደ ቤቱ ባስገቡት ጊዜ፣ ጴጥሮስ በውጪ ሆኖ እሳት ይሞቅ ነበር።

በቤቱ ውስጥ የአይሁድ መሪዎች ኢየሱስን ለምርመራ አቀረቡት። በእርሱ ላይ የዋሹ ብዙ የሐሰት ምስክሮችን አመጡ። ይሁን እንጂ፣ ቃላቸው እርስ በርሱ አልተስማማም፣ ስለዚህ የአይሁድ መሪዎች ኢየሱስ በማንኛውም ነገር ወንጀለኛ መሆኑን ማረጋገጥ አልቻሉም።

በመጨረሻ፣ ሊቀ ካህናቱ ኢየሱስን ትኵር ብሎ ተመለከተውና፣ ‹‹ንገረን፣ አንተ መሲሑ፣ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ነህን?›› አለው።

ኢየሱስም፣ ‹‹አዎን ነኝ፣ ከእግዚአብሔር ጋር ተቀምጬ ሳለሁና ከሰማይም ስመጣ ታያለህ›› አለው። ሊቀ ካህናቱ በቊጣ ልብሱን ቀደደና ለሌሎቹ የሃይማኖት መሪዎች፣ ‹‹ምንም ዓይነት ምስክሮች አያስፈልጉንም! የእግዚአብሔር ልጅ ነኝ ሲል ራሳችሁ ሰምታችሁታል። ፍርዳችሁ ምንድን ነው?›› ብሎ ጮኸ።

ሁሉም የአይሁድ መሪዎች፣ ‹‹ሞት ይገባዋል!›› ብለው ለሊቀ ካህናቱ መለሱለት። ከዚያም ኢየሱስን ፊቱን ሸፈኑት፣ ተፉበት፣ መቱት፣ ዘበቱበትም።

ጴጥሮስ ከቤቱ ውጪ በመጠበቅ ላይ እያለ የቤት ሠራተኛ የሆነች ልጅ ዐየችውና፣ ‹‹አንተም ደግሞ ከኢየሱስ ጋር ነበርክ!›› አለችው፡፡ ጴጥሮስ እርስዋ የተናገረችውን ካደ፡፡ ከዚያ በኋላ ሌላዋ የቤት ሠራተኛ ያንኑ ተናገረች፣ ጴጥሮስም እንደገና ካደ፡፡ በመጨረሻ ሕዝቡ ‹‹ሁለታችሁም ከገሊላ ስለሆናችሁ አንተ ከኢየሱስ ጋር መሆንህን እናውቃለን›› አሉ፡፡

ከዚያም ጴጥሮስ፣ ‹‹ይህንን ሰው እኔ አላውቀውም!›› ብሎ ማለ። ወዲያውኑ ዶሮ ጮኸ፣ ኢየሱስም ዘወር አለና ጴጥሮስን ተመለከተው።

ጴጥሮስ ከዚያ ሄደና በምሬት አለቀሰ። ይህ በእንዲህ እንዳለ፣ ኢየሱስን አሳልፎ የሰጠው ይሁዳ፣ የአይሁድ መሪዎች እንዲሞት በኢየሱስ ላይ እንደ ፈረዱበት ዐየ። ይሁዳ በሐዘን ተሞልቶ ሄደና ራሱን ገደለ።

በነጋታው ማለዳ ላይ የአይሁድ መሪዎች ኢየሱስን ወደ ሮማው ገዥ ወደ ጲላጦስ አመጡት። ጲላጦስ ኢየሱስን ወንጀለኛ ነህ ብሎ ይፈርድበትና በሞት እንዲቀጣ ያደርጋል ብለው ተስፋ አድርገው ነበር። ጲላጦስ ኢየሱስን፣ ‹‹የአይሁድ ንጉሥ ነህን?›› ብሎ ጠየቀው።

ኢየሱስ እንዲህ ብሎ መለሰለት፣ ‹‹አንተም ብለሃል፣ ነገር ግን መንግሥቴ ምድራዊ መንግሥት አይደለችም። እንደዚያ ቢሆን ኖሮ፣ አገልጋዮቼ ይዋጉልኝ ነበር። እኔ ስለ እግዚአብሔር እውነትን ለመናገር ወደ ምድር መጥቼአለሁ። እውነትን የሚወድ ሁሉ እኔን ይሰማኛል።›› ጲላጦስ፣ ‹‹እውነት ምንድን ነው?›› አለ።

ጲላጦስ ከኢየሱስ ጋር ከተናገረ በኋላ ወደ ሕዝቡ ወጣና፣ ‹‹በዚህ ሰው ላይ ምንም ወንጀል አላገኘሁበትም›› አለ። የአይሁድ መሪዎችና ሕዝቡ ግን፣ ‹‹ስቀለው!›› ብለው ጮኹ። ጲላጦስ፣ ‹‹ወንጀለኛ አይደለም›› ብሎ መለሰላቸው። እነርሱ ግን የበለጠ ጮኹ። ከዚያም ጲላጦስ ለሦስተኛ ጊዜ፣ ‹‹ወንጀለኛ አይደለም!›› አለ።

ጲላጦስ ሕዝቡ ረበሻ ያስነሣል ብሎ ፈራ፣ ስለዚህ ኢየሱስን እንዲሰቅሉት ወታደሮቹን አዘዘ። የሮማ ወታደሮችም ኢየሱስን ገረፉትና ቀይ የነገሥታት ልብስ አለበሱት፣ እንዲሁም የሾኽ አክሊል በራሱ ላይ አደረጉ። ከዚያም፣ ‹‹እነሆ፣ የአይሁድ ንጉሥ!›› እያሉ ዘበቱበት።
የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከማቴዎስ 26፡57-27፡26፤ ማርቆስ 14፡53-15፡15፤ ሉቃስ 22፡54-23፡25፤ ዮሐንስ 18፡12-19፡16።