አማርኛ: Open Bible Stories

Updated ? hours ago # views See on DCS

48. ኢየሱስ የተስፋው መሲሕ

Image

እግዚአብሔር ዓለምን በፈጠረ ጊዜ ሁሉም ነገር ፍጹም ነበረ። ኃጢአት አልነበረም። አዳምና ሔዋን እርስ በርሳቸው ይዋደዱ ነበር፣ እግዚአብሔርንም ይወዱት ነበር። በሽታ ወይም ሞት አልነበረም። እግዚአብሔር የፈለገው ዓለም እንደዚህ እንድትሆን ነበር።

Image

ሰይጣን በገነት ሔዋንን ያስት ዘንድ በእባቡ በኩል ተናገረ። በዚያን ጊዜ እርስዋና አዳም በእግዚአብሔር ላይ ኃጢአት ሠሩ። እነርሱ ኃጢአት በመሥራታቸው ምክንያት በምድር ያለ ሰው ሁሉ ይታመማል፤ ይሞታልም።

Image

አዳምና ሔዋን ኃጢአት በመሥራታቸው ምክንያት ከዚህም የበለጠ ክፉ ነገር ሆነ። እነርሱ የእግዚአብሔር ጠላቶች ሆኑ። ከዚህ የተነሣ ከዚያን ጊዜ አንሥቶ ሁሉም ሰው በኃጢአተኛ ባሕርይ ተወልዶአል፤ ደግሞም የእግዚአብሔር ጠላት ሆኖአል። በእግዚአብሔርና በሰዎች መካከል የነበረው ግንኙነት በኃጢአት ምክንያት ተቋረጠ። ነገር ግን እግዚአብሔር ያንን ግንኙነት የመመለስ ዕቅድ ነበረው።

Image

ከሔዋን ዝርያዎች አንዱ የሰይጣንን ራስ እንደሚቀጠቅጥ፣ ሰይጣንም ሰኰናውን እንዲያቈስል እግዚአብሔር ተስፋ ሰጠ። ይህም ሰይጣን መሲሑን ይገድላል፣ ነገር ግን እግዚአብሔር እንደ ገና ከሞት ያስነሣዋል ማለት ነው፣ ከዚያም መሲሑ የሰይጣንን ራስ ለዘላለም ይቀጠቅጠዋል። ከብዙ ዓመታት በኋላ እግዚአብሔር መሲሑ ኢየሱስ መሆኑን ገለጠ።

Image

እግዚአብሔር ምድርን ሁሉ በጥፋት ውሃ ባጠፋ ጊዜ፣ በእርሱ ያመኑትን ሰዎች ለማዳን መርከብ አቀረበ። ልክ እንደዚሁ ሰው ሁሉ በኃጢአቱ ምክንያት መጥፋት ይገባው ነበር፣ ነገር ግን እግዚአብሔር በእርሱ የሚያምኑትን ሁሉ ለማዳን ኢየሱስን ሰጠ።

Image

ለብዙ መቶ ዓመታት ካህናት ሰዎች ለኃጢአታቸው የሚገባቸውን ቅጣት መቀበል እንደሚገባቸው ለማሳየት ስለ ሕዝቡ ኃጢአት ያለ ማቋረጥ ለእግዚአብሔር መሥዋዕት አቀረቡ። ነገር ግን እነዚያ መሥዋዕቶች ኃጢአታቸውን ሊያስወግዱ አልቻሉም። ኢየሱስ ታላቁ ሊቀ ካህናት ነው። ከሌሎች ካህናት በተለየ ሁኔታ በዓለም ላይ ያሉ ሰዎችን ሁሉ ኃጢአት ማስወገድ የሚችል ብቸኛ መሥዋዕት አድርጎ ራሱን አቀረበ። ኢየሱስ ማንኛውም ሰው የሠራውን የእያንዳንዱን ኃጢአት ቅጣት ስለ ወሰደ ፍጹም ሊቀ ካህናት ነው።

Image

እግዚአብሔር ለአብርሃም፣ ‹‹የምድር ሕዝብ ወገኖች ሁሉ በአንተ ዘር ይባረካሉ›› ብሎ ነገረው። ኢየሱስ የአብርሃም ዘር ነው። በእርሱ በኩል የሕዝብ ወገኖች ሁሉ ተባርከዋል፣ ምክንያቱም በኢየሱስ የሚያምን ሰው ሁሉ ከኃጢአት ድኖአል፣ እንዲሁም የአብርሃም መንፈሳዊ ልጅ ይሆናል።

Image

ልጁን ይስሐቅን መሥዋዕት አድርጎ እንዲያቀርብ እግዚአብሔር ለአብርሃም በነገረው ጊዜ፣ እግዚአብሔር በልጁ በይስሐቅ ፈንታ የመሥዋዕት በግ አቀረበ። እኛ ሁላችንም በኃጢአታችን መሞት ይገባናል! ነገር ግን እግዚአብሔር መሥዋዕት ሆኖ በእኛ ቦታ እንዲሞት የእግዚአብሔር በግ የሆነውን ኢየሱስን ሰጠ።

Image

እግዚአብሔር በግብፅ ላይ የመጨረሻውን መቅሠፍት በላከ ጊዜ እንከን የሌለበት ጠቦት እንዲያርዱና ደሙን በበሩ መቃንና ጉበን ላይ እንዲረጩት ለእስራኤላውያን ቤተ ሰቦች ሁሉ ተናገረ። እግዚአብሔርም ደሙን ባየ ጊዜ ቤቶቹን አልፎ ሄደ፤ በኵር ልጆቻቸውንም አልገደለም። ይህ ታሪካዊ ድርጊት ፋሲካ ተብሎአል።

Image

ኢየሱስ የፋሲካ በጋችን ነው። እርሱ ፍጹምና ምንም ኃጢአት የሌለብት የእግዚእብሔር በግ ነው፤ በፋሲካ በዓል ጊዜም ተገደለ። ማንኛውም ሰው በኢየሱስ በሚያምንበት ጊዜ፣ የኢየሱስ ደም ለዚያ ሰው ኃጢአት ክፍያ ነው፣ የእግዚአብሔር ቅጣትም ከዚያ ሰው ላይ ያልፋል።

Image

እግዚአብሔር የተመረጡ ሕዝቡ ከነበሩት ከእስራኤላውያን ጋር ቃል ኪዳን አደረገ። ነገር ግን አሁን እግዚአብሔር ለሁሉም ሰው የሚሆን ዐዲስ ቃል ኪዳን አድርጎአል። በዚህ ዐዲስ ቃል ኪዳን ምክንያት ከማንም ሕዝብ ወገን የሆነ ማንኛውም ሰው በኢየሱስ በማመን የእግዚአብሔር ሕዝብ ወገን መሆን ይችላል።

Image

ሙሴ የእግዚአብሔርን ቃል ያወጀ ታላቅ ነቢይ ነበረ። ኢየሱስ ግን ከሁሉም የላቀ ነቢይ ነው። እርሱ አምላክ ነው፣ ስለዚህ እርሱ ያደረገውና የተናገረው ነገር ሁሉ የእግዚአብሔር ሥራና የእግዚአብሔር ቃል ነው።

Image

እግዚአብሔር ለንጉሥ ዳዊት ከትውልዱ አንዱ ንጉሥ ሆኖ በእግዚአብሔር ሕዝብ ላይ ለዘላለም እንደሚገዛ ተስፋ ሰጠው። ኢየሱስ የእግዚአብሔር ልጅና መሲሑ ስለሆነ፣ ለዘላለም መግዛት የሚችል ልዩ የዳዊት ዘር እርሱ ነው።

Image

ዳዊት የእስራኤል ንጉሥ ነበር፣ ኢየሱስ ግን የፍጥረት ዓለም ሁሉ ንጉሥ ነው! ተመልሶ ይመጣና በፍትሕና በሰላም መንግሥቱን ለዘላለም ይገዛል።

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከዘፍጥረት 1-3፤ 6፤ 14፤ 22፤ ዘጸአት 12፣ 20፤ 2ኛ ሳሙኤል 7፤ ዕብራውያን 3፡1-6፤ 4፡14-5፡10፤ 7፡1-8፡13፤ 9፡11-10፡18፤ ራእይ 21።