አማርኛ: Open Bible Stories

Updated ? hours ago # views See on DCS

50. ኢየሱስ ይመለሳል

Image

ለ2,000 ዓመታት ያህል በዓለም ዙሪያ ያሉ ብዙ ሰዎች ስለ መሲሑ ኢየሱስ የሚነገረውን የምሥራች እየሰሙ ቈይተዋል። ቤተ ክርስቲያን እያደገች ኖራለች። ኢየሱስ በዓለም ፍጻሜ እንደሚመለስ ተስፋ ሰጥቶአል። እርሱ ገና እስካሁን ባይመለስም እንኳ፣ የሰጠውን የተስፋ ቃል ለመፈጸም ይመጣል።

Image

እግዚአብሔር የኢየሱስን መመለስ እየተጠባበቅን፣ ቅዱስ በሆነና እርሱን በሚያስከብረው መንገድ እንድንኖር ይፈልጋል። ደግሞም ስለ መንግሥቱ ለሌሎች እንድንናገር ይፈልጋል። ኢየሱስ በምድር ላይ ይኖር በነበረበት ጊዜ ሲያስተምር፣ ‹‹ደቀ መዛሙርቴ ስለ እግዚአብሔር መንግሥት የምሥራች በዓለም ሁሉ በሁሉም ስፍራ ላሉ ሰዎች ይሰብካሉ፣ በዚያን ጊዜ ፍጻሜ ይመጣል›› ብሏል።

Image

ብዙ የሕዝብ ወገኖች አሁንም ስለ ኢየሱስ አልሰሙም። ኢየሱስ ወደ ሰማይ ከመመለሱ በፊት፣ የምሥራቹን ላልሰሙት ሰዎች እንዲያውጁ ለክርስቲያኖች ነገራቸው። ‹‹ሂዱና የሕዝብ ወገኖችን ሁሉ ደቀ መዛሙርት አድርጉአቸው!›› አለ። ደግሞም ‹‹መከሩም ደርሶአል!›› አለ።

Image

ደግሞም ኢየሱስ እንዲህ አለ፣ ‹‹አገልጋይ ከጌታው አይበልጥም። ልክ የዚህ ዓለም ባለ ሥልጣናት እኔን እንደ ጠሉኝ፤ እናንተንም በእኔ ምክንያት ያሠቃዩአችሁና ይገድሉአችኋል። ምንም እንኳ በዚህ ዓለም መከራ ብትቀበሉም፣ አይዞአችሁ ምክንያቱም እኔ ይህን ዓለም የሚገዛውን ሰይጣንን አሸንፌዋለሁ። እናንተ በእኔ አምናችሁ እስከ መጨረሻ ብትጸኑ፣ በዚያን ጊዜ እግዚአብሔር ያድናችኋል!››

Image

ኢየሱስ የዓለም ፍጻሜ በሚሆንበት ጊዜ፣ በሰዎች ላይ የሚደርሰውን ነገር ለማብራራት ለደቀ መዛሙርቱ አንድ ምሳሌ ነገራቸው። ‹‹አንድ ሰው በእርሻው መልካም ዘርን ዘራ። ተኝቶ እያለ ጠላቱ መጣና በስንዴው ላይ የአረም ዘር ዘራበትና ሄደ።››

Image

‹‹የተዘራው ስንዴ በበቀለ ጊዜ፣ የሰውዬው አገልጋዮች፣ ‹ጌታው፣ በዚያ እርሻ መልካም ዘር ዘርተህ ነበር። ታዲያ በውስጡ ለምንድን ነው አረም ያለበት?› ብለው ጠየቁት፣ ጌታውም፣ ‹የዘራው ጠላት መሆን አለበት››› ብሎ መለሰላቸው።

Image

‹‹አገልጋዮቹ ለጌታቸው፣ ‹አረሙን እንንቀለውን?› ብለው ጠየቁት። ጌታቸው እንዲህ አለ፣ ‹አይደለም። ይህንን ብታደርጉ ስንዴውንም ትነቅሉታላችሁ። እስከ መከር ድረስ ይቆዩ፤ በዚያን ጊዜ መላእክትን እልካለሁ። እነርሱም አረሙን ሰብስበው ያቃጥላሉ። ስንዴውን ግን በጎተራዬ ያከማቻሉ››› አላቸው።

Image

ደቀ መዛሙርቱ የምሳሌው ትርጕም አልገባቸውም፣ ስለዚህ እንዲያብራራላቸው ኢየሱስን ጠየቁት። ኢየሱስ እንዲህ አለ፣ ‹‹መልካሙን ዘር የዘራው ሰው መሲሑን ይወክላል። እርሻው ዓለምን ይወክላል። መልካሙ ዘር የእግዚአብሔርን መንግሥት ሰዎች ይወክላል።››

Image

‹‹አረሙ ከክፉው ወገን የሆኑ ሰዎችን ይወክላል። አረሙን የዘራው ጠላት ዲያብሎስን ይወክላል። መከሩ የዓለምን ፍጻሜ ይወክላል፣ አጫጆቹም የእግዚአብሔርን መላእክት ይወክላሉ።

Image

‹‹በዓለም ፍጻሜ፣ መላእክት የዲያብሎስ ወገኖች የሆኑ ሰዎችን ሁሉ በአንድ ላይ ይሰበስቡና ወደሚንቀለቀል እሳት ይጥሉአቸዋል፣ በዚያም ይጮኻሉ፤ አስከፊ በሆነ ሥቃይም ጥርሶቻቸውን ያፋጫሉ፡፡ በዚያን ጊዜ ጻድቃን በአባታቸው በእግዚአብሔር መንግሥት እንደ ፀሐይ ያበራሉ፡፡››

Image

ደግሞም ኢየሱስ ልክ ከዓለም ፍጻሜ በፊት ወደ ምድር እንደሚመለስ ተናገረ። በሄደበት አኳኋን ተመልሶ ይመጣል፣ ይኸውም፣ አካላዊ ሰውነት ይኖረዋል፣ በሰማይ ደመናም ይመጣል። ኢየሱስ በሚመለስበት ጊዜ እያንዳንዱ በክርስቶስ አምኖ የሞተ ክርስቲያን ከሙታን ይነሣና በሰማይ ላይ ይገናኘዋል።

Image

በዚያን ጊዜ ገና በሕይወት ያሉ ክርስቲያኖች ወደ ሰማይ ይነጠቁና ከሙታን ከተነሡ ሌሎች ክርስቲያኖች ጋር ይቀላቀላሉ። በዚያ ሁላቸውም ከኢየሱስ ጋር ይሆናሉ። ከዚያ በኋላ ኢየሱስ ከሕዝቡ ጋር ፍጹም በሆነ ሰላምና አንድነት ለዘላለም ይኖራል።

Image

ኢየሱስ በእርሱ ለሚያምኑ ሁሉ አክሊል ለመስጠት ተስፋ ሰጥቶአል። እነርሱ ፍጹም በሆነ ሰላም ከእግዚአብሔር ጋር ለዘላለም ይኖራሉ ይነግሣሉም።

Image

ነገር ግን እግዚአብሔር በኢየሱስ በማያምኑ ሁሉ ላይ ይፈርዳል። ለዘላለም ወደሚያለቅሱበትና በሥቃይ ጥርሶቻቸውን ወደሚያፏጩበት ወደ ገሃነም እሳት ይጥላቸዋል። ከቶ የማይጠፋ እሳት ባለማቋረጥ ያቃጥላቸዋል።

Image

ኢየሱስ በሚመለሰበት ጊዜ፣ ሰይጣንና መንግሥቱን ሙሉ በሙሉ ያጠፋቸዋል። ሰይጣንን ለእግዚአብሔር ከመታዘዝ ይልቅ እርሱን ለመከተል ከመረጡት ሁሉ ጋር ለዘላለም ወደሚቃጠሉበት ወደ ገሃነም ይጥለዋል።

Image

አዳምና ሔዋን ለእግዚአብሔር ስላልታዘዙና ኃጢአትን ወደዚህ ዓለም ስላመጡ፣ እግዚአብሔር ዓለምን ረገማት፤ ሊያጠፋትም ወሰነ። ነገር ግን አንድ ቀን እግዚአብሔር ፍጹም የሆነ ዐዲስ ሰማይና ዐዲስ ምድር ይፈጥራል።

Image

ኢየሱስና ሕዝቡ በዐዲሲቱ ምድር ይኖራሉ፣ ኢየሱስ በሁሉም ነገር ላይ ለዘላለም ይነግሣል፡፡ እርሱ እንባን ሁሉ ያብሳል፣ ከእንግዲህ ወዲያ ሥቃይ፣ ሐዘን፣ ልቅሶ፣ ክፋት፣ ሕመም፣ ወይም ሞት አይኖርም፡፡ ኢየሱስ መንግሥቱን በሰላምና በፍትሕ ይገዛል፣ ለዘላለምም ከሕዝቡ ጋር ይሆናል፡፡

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከማቴዎስ 24፡14፤ 28፡18፤ ዮሐንስ 15፡20፤ 16፡33፤ ራእይ 2፡10፤ ማቴዎስ 13፡24-30፤ 36-42፤ 1ኛ ተሰሎንቄ 4፡13-5፡11፤ ያዕቆብ 1፡12፤ ማቴዎስ 22፡13፤ ራእይ 20፡10፤ 21፡1-22፡21፡፡