አማርኛ: Open Bible Stories

Updated ? hours ago # views See on DCS

37. ኢየሱስ አልዓዛርን ከሞት አስነሣ

Image

አንድ ቀን ኢየሱስ አልዓዛር በጣም ታሞአል የሚል መልእክት ደረሰው፡፡ አልዓዛርና ሁለቱ እኅቶቹ ማርያምና ማርታ የኢየሱስ የቅርብ ወዳጆች ነበሩ፡፡ ኢየሱስ ይህንን ወሬ በሰማ ጊዜ፣ ‹‹ይህ ሕመም ለእግዚአብሔር ክብር ነው እንጂ ለሞት አይደለም›› አለ፡፡ ኢየሱስ እነርሱን ይወዳቸው ነበር፣ ነገር ግን ለሁለት ቀናት በነበረበት ስፍራ ቆየ፡፡

Image

ሁለቱ ቀናት ካለፉ በኋላ፣ ኢየሱስ ደቀ መዛሙርቱን፣ ‹‹ወደ ይሁዳ ምድር ተመልሰን እንሂድ›› አላቸው፡፡ ደቀ መዛሙርቱም መልሰው ‹‹ነገር ግን መምህር ሆይ፣ ‹‹ከጥቂት ጊዜ በፊት በዚያ ያሉት ሕዝብ ሊገድሉህ ይፈልጉ ነበር!›› አሉ፡፡ ኢየሱስ፣ ‹‹ወዳጃችን አልዓዛር አንቀላፍቶአል፣ ከእንቅልፉ ማስነሣት አለብኝ›› አላቸው፡፡

Image

የኢየሱስ ደቀ መዛሙርት፣ ‹‹ጌታ ሆይ፣ አልዓዛር ተኝቶስ ከሆነ፣ ተሽሎታል›› ብለው መለሱለት፡፡ በዚያን ጊዜ ኢየሱስ፣ ‹‹አልዓዛር ሞቶአል፡፡ እናንተ በእኔ ታምኑ ዘንድ እዚያ ባለመኖሬ ደስ ብሎኛል›› ብሎ በግልጽ ነገራቸው።

Image

ኢየሱስ አልዓዛር ወደ ተወለደበት ከተማ በደረሰ ጊዜ፣ አልዓዛር ከሞተ አራት ቀን ሆኖት ነበር፡፡ ማርታ ኢየሱስን ልትገናኘው ወጣችና እንዲህ አለች፣ ‹‹ጌታ ሆይ፣ አንተ እዚህ ብትኖር ኖሮ ወንድሜ አይሞትም ነበር፡፡ ነገር ግን እግዚአብሔር የምትለምነውን ሁሉ እንደሚሰጥህ አምናለሁ፡፡››

Image

ኢየሱስም መልሶ፣ ‹‹እኔ ትንሣኤና ሕይወት ነኝ፡፡ በእኔ የሚያምን ሁሉ ቢሞት እንኳ ሕያው ይሆናል፡፡ በእኔ የሚያምን ሁሉ ከቶ አይሞትም፡፡ ይህን ታምኛለሽን?›› አላት፡፡ ማርታም፣ ‹‹አዎን፣ ጌታ ሆይ! አንተ መሲሑ፣ የእግዚአብሔር ልጅ መሆንህን አምናለሁ›› ብላ መለሰችለት፡፡

Image

ከዚያም ማርያም መጣች፡፡ በኢየሱስ እግር ወደቀችና፣ ‹‹ጌታ ሆይ፣ አንተ በዚህ ኖረህ ብትሆን ኖሮ ወንድሜ ባልሞተም ነበር›› አለች፡፡ ኢየሱስ፣ ‹‹አልዓዛርን ወዴት ነው ያኖራችሁት?›› ብሎ ጠየቃቸው፡፡ እነርሱም ‹‹በመቃብር ነው፡፡ ናና እይ›› ብለው ነገሩት፡፡ ከዚያም ኢየሱስ አለቀሰ፡፡

Image

መቃብሩ ዋሻ ነበር፣ ድንጋይም በአፉ ላይ ተገጥሞበት ነበር፡፡ ኢየሱስ ወደ መቃብሩ በደረሰ ጊዜ ‹‹ድንጋዩን አንከባሉት›› ብሎ ነገራቸው፡፡ ነገር ግን ማርታ፣ ‹‹ከሞተ አራት ቀን ሆኖታል፡፡ አሁን ይሸታል›› አለችው፡፡

Image

ኢየሱስ፣ ‹‹በእኔ ብታምኚስ የእግዚአብሔርን ክብር ታይዋለሽ ብዬ አልነገርኩሽምን?›› አላት፡፡ ስለዚህ ድንጋዩን አንከባለሉት፡፡

Image

ከዚያ በኋላ ኢየሱስ ወደ ላይ ተመለከተና፣ ‹‹አባት ሆይ፣ ስለምትሰማኝ አመሰግንሃለሁ፡፡ አንተ ሁልጊዜ እንደምትሰማኝ ዐውቃለሁ፣ ነገር ግን አንተ እንደ ላክኸኝ ያምኑ ዘንድ እዚህ ስለ ቆሙት ስለ እነዚህ ሰዎች ሁሉ ይህን እላለሁ›› አለ፡፡ ከዚያም ኢየሱስ፣ ‹‹አልዓዛር ሆይ፣ ወደ ውጭ ና!›› ብሎ ጮኸ፡፡

Image

ስለዚህ አልዓዛር ወጣ! በከፈን እንደ ተገነዘ ነበር፡፡ ኢየሱስም፣ ‹‹ፍቱትና ይሂድ ተዉት!›› አላቸው፡፡ ከአይሁድ ብዙዎች በዚህ ተአምር ምክንያት በኢየሱስ አመኑ፡፡

Image

ነገር ግን የአይሁድ የሃይማኖት መሪዎች ቀኑ፣ ስለዚህ ኢየሱስንና አልዓዛርን እንዴት መግደል እንዳለባቸው ለማቀድ በአንድ ላይ ተሰበሰቡ፡፡

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከዮሐንስ 11፡1-46፡፡