አማርኛ: Open Bible Stories

Updated ? hours ago # views See on DCS

47. ጳውሎስና ሲላስ በፊልጵስዩስ

Image

ሳውል በሮማ የንጉሠ ነገሥት ግዛት ሁሉ በሚጓዝበት ጊዜ፣ ‹‹ጳውሎስ›› የሚለውን ሮማዊ ስሙን ይጠቀም ጀመር። አንድ ቀን ጳውሎስና ጓደኛው ሲላስ ስለ ኢየሱስ የምሥራች ሊያውጁ ወደ ፊልጵስዩስ ከተማ ሄዱ። ሰዎች ሊጸልዩ ወደ ተሰበሰቡበት ከከተማይቱ ውጭ በወንዙ አጠገብ ወዳለ ስፍራ ሄዱ። በዚያ ነጋዴ የነበረች ልድያ የሚሉአት አንዲት ሴት አገኙ። እርስዋ እግዚአብሔርን የምትወድና የምታመልክ ሴት ነበረች።

Image

ስለ ኢየሱስ የተነገረውን መልእክት እንድታምን እግዚአብሔር የልድያን ልብ ከፈተላት፤ እርስዋና ቤተ ሰብዋ ተጠመቁ፣ በቤትዋ እንዲቀመጡም ጳውሎስንና ሲላስን ጋበዘቻቸው፣ ስለዚህ እነርሱ ከእርስዋና ከቤተ ሰብዋ ጋር ለተወሰነ ጊዜ ቆዩ።

Image

ጳውሎስና ሲላስ ብዙ ጊዜ በጸሎት ስፍራ ከሰዎች ጋር ይገናኙ ነበር። በየዕለቱ ወደዚያ ሲሄዱ ጋኔን የያዛት አንዲት የቤት ሠራተኛ ትከተላቸው ነበር። እርሷም በዚህ ጋኔን አማካይነት ስለ መጪው ጊዜ ለሰዎች ትተነብይላቸው ነበር፣ ስለዚህ በጥንቈላ ለጌቶችዋ ብዙ ገንዘብ ታስገኝ ነበር።

Image

የቤት ሠራተኛይቱም እነርሱ ሲዘዋወሩ እየተከተለቻቸው፣ ‹‹እነዚህ ሰዎች የልዑል እግዚአብሔር አገልጋዮች ናቸው። ለእናንተ የመዳንን መንገድ ይነግሩአችኋል!›› በማለት መጮህዋን ቀጠለች። ይህንን ደጋግማ ስለ አደረገች ጳውሎስ ተበሳጨ።

Image

በመጨረሻም አንድ ቀን ሠራተኛይቱ መጮኽ በጀመረች ጊዜ ጳውሎስ ወደ እርስዋ ዘወር አለና በእርስዋ የነበረውን ጋኔን፣ ‹‹በኢየሱስ ስም ከእርስዋ ውጣ›› አለው፡፡ ወዲያውኑ ጋኔኑ ለቀቃት፡፡

Image

በዚህ የባሪያዪቱ ጌቶች በጣም ተቈጡ! ያለ ጋኔኑ ባሪያዪቱ ልጅ ስለ ሰዎች መጪ ጊዜ መናገር እንደማትችል ዐወቁ። ይህም ማለት ለሰዎች የወደፊቱን ነገር ልትነግራቸው ስለማትችል ለጌቶችዋ ገንዘብ አይከፍሉም ማለት ነው።

Image

ስለዚህ የባሪያዪቱ ጌቶች ጳውሎስንና ሲላስን ወደ ሮማ ባለ ሥልጣናት ወሰዱአቸው፣ እነርሱም ደብድበው ወደ እስር ቤት ጣሉአቸው።

Image

የሮማ ወታደሮችም ጳውሎስንና ሲላስን በእስር ቤት ውስጠኛ ክፍል አሰሩአቸው፤ እግሮቻቸውንም ከግንድ ጋር አሰሩአቸው፡፡ ሆኖም ግን እኩለ ሌሊት ላይ ለእግዚአብሔር የምስጋና መዝሙር ዘመሩ፡፡

Image

በድንገት ኃይለኛ የመሬት መንቀጥቀጥ ሆነ! የእስር ቤቱ በሮች ሁሉ ወለል ብለው ተከፈቱ፣ የእስረኞቹ ሁሉ ሰንሰለቶችም ረገፉ።

Image

የእስር ቤቱ ጠባቂ ከእንቅልፉ ነቃ፣ የእስር ቤቱ በሮች ሁሉ መከፈታቸውን ባየ ጊዜ በጣም ደነገጠ! እስረኞቹ ሁሉ ያመለጡ መሰለው፣ ስለዚህ ራሱን ለመግደል ዐሰበ። (እስረኞቹ እንዲያመልጡ ካደረገ የሮማ ባለ ሥልጣናት እንደሚገድሉት ያውቅ ነበር።) ነገር ግን ጳውሎስ ዐየውና፣ ‹‹ተው! ራስህን አትጕዳ። እኛ ሁላችንም እዚህ አለን›› ብሎ ጮኸ።

Image

የእስር ቤቱ ጠባቂ ወደ ጳውሎስና ሲላስ እየተንቀጠቀጠ መጣና፣ ‹‹እድን ዘንድ ምን ላድርግ?›› ብሎ ጠየቀ። ጳውሎስ፣ ‹‹በጌታ በኢየሱስ እመን፣ አንተና ቤተ ሰዎችህ ትድናላችሁ›› ብሎ መለሰለት። ከዚያም የእስር ቤት ጠባቂው ጳውሎስንና ሲላስን ወደ ቤቱ ወሰዳቸውና ቊስላቸውን አጠበላቸው። ጳውሎስ በቤቱ ለነበሩት ሁሉ ስለ ኢየሱስ የምሥራች ሰበከላቸው።

Image

የእስር ቤት ጠባቂውና መላው ቤተ ሰቡ በኢየሱስ አምነው ተጠመቁ። ከዚያም የእስር ቤት ጠባቂው ለጳውሎስና ለሲላስ ምግብ አቀረበላቸውና በአንድነት ደስ አላቸው።

Image

በማግስቱ የከተማው መሪዎች ጳውሎስንና ሲላስን ከእስር ቤት ፈቱአቸውና ከፊልጵስዩስ እንዲሄዱ ጠየቁአቸው፡፡ ጳውሎስና ሲላስ ልድያንና አንዳንድ ሌሎች ወዳጆችን ጐበኙና ከተማይቱን ለቀው ሄዱ፡፡ የኢየሱስ የምሥራች ቃል መስፋፋቱን ቀጠለ፤ ቤተ ክርስቲያንም ማደግዋን ቀጠለች፡፡

Image

ጳውሎስና ሌሎች ክርስቲያን መሪዎች ስለ ኢየሱስ የምሥራች እየሰበኩና እያስተማሩ ወደ ብዙ ከተሞች ተጓዙ። ደግሞም በአብያተ ክርስቲያናቱ ላሉ አማኞች ሊያበረታቱአቸውና ሊያስተምሩአቸው ብዙ መልእክቶችን ጻፉላቸው። ከእነዚህ መልእክቶች አንዳንዶቹ በመጽሐፍ ቅዱስ ያሉት መጻሕፍት ሆኑ።

የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከሐዋርያት ሥራ 16፡11-40።