48. ኢየሱስ የተስፋው መሲሕ

እግዚአብሔር ዓለምን በፈጠረ ጊዜ ሁሉም ነገር ፍጹም ነበረ። ኃጢአት አልነበረም። አዳምና ሔዋን እርስ በርሳቸው ይዋደዱ ነበር፣ እግዚአብሔርንም ይወዱት ነበር። በሽታ ወይም ሞት አልነበረም። እግዚአብሔር የፈለገው ዓለም እንደዚህ እንድትሆን ነበር።

ሰይጣን በገነት ሔዋንን ያስት ዘንድ በእባቡ በኩል ተናገረ። በዚያን ጊዜ እርስዋና አዳም በእግዚአብሔር ላይ ኃጢአት ሠሩ። እነርሱ ኃጢአት በመሥራታቸው ምክንያት በምድር ያለ ሰው ሁሉ ይታመማል፤ ይሞታልም።

አዳምና ሔዋን ኃጢአት በመሥራታቸው ምክንያት ከዚህም የበለጠ ክፉ ነገር ሆነ። እነርሱ የእግዚአብሔር ጠላቶች ሆኑ። ከዚህ የተነሣ ከዚያን ጊዜ አንሥቶ ሁሉም ሰው በኃጢአተኛ ባሕርይ ተወልዶአል፤ ደግሞም የእግዚአብሔር ጠላት ሆኖአል። በእግዚአብሔርና በሰዎች መካከል የነበረው ግንኙነት በኃጢአት ምክንያት ተቋረጠ። ነገር ግን እግዚአብሔር ያንን ግንኙነት የመመለስ ዕቅድ ነበረው።

ከሔዋን ዝርያዎች አንዱ የሰይጣንን ራስ እንደሚቀጠቅጥ፣ ሰይጣንም ሰኰናውን እንዲያቈስል እግዚአብሔር ተስፋ ሰጠ። ይህም ሰይጣን መሲሑን ይገድላል፣ ነገር ግን እግዚአብሔር እንደ ገና ከሞት ያስነሣዋል ማለት ነው፣ ከዚያም መሲሑ የሰይጣንን ራስ ለዘላለም ይቀጠቅጠዋል። ከብዙ ዓመታት በኋላ እግዚአብሔር መሲሑ ኢየሱስ መሆኑን ገለጠ።

እግዚአብሔር ምድርን ሁሉ በጥፋት ውሃ ባጠፋ ጊዜ፣ በእርሱ ያመኑትን ሰዎች ለማዳን መርከብ አቀረበ። ልክ እንደዚሁ ሰው ሁሉ በኃጢአቱ ምክንያት መጥፋት ይገባው ነበር፣ ነገር ግን እግዚአብሔር በእርሱ የሚያምኑትን ሁሉ ለማዳን ኢየሱስን ሰጠ።

ለብዙ መቶ ዓመታት ካህናት ሰዎች ለኃጢአታቸው የሚገባቸውን ቅጣት መቀበል እንደሚገባቸው ለማሳየት ስለ ሕዝቡ ኃጢአት ያለ ማቋረጥ ለእግዚአብሔር መሥዋዕት አቀረቡ። ነገር ግን እነዚያ መሥዋዕቶች ኃጢአታቸውን ሊያስወግዱ አልቻሉም። ኢየሱስ ታላቁ ሊቀ ካህናት ነው። ከሌሎች ካህናት በተለየ ሁኔታ በዓለም ላይ ያሉ ሰዎችን ሁሉ ኃጢአት ማስወገድ የሚችል ብቸኛ መሥዋዕት አድርጎ ራሱን አቀረበ። ኢየሱስ ማንኛውም ሰው የሠራውን የእያንዳንዱን ኃጢአት ቅጣት ስለ ወሰደ ፍጹም ሊቀ ካህናት ነው።

እግዚአብሔር ለአብርሃም፣ ‹‹የምድር ሕዝብ ወገኖች ሁሉ በአንተ ዘር ይባረካሉ›› ብሎ ነገረው። ኢየሱስ የአብርሃም ዘር ነው። በእርሱ በኩል የሕዝብ ወገኖች ሁሉ ተባርከዋል፣ ምክንያቱም በኢየሱስ የሚያምን ሰው ሁሉ ከኃጢአት ድኖአል፣ እንዲሁም የአብርሃም መንፈሳዊ ልጅ ይሆናል።

ልጁን ይስሐቅን መሥዋዕት አድርጎ እንዲያቀርብ እግዚአብሔር ለአብርሃም በነገረው ጊዜ፣ እግዚአብሔር በልጁ በይስሐቅ ፈንታ የመሥዋዕት በግ አቀረበ። እኛ ሁላችንም በኃጢአታችን መሞት ይገባናል! ነገር ግን እግዚአብሔር መሥዋዕት ሆኖ በእኛ ቦታ እንዲሞት የእግዚአብሔር በግ የሆነውን ኢየሱስን ሰጠ።

እግዚአብሔር በግብፅ ላይ የመጨረሻውን መቅሠፍት በላከ ጊዜ እንከን የሌለበት ጠቦት እንዲያርዱና ደሙን በበሩ መቃንና ጉበን ላይ እንዲረጩት ለእስራኤላውያን ቤተ ሰቦች ሁሉ ተናገረ። እግዚአብሔርም ደሙን ባየ ጊዜ ቤቶቹን አልፎ ሄደ፤ በኵር ልጆቻቸውንም አልገደለም። ይህ ታሪካዊ ድርጊት ፋሲካ ተብሎአል።

ኢየሱስ የፋሲካ በጋችን ነው። እርሱ ፍጹምና ምንም ኃጢአት የሌለብት የእግዚእብሔር በግ ነው፤ በፋሲካ በዓል ጊዜም ተገደለ። ማንኛውም ሰው በኢየሱስ በሚያምንበት ጊዜ፣ የኢየሱስ ደም ለዚያ ሰው ኃጢአት ክፍያ ነው፣ የእግዚአብሔር ቅጣትም ከዚያ ሰው ላይ ያልፋል።

እግዚአብሔር የተመረጡ ሕዝቡ ከነበሩት ከእስራኤላውያን ጋር ቃል ኪዳን አደረገ። ነገር ግን አሁን እግዚአብሔር ለሁሉም ሰው የሚሆን ዐዲስ ቃል ኪዳን አድርጎአል። በዚህ ዐዲስ ቃል ኪዳን ምክንያት ከማንም ሕዝብ ወገን የሆነ ማንኛውም ሰው በኢየሱስ በማመን የእግዚአብሔር ሕዝብ ወገን መሆን ይችላል።

ሙሴ የእግዚአብሔርን ቃል ያወጀ ታላቅ ነቢይ ነበረ። ኢየሱስ ግን ከሁሉም የላቀ ነቢይ ነው። እርሱ አምላክ ነው፣ ስለዚህ እርሱ ያደረገውና የተናገረው ነገር ሁሉ የእግዚአብሔር ሥራና የእግዚአብሔር ቃል ነው።

እግዚአብሔር ለንጉሥ ዳዊት ከትውልዱ አንዱ ንጉሥ ሆኖ በእግዚአብሔር ሕዝብ ላይ ለዘላለም እንደሚገዛ ተስፋ ሰጠው። ኢየሱስ የእግዚአብሔር ልጅና መሲሑ ስለሆነ፣ ለዘላለም መግዛት የሚችል ልዩ የዳዊት ዘር እርሱ ነው።

ዳዊት የእስራኤል ንጉሥ ነበር፣ ኢየሱስ ግን የፍጥረት ዓለም ሁሉ ንጉሥ ነው! ተመልሶ ይመጣና በፍትሕና በሰላም መንግሥቱን ለዘላለም ይገዛል።
የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከዘፍጥረት 1-3፤ 6፤ 14፤ 22፤ ዘጸአት 12፣ 20፤ 2ኛ ሳሙኤል 7፤ ዕብራውያን 3፡1-6፤ 4፡14-5፡10፤ 7፡1-8፡13፤ 9፡11-10፡18፤ ራእይ 21።