41. እግዚአብሔር ኢየሱስን ከሙታን አስነሣው

ወታደሮቹ ኢየሱስን ከሰቀሉት በኋላ፣ የማያምኑ የአይሁድ መሪዎች ጲላጦስን፣ ‹‹ያ ውሸታም ኢየሱስ፣ ከሦስት ቀን በኋላ ከሙታን እነሣለሁ ብሎአል፡፡ ደቀ መዛሙርቱ ሥጋውን እንዳይሰርቁትና ከሙታን ተነሥቶአል እንዳይሉ መቃብሩ መጠበቅ አለበት›› አሉት፡፡

ጲላጦስ፣ ‹‹ወታደሮችን ውሰዱና መቃብሩን በደንብ እንዲጠብቁ አድርጉ›› አለ። ስለዚህ በመቃብሩ መግቢያ ባለው ድንጋይ ላይ ማኅተም አደረጉና ሥጋውን ማንም እንዳይሰርቀው በዚያ ወታደሮችን አቆሙ።

ኢየሱስ የተሰቀለበት ቀን ማግስት ሰንበት ነበረ። አይሁድ በዚያ ቀን ወደ መቃብር እንዲሄዱ አይፈቀድላቸውም ነበር። ስለዚህ ከሰንበት ቀን በኋላ በማለዳ ጥቂት ሴቶች ሥጋው ላይ ሽቱ ለማድረግ ወደ ኢየሱስ መቃብር ሊሄዱ ተዘጋጁ።

በድንገትም ታላቅ የምድር መንቀጥቀጥ ሆነ። እንደ መብረቅ የሚያበራ መልአክ ከሰማይ ታየ። የመቃብሩን መግቢያ ከድኖ የነበረውን ድንጋይ አንከባለለና ተቀመጠበት። መቃብሩን ይጠብቁ የነበሩት ወታደሮች በፍርሃት እንደ ሞቱ ሰዎች ሆነው መሬት ላይ ወደቁ።

ሴቶቹ ወደ መቃብሩ በደረሱ ጊዜ መልአኩ፣ ‹‹አትፍሩ! ኢየሱስ እዚህ የለም። ልክ እነሣለሁ ብሎ እንደ ተናገረው ከሞት ተነሥቶአል! መቃብሩን ተመልከቱ›› ብሎ ነገራቸው። ሴቶቹ ወደ መቃብሩ ውስጥ ተመለከቱና የኢየሱስን ሥጋ ያኖሩበትን ስፍራ ዐዩ። ሥጋው በዚያ አልነበረም።

ከዚያም መልአኩ ለሴቶቹ፣ ‹‹ሂዱና ‹ኢየሱስ ከሙታን ተነሥቶአል፤ ቀድሞአችሁ ወደ ገሊላ ይሄዳል ብላችሁ ለደቀ መዛሙርቱ ንገሩአቸው››› ብሎ ነገራቸው።

ሴቶቹ በፍርሃትና በታላቅ ደስታ ተሞልተው ነበር። የምሥራቹን ለደቀ መዛሙርቱ ለመንገር እየሮጡ ሄዱ።

ሴቶቹ የምሥራቹን ለደቀ መዛሙርቱ ለመንገር በመሄድ ላይ እያሉ፣ ኢየሱስ ታያቸው፣ እነርሱም ሰገዱለት። ኢየሱስ፣ ‹‹አትፍሩ። ወደ ገሊላ እንዲሄዱ ለደቀ መዛሙርቴ ንገሩአቸው። በዚያ ያዩኛል›› አላቸው።
የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከማቴዎስ 27፡62-28፡15፤ ማርቆስ 16፡1-11፤ ሉቃስ 24፡1-12፤ ዮሐንስ 20፡1-18።