14. በምድረ በዳ መቅበዝበዝ

እግዚአብሔር ከእነርሱ ጋር ያደረገው ቃል ኪዳን ክፍል ለሆኑት ሕግጋት እንዲታዘዙ ለእስራኤላውያን ከነገራቸው በኋላ የሲና ተራራን ለቀው ሄዱ። እግዚአብሔርም ሕዝቡን ከሲና ተራራ ከነዓን ተብላ ትጠራ ወደ ነበረችው ወደ ተስፋዪቱ ምድር ይመራቸው ጀመር። የደመናው ዓምድ ከፊት ለፊታቸው ወደ ከነዓን ሄደ፣ እነርሱም ተከተሉት።

እግዚአብሔር የተስፋዪቱን ምድር ለዘሮቻቸው እንደሚሰጣቸው ለአብርሃም፣ ለይስሐቅና ለያዕቆብ ተስፋ ሰጥቶአቸው ነበር፣ ነገር ግን በዚያች ምድር ብዙ የሕዝብ ወገኖች ይኖሩ ነበር። እነርሱም ከነዓናውያን ተብለው ይጠሩ ነበር። ከነዓናውያን እግዚአብሔርን አያመልኩትም ወይም አይታዘዙትም ነበር።ነገር ግን ሐሰተኞች አማልክትን ያመልኩ ነበር፤ ብዙ ክፉ ነገሮችንም ያደርጉ ነበር።

እግዚአብሔር ለእስራኤላውያን እንዲህ ብሎ ነገራቸው፣ ‹‹በተስፋዪቱ ምድር ያሉትን ከነዓናውያንን ሁሉ አጥፉአቸው። ከእነርሱ ጋር ሰላምን አታድርጉ፤ አታግቡአቸውም። ጣዖቶቻቸውን ሁሉ ፈጽማችሁ አጥፉአቸው። ለእኔ ባትታዘዙ፣ በእኔ ፈንታ የእነርሱን ጣዖታት ታመልካላችሁ።››

እስራኤላውያን ወደ ከነዓን ድንበር በደረሱ ጊዜ፣ ሙሴ ከእያንዳንዱ የእስራኤል ነገድ አንድ አንድ ሰው፣ ዐሥራ ሁለት ሰዎችን መረጠ። ሄደው ምድሪቱ ምን እንደምትመስል እንዲሰልሉ መመሪያ ሰጣቸው።ደግሞም ከነዓናውያን ብርቱዎች ወይም ደካሞች መሆናቸውን ለማየት ከነዓናውያንን መሰለል ነበረባቸው።

ዐሥራ ሁለቱ ሰዎች በከነዓን ውስጥ ለአርባ ቀን ተጓዙና ተመልሰው መጡ።መጥተውም ‹‹ምድሪቱ በጣም ለም ነች፤ ሰብሉም የተትረፈረፈ ነው!›› ብለው ለሕዝቡ ነገሩአቸው። ከስችላዮቹ ዐሥሩ ግን፣ ‹‹ከተሞቹ በጣም ብርቱዎች፤ ሰዎቹም ግዙፍ ናቸው! እነርሱን ብንወጋቸው በእርግጥ ያሸንፉናል፤ ይገድሉናልም!›› አሉ።

ወዲያውኑ ሌሎቹ ሁለት ሰላዮች፣ ካሌብና ኢያሱ፣ ‹‹የከነዓን ሰዎች ረጃጅሞችና ብርቱዎች መሆናቸው እውነት ነው፣ ነገር ግን እኛ በእርግጥ እናሸንፋቸዋለን! እግዚአብሔር ስለ እኛ ይዋጋል!›› አሉ።፡

ሕዝቡ ግን ካሌብንና ኢያሱን አልሰሙአቸውም። ሙሴንና አሮንን ተቈጡአቸውና፣ ‹‹ወደዚህ አስከፊ ቦታ ለምን አመጣችሁን? እኛ በጦርነት ከምንሞትና ሚስቶቻችንና ልጆቻችን ባሮች ከሚሆኑ ይልቅ በግብፅ ብንኖር ይሻለን ነበር›› አሉ። ሕዝቡ ወደ ግብፅ መልሶ የሚወስዳቸውን ሌላ መሪ ለመምረጥ ፈለጉ።

እግዚአብሔር በጣም ተቈጣና ወደ መገናኛው ድንኳ መጣ። እንዲህም አለ፣ ‹‹እናንተ በእኔ ላይ ስላመፃችሁ፣ ሕዝቡ ሁሉ በምድረ በዳ ይቅበዘበዛሉ። ከኢያሱና ከካሌብ በቀር ሃያ ዓመትና ከዚያ በላይ የሆናቸው ሁሉ በዚያ ይሞታሉ እንጂ ከቶ ወደ ተስፋዪቱ ምድር አይገቡም›› አላቸው።

ሕዝቡ ይህን በሰሙ ጊዜ፣ ኃጢአት በመሥራታቸው ዐዘኑ። የጦር መሣሪያዎቻቸውን ይዘው የከነዓንን ሰዎች ለመውጋት ሄዱ። ሙሴ ግን እግዚአብሔር ከእነርሱ ጋር ስላልነበረ እንዳይሄዱ አስጠነቀቃቸው፣ ነገር ግን እርሱን አልሰሙትም።

እግዚአብሔር አብሮአቸው ወደ ጦርነቱ አልሄደም፣ ስለዚህ ተሸነፉ፤ ብዙዎቻቸውም ተገደሉ። ከዚያም እስራኤላውያን ከከነዓን ተመለሱና በምድረ በዳ ለአርባ ዓመት ተቅበዘበዙ።

የእስራኤል ሕዝብ በምድረ በዳ በተቅበዘበዙባቸው አርባ ዓመታት እግዚአብሔር የሚያስፈልጋቸውን ሰጣቸው። ከሰማይ ‹‹መና›› ተብሎ የሚጠራ ምግብ ሰጣቸው። ደግሞም ሥጋ ይበሉ ዘንድ ወደ ሰፈራቸው ድርጭቶችን ላከላቸው። በዚያን ጊዜ ሁሉ እግዚአብሔር ልብሳቸውና ጫማቸው እንዳያልቅ አደረገ።

እግዚአብሔር ተአምራዊ በሆነ መንገድ ውሃ እንኳ ከአለት ሰጣቸው። ይህም ሁሉ ሆኖ ግን የእስራኤል ሕዝብ በእግዚአብሔርና በሙሴ ላይ አማረሩ፤ አጕረመረሙም። ቢሆንም፣ እግዚአብሔር ለአብርሃም፣ ለይስሐቅና ለያዕቆብ ለሰጠው ተስፋ አሁንም ታማኝ ነበር።

ሕዝቡ ምንም ውሃ ባልነበራቸው በሌላ ጊዜ እግዚአብሔር ለሙሴ፣ ‹‹አለቱን ተናገረው፣ ከእርሱም ውሃ ይወጣል›› አለው። ነገር ግን ሙሴ ለአለቱ በመናገር ፈንታ በበትር ሁለት ጊዜ ስለ መታው በሕዝቡ ሁሉ ፊት እግዚአብሔርን አላከበረም። ሁለም ሰው እንዲጠጣ ከአለቱ ውሃ ወጣ፣ ነገር ግን እግዚአብሔር በሙሴ ላይ ተቈጣና፣ ‹‹ወደ ተስፋዪቱ ምድር አትገባም›› አለው።

እስራኤላውያን ለአርባ ዓመት በምድረ በዳ ከተቅበዘበዙ በኋላ በእግዚአብሔር ላይ ያመፁት ሁሉ ሞቱ። ከዚያም እግዚአብሔር ሕዝቡን እንደ ገና ወደ ተስፋዪቱ ምድር ዳርቻ መራቸው። አሁን ሙሴ በጣም አርጅቶ ነበር፣ ስለዚህ ሕዝቡን በመምራት እንዲያግዘው እግዚአብሔር ኢያሱን መረጠ። ደግሞም እግዚአብሔር አንድ ቀን እንደ ሙሴ ያለ ሌላ ነቢይ እንደሚልክ ለሙሴ ተስፋ ሰጠው።

ከዚያም እግዚአብሔር የተስፋዪቱን ምድር ለማየት ይችል ዘንድ ወደ ተራራ ራስ ላይ እንዲወጣ ለሙሴ ነገረው። ሙሴ የተስፋዪቱን ምድር ዐየ፣ ነገር ግን እግዚአብሔር ወደ እርስዋ እንዲገባ አልፈቀደለትም። ከዚያም ሙሴ ሞተ፣ እስራኤላውያንም ለሠላሳ ቀናት አለቀሱለት። ኢያሱም ዐዲሱ መሪአቸው ሆነ። ኢያሱ በእግዚአብሔር ያመነና ለእግዚአብሔር የሚታዘዝ ስለ ነበር ጥሩ መሪ ነበር።
የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከዘጸአት 16-17፤ ዘኍልቁ 10-14፤ 20፤ 27፤ ዘዳግም 34፡፡