አማርኛ: Open Bible Stories

Updated ? hours ago # views See on DCS

41. እግዚአብሔር ኢየሱስን ከሙታን አስነሣው

Image

ወታደሮቹ ኢየሱስን ከሰቀሉት በኋላ፣ የማያምኑ የአይሁድ መሪዎች ጲላጦስን፣ ‹‹ያ ውሸታም ኢየሱስ፣ ከሦስት ቀን በኋላ ከሙታን እነሣለሁ ብሎአል፡፡ ደቀ መዛሙርቱ ሥጋውን እንዳይሰርቁትና ከሙታን ተነሥቶአል እንዳይሉ መቃብሩ መጠበቅ አለበት›› አሉት፡፡

Image

ጲላጦስ፣ ‹‹ወታደሮችን ውሰዱና መቃብሩን በደንብ እንዲጠብቁ አድርጉ›› አለ። ስለዚህ በመቃብሩ መግቢያ ባለው ድንጋይ ላይ ማኅተም አደረጉና ሥጋውን ማንም እንዳይሰርቀው በዚያ ወታደሮችን አቆሙ።

Image

ኢየሱስ የተሰቀለበት ቀን ማግስት ሰንበት ነበረ። አይሁድ በዚያ ቀን ወደ መቃብር እንዲሄዱ አይፈቀድላቸውም ነበር። ስለዚህ ከሰንበት ቀን በኋላ በማለዳ ጥቂት ሴቶች ሥጋው ላይ ሽቱ ለማድረግ ወደ ኢየሱስ መቃብር ሊሄዱ ተዘጋጁ።

Image

በድንገትም ታላቅ የምድር መንቀጥቀጥ ሆነ። እንደ መብረቅ የሚያበራ መልአክ ከሰማይ ታየ። የመቃብሩን መግቢያ ከድኖ የነበረውን ድንጋይ አንከባለለና ተቀመጠበት። መቃብሩን ይጠብቁ የነበሩት ወታደሮች በፍርሃት እንደ ሞቱ ሰዎች ሆነው መሬት ላይ ወደቁ።

Image

ሴቶቹ ወደ መቃብሩ በደረሱ ጊዜ መልአኩ፣ ‹‹አትፍሩ! ኢየሱስ እዚህ የለም። ልክ እነሣለሁ ብሎ እንደ ተናገረው ከሞት ተነሥቶአል! መቃብሩን ተመልከቱ›› ብሎ ነገራቸው። ሴቶቹ ወደ መቃብሩ ውስጥ ተመለከቱና የኢየሱስን ሥጋ ያኖሩበትን ስፍራ ዐዩ። ሥጋው በዚያ አልነበረም።

Image

ከዚያም መልአኩ ለሴቶቹ፣ ‹‹ሂዱና ‹ኢየሱስ ከሙታን ተነሥቶአል፤ ቀድሞአችሁ ወደ ገሊላ ይሄዳል ብላችሁ ለደቀ መዛሙርቱ ንገሩአቸው››› ብሎ ነገራቸው።

Image

ሴቶቹ በፍርሃትና በታላቅ ደስታ ተሞልተው ነበር። የምሥራቹን ለደቀ መዛሙርቱ ለመንገር እየሮጡ ሄዱ።

Image

ሴቶቹ የምሥራቹን ለደቀ መዛሙርቱ ለመንገር በመሄድ ላይ እያሉ፣ ኢየሱስ ታያቸው፣ እነርሱም ሰገዱለት። ኢየሱስ፣ ‹‹አትፍሩ። ወደ ገሊላ እንዲሄዱ ለደቀ መዛሙርቴ ንገሩአቸው። በዚያ ያዩኛል›› አላቸው።

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከማቴዎስ 27፡62-28፡15፤ ማርቆስ 16፡1-11፤ ሉቃስ 24፡1-12፤ ዮሐንስ 20፡1-18።