22. የዮሐንስ መወለድ

አስቀድሞ እግዚአብሔር በመላእክቱና በነቢያቱ በኩል ለሕዝቡ ተናግሮ ነበር፡፡ ነገር ግን ከዚያ በኃላ ለእነርሱ ሳይነገራቸው 400 ዓመታት አለፉ፡፡ አንድ ቀን በድንገት አንድ መልአክ ዘካርያስ ተብሎ ወደሚጠራ ሽማግሌ ካህን ከእግዚአብሔር ዘንድ መልእክት ይዞ መጣ፡፡ ዘካርያስና ሚስቱ ኤልሳቤጥ እግዚአብሔርን የሚፈሩ ሰዎች ነበሩ፣ ነገር ግን እርስዋ ልጆችን አልወለደችም ነበር፡፡

መልአኩ ዘካርያስን አለው፣ ‹‹ሚስትህ ወንድ ልጅ ትወልዳለች።ስሙንም ዮሐንስ ብለህ ተጠራዋለህ፤ እርሱ በመንፈስ ቅዱስ ይሞላል፣ ሕዝቡንም ለመሲሑ ያዘጋጃል!›› ዘካርያስ፣ ‹‹ሚስቴና እኔ ልጆችን ለመውለድ በጣም አርጅተናል! ይህ እንደሚሆን እንዴት ዐውቃለሁ?›› ብሎ መለሰ።

መልአኩ ለዘካርያስ እንዲህ ብሎ መለሰለት፣ “ይህን የምሥራች እንዳመጣላችሁ እግዚአብሔር ላከኝ፡፡ አንተ ስላላመንከኝ፣ ልጁ እስኪወለድ ድረስ መናገር አትችልም፡፡” ወዲያውኑ ዘካርያስ መናገር አልቻለም፡፡ ከዚያ በኋላ መልአኩ ከዘካርያስ ተለየ፡፡ ዘካርያስም ወደ ቤት ተመለሰ፤ ሚስቱም ፀነሰች፡፡

ኤልሳቤጥ የስድስት ወር ነፍሰ ጡር በነበረች ጊዜ፣ ያው መልአክ በድንገት ስምዋ ማርያም ለተባለ ለኤልሳቤጥ ዘመድ ተገለጠ። እርስዋ ድንግል ነበረችና ልታገባ ዮሴፍ ለተባለ ሰው ታጭታ ነበር። መልአኩ፣ ‹‹ትፀንሻለሽ፤ ወንድ ልጅም ትወልጃለሽ። ስሙንም ኢየሱስ ትዪዋለሽ። እርሱም የልዑል እግዚአብሔር ልጅ ይባላል፤ ለዘላለምም ገዥ ይሆናል›› አለ።

ማርያም‹‹እኔ ድንግል ስለ ሆንኩ፣ ይህ እንዴት ይሆናል?›› ብላ መለሰች። መልአኩ እንዲህ ብሎ አብራራ፣ ‹‹መንፈስ ቅዱስ ወደ አንቺ ይመጣል፣ የልዑል እግዚዘብሔር ኃይል ይጸልልሻል። ስለዚህ ልጁ ቅዱስ የእግዚአብሔር ልጅ ይሆናል።›› ማርያምም አመነች፤ መልአኩ ያለውንም ተቀበለች።

መልአኩ ለማርያም ከተናገረ በኋላ ወዲያወኑ ሄደችና ኤልሳቤጥን ጐበኘቻት። ኤልሳቤጥ የማርያምን ሰላምታ እንደ ሰማች፣ የኤልሳቤጥ ልጅ በሆዷ ውስጥ ዘለለ። ሴቶቹ እግዚአብሔር ስላደረገላቸው ነገር አብረው ሐሤት አደረጉ። ማርያም ኤልሳቤጥን ለሦስት ወራት ከጐበኘቻት በኋላ፣ ወደ ቤትዋ ተመለሰች።

ኤልሳቤጥ ወንድ ልጅዋን ከወለደች በኋላ፣ ዘካርያስና ኤልሳቤጥ መልአኩ እንዳዘዘው ሕፃኑን ዮሐንስ ብለው ሰየሙት፡፡ በዚያን ጊዜ እግዚአብሔር ዘካርያስ እንደ ገና እንዲናገር ፈቀደለት፡፡ ዘካርያስ እንዲህ አለ፣ ‹‹ሕዝቡን ዐስቦአልና እግዚአብሔር ይመስገን! አንተም ልጄ፣ ለኃጢአታቸው ይቅርታ መቀበል እንዴት እንደሚችሉ ለሕዝቡ የምትናገር የልዑል እግዚአብሔር ነቢይ ትባላለህ!››
የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከሉቃስ 1፡፡