33. የአርሶ አደሩ ታሪክ

አንድ ቀን ኢየሱስ በሐይቁ ዳርቻ አጠገብ በጣም ብዙ ሕዝብ እያስተማረ ነበር፡፡ ኢየሱስ ሊናገራቸው በቂ ቦታ ለማግኘት በውሃው ዳርቻ በጀልባ ገብቶ እስኪቀመጥ ድረስ በጣም ብዙ ሰዎች ሊሰሙት መጡ፡፡ በጀልባው ተቀመጠና ሕዝቡን አስተማረ፡፡

ኢየሱስ ይህንን ምሳሌ ተናገረ፡፡ ‹‹አንድ አርሶ አደር ዘር ሊዘራ ወጣ፡፡ በእጁ ዘሩን ሲዘራ አንዳንዱ በመንገድ ዳር ወደቀ፣ ወፎችም መጥተው ያን ዘር በሙሉ በሉት፡፡››

‹‹ሌላው ዘር ብዙ አፈር በሌለበት በአለታማ መሬት ላይ ወደቀ፣ ዘሩም ቶሎ ወዲያው በቀለ፤ ነገር ግን ብዙ አፈር ስለሌለ ሥሩ ወደ መሬት መጥለቅ አልቻለም፡፡ ፀሐይዋ በወጣችና በሞቀች ጊዜ፣ ቡቃያው ጠወለገና ደረቀ፡፡››

‹‹አሁንም ሌላው ዘር በእሾኽ መካከል ወደቀ፡፡ ይህ ዘር መብቀል ጀመረ፣ ነገር ግን እሾኹ አነቀው፡፡ ስለዚህ በእሾኻማው መሬት ላይ የበቀለው ቡቃያ ምንም ፍሬ አላፈራም፡፡››

‹‹ሌላው ዘር በመልካም መሬት ላይ ወደቀ፡፡ ይህ ዘር በቀለና አንዱ 30፣ አንዱ 60፣ አንዱም መቶ ፍሬ ሰጠ፡፡ ጆሮ ያለው ይስማ!››

ይህ ምሳሌ ደቀ መዛሙርቱን ግራ አጋባቸው፡፡ ስለዚህ ኢየሱስ እንዲህ ብሎ አብራራላቸው፣ ‹‹ዘሩ የእግዚአብሔር ቃል ነው፡፡ በመንገዱ ዳር የተዘራው ዘር የሚያሳየው የእግዚአብሔርን ቃል የሚሰማ ሰው ነው፣ ነገር ግን አያስተውለውም፣ ዲያብሎስም ቃሉን ይወስድበታል፡፡››

‹‹በአለታማ መሬት የተዘራው ዘር የሚያሳየው የእግዚአብሔርን ቃል ሰምቶ በደስታ የሚቀበለው ሰው ነው፡፡ ነገር ግን መከራ ወይም ስደት በሚያጋጥመው ጊዜ እምነቱን ይተዋል፡፡››

‹‹በእሾኻማው መሬት ላይ የተዘራው ዘር የሚያሳየው የእግዚአብሔርን ቃል የሚሰማ ሰው ነው፣ ነገር ግን ከጊዜ በኋላ የዚህ ዓለም ዐሳብ፣ ባለጠግነትና ደስታ ለእግዚአብሔር ያለውን ፍቅር ያንቃል፡፡ ከዚህ የተነሣ፣ የሰማው ትምህርት ፍሬ አያፈራም፡፡

‹‹በመልካሙ መሬት ላይ የተዘራው ዘር የሚያሳየው ግን የእግዚአብሔርን ቃል የሚሰማ፣ የሚያምነውና ፍሬ የሚያፈራ ሰው ነው፡፡››
የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከማቴዎስ 13፡1-8፣ 18-23፤ ማርቆስ 4፡1-8፣ 13-20፤ ሉቃስ 8፡4-15፡፡