15. የተስፋይቱ ምድር

በመጨረሻ እስራኤላውያን ወደ ተስፋዪቱ ምድር፣ ወደ ከነዓን የሚገቡበት ጊዜ ደረሰ። ኢያሱ በብርቱ ግንብ ተጠብቃ ወደ ነበረችው የከነዓናውያን ከተማ ወደ ኢያሪኮ ሁለት ሰላዮችን ላከ። በዚያች ከተማ ሰላዮቹን የሸሸገችና ኋላ ላይ እንዲያመልጡ የረዳቻቸው ረዓብ የተባለች ጋለሞታ ትኖር ነበር። እርስዋ ይህን ያደረገችው በእግዚአብሔር ስላመነች ነው። ሰላዮቹ፤ እስራኤላውያን ኢያሪኮን በሚያጠፉበት ጊዜ ረዓብንና ቤተ ሰብዋን እንደሚያድኑአቸው ቃል ገቡላት።

እስራኤላውያን ወደ ተስፋዪቱ ምድር ለመግባት የዮርዳኖስን ወንዝ መሻገር ነበረባቸው። እግዚአብሔር፣ ‹‹መጀመሪያ ካህናቱ እንዲሻገሩ አድርግ›› ብሎ ለኢያሱ ነገረው። ካህናቱ ወደ ዮርዳኖስ ወንዝ መግባት በጀመሩ ጊዜ፣ እስራኤላውያን በደረቅ መሬት መሻገር ይችሉ ዘንድ ከላይ በኩል ይፈስ የነበረ ውሃ መፍሰሱን አቆመ።

ሕዝቡ የዮርዳኖስን ወንዝ ከተሻገሩ በኋላ፣ እግዚአብሔር ኃይለኛውን የኢያሪኮ ከተማ እንዴት እንደሚያጠፋት ለኢያሱ ነገረው። ሕዝቡ ለእግዚአብሔር ታዘዙ። ወታደሮቹና ካህናቱ ልክ እግዚአብሔር እንደ ነገራቸው በቀን አንዴ ለስድስት ቀናት የኢያሪኮን ከተማ ዞሩ።

ከዚያም በሰባተኛው ቀን፣ እስራኤላውያን ሰባት ጊዜ ከተማይቱን ዞሩ። ለመጨረሻ ጊዜ ከተማዪቱን እየዞሩ እያሉ ወታደሮቹ ጮኹ፣ ካህናቱም መለከቶቻቸውን ነፉ።

ከዚያም በኢያሪኮ ዙሪያ የነበረው ግንብ ወደቀ! እግዚአብሔር እንዳዘዘው እስራኤላውያን በከተማይቱ የነበረውን ነገር ሁሉ አጠፉ። የእስራኤላውያን ወገን የሆኑትን ረዓብንና ቤተ ሰብዋን ብቻ አዳኑአቸው። በከነዓን የሚኖሩ ሌሎች ሕዝቦች እስራኤላውያን ኢያሪኮን እንዳጠፉአት በሰሙ ጊዜ፣ እስራኤላውያን እነርሱንም ደግሞ እንደሚያጥቋቸው በማሰብ ፈሩ።

እግዚአብሔር በከነዓን ካሉ ከማናቸውም የሕዝብ ወገኖች ጋር የሰላም ስምምነት እንዳያደርጉ እስራኤላውያንን አዞአቸው ነበር። ነገር ግን ገባዖናውያን የተባሉት ከከነዓናውያን ሕዝብ ወገኖች አንዱ የሆኑት፣ ከከነዓን ራቅ ብሎ ከሚገኝ ቦታ የመጡ መሆናቸውን ለኢያሱ ዋሽተው ነገሩት። ከእነርሱ ጋር የሰላም ስምምነት እንዲያደርግ ኢያሱን ጠየቁት። ገባዖናውያን ከየት እንደ ሆኑ ኢያሱና እስራኤላውያን እግዚአብሔርን አልጠየቁም። ስለዚህ ኢያሱ ከእነርሱ ጋር የሰላም ስምምነት አደረገ።

ገባዖናውያን እንዳታለሉአቸው ባወቁ ጊዜ እስራኤላውያን ተናደዱ፣ ነገር ግን በእግዚአብሔር ፊት የገቡት ቃል ስለ ነበር ከእነርሱ ጋር ያደረጉትን የሰላም ስምምነት ጠበቁ። ቆየት ብሎ በሌላ ጊዜ፣ በከነዓን የነበሩ አሞራውያን የሚባሉ የሌላ ሕዝብ ወገን ነገሥታት፣ የገባዖን ሰዎች ከእስራኤላውያን ጋር የሰላም ስምምነት እንዳደረጉ ሰሙ፣ ስለዚህ ጦር ሠራዊታቸውን አንድ ላይ አስተባበሩና ገባዖናውያንን ወጉ። ገባዖናውያንም እርዳታ ጥየቃ ወደ ኢያሱ መልእክት ላኩ።

ስለዚህ ኢያሱ የእስራኤልን ጦር ሠራዊት ሰበሰበና ወደ ገባዖናውያን ለመድረስ ሌሊቱን ሙሉ ተጓዙ። በማለዳ ሳያስቡት የአሞራውያንን ጦር ሠራዊት መቱ።

በዚያን ቀን እግዚአብሔር ለእስራኤላውያን ተዋጋ። አሞራውያንን አደናገራቸውና ትልልቅ የበረዶ ድንጋይ ልኮ ከአሞራውያን ብዙዎችን ገደለ።

ደግሞ እግዚአብሔር እስራኤላውያን አሞራውያንን ፈጽመው ለማጥፋት በቂ ጊዜ ይኖራቸው ዘንድ ፀሐይ በሰማይ በአንድ ቦታ እንድትቆም አደረገ። በዚያን ቀን እግዚአብሔር ለእስራኤል ታላቅ ድል አጐናጸፋቸው።

እግዚአብሔር እነዚያን ጦር ሠራዊት ካጠፉ በኋላ፣ ብዙዎቹ የከነዓናውያን ሕዝብ ወገኖች እስራኤልን ለመውጋት በአንድነት ተሰበሰቡ። ነገር ግን ኢያሱና እስራኤላውያን ወጉና አጠፉአቸው።

ከዚህ ጦርነት በኋላ እግዚአብሔር ለእያንዳንዱ ለእስራኤል ነገድ ከተስፋዪቱ ምድር የሚደርሰውን ክፍል ሰጠው። ከዚያም እግዚአብሔር ለእስራኤል በድንበሮችዋ ሁሉ ሰላምን ሰጣት።

ኢያሱ ባረጀ ጊዜ፣ የእስራኤልን ሕዝብ ሁሉ አንድ ላይ ጠራ። ከዚያም ኢያሱ እግዚአብሔር በሲና ከእስራኤላውያን ጋር ላደረገው ቃል ኪዳን ሕዝቡ የመታዘዝ ግዴታ እንዳለበቸው አስታወሳቸው። ሕዝቡ ለእግዚአብሔር ታማኞች ሆነው ለመኖርና ሕግጋቱን ለመከተል ቃል ገቡ።
የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከኢያሱ 1-24፡፡