27.የደጉ ሳምራዊ ታሪክ

አንድ ቀን አንድ የአይሁድ ሕግ ዐዋቂ ሊፈትነው ወደ ኢየሱስ መጣ፣ ‹‹መምህር ሆይ፣ የዘላለምን ሕይወት እንድወርስ ምን ላድርግ?›› አለው፡፡ ኢየሱስ፣ ‹‹በእግዚአብሔር ሕግ የተጻፈው ምንድን ነው?›› ብሎ መለሰለት፡፡

ሕግ ዐዋቂውም ‹‹የእግዚአብሔር ሕግ፣ ጌታ አምላክህን በፍጹም ልብህ በፍጹም ነፍስህም በፍጹም ኃይልህም በፍጹም ዐሳብህም ውደድ። ባልንጀራህንም እንደ ራስህ ውደድ›› ይላል ብሎ መለሰ። ኢየሱስ፣ ‹‹ትክክል ነህ! ይህን አድርግ በሕይወትም ትኖራለህ›› አለው።

ነገር ግን ሕግ ዐዋቂው ጻድቅ መሆኑን ለማረጋገጥ ፈለገ፣ ስለዚህ፣ ‹‹ባልንጀራዬ ማን ነው?›› ብሎ ጠየቀ፡፡

ኢየሱስ ምሳሌ በመናገር ለሕግ ዐዋቂው መለሰለት። ‹‹ከኢየሩሳሌም ወደ ኢያሪኮ ይጓዝ የነበረ አንድ አይሁዳዊ ነበረ።››

‹‹ሰውዬው በመጓዝ ላይ እያለ ወንበዴዎች አጠቁት፡፡ ያለውን ነገር ሁሉ ወሰዱበትና እጅግ ደበደቡት፡፡ በሞት አፋፍም ጥለውት ሄዱ፡፡››

ከዚያ በኋላ ብዙም ሳይቆይ አንድ አይሁዳዊ ካህን በዚያም መንገድ ይጓዝ ነበር፡፡ ይህ የሃይማኖት መሪ የተዘረፈውንና የተደበደበውን ሰው ባየ ጊዜ መንገዱን ቀይሮ ሳይረዳው ትቶት ሄደ።››

ከዚያ በኋላ ብዙም ሳይቆይ፣ አንድ ሌዋዊ መጣ፡፡ (ሌዋውያን በቤተ መቅደስ ካህናቱን የሚረዱ የአይሁድ ነገድ ነበሩ፡፡) ሌዋዊውም ደግሞ እንዳይረዳው መንገዱን ቀይሮ የተዘረፈውንና የተደበደበውን ሰው ችላ ብሎ ትቶት ሄደ፡፡››

በዚያ መንገድ የወረደው የሚቀጥለው ሰው ሳምራዊ ነበር፡፡ (ሳምራውያን የሌሎች አገሮች ሰዎችን ያገቡ የአይሁድ ዝርያዎች ነበሩ፡፡ ሳምራውያንና አይሁዳውያን አይዋደዱም ነበር፡፡) ነገር ግን ሳምራዊው አይሁዳዊውን ባየ ጊዜ በጣም አድርጎ ራራለት፡፡ ስለዚህ ተንከባከበውና ቊስሉን አሰረለት፡፡››

‹‹ከዚያ በኋላ ሳምራዊው ሰውዬውን አንሥቶ በራሱ አህያ ላይ አስቀምጦት ወደ እንግዶች ማደሪያ ወሰደው ተንከባከበውም፡፡››

‹‹በማግሥቱም ሳምራዊው ጕዞውን መቀጠል ግድ ሆነበት፡፡ ለእንግዶች ማረፊያ ኃላፊ ገንዘብ ሰጠውና፣ ‹‹እባክህ ተንከባከበው፣ ከዚህ ሌላ ገንዘብ የምታወጣ ከሆነ በምመለስበት ጊዜ እከፍልሃለሁ›› አለው፡፡

ኢየሱስም ሕግ ዐዋቂውን፣ ‹‹ምን ታስባለህ? ለተዘረፈውና ለተደበደበው ሰው ባልንጀራው ከሦስቱ ሰዎች የትኛው ነበር?›› ብሎ ጠየቀው፡፡ እርሱም፣ ‹‹ምሕረት ያደረገለት ነበር›› ብሎ መለሰለት፡፡ ኢየሱስ፣ ‹‹አንተም ሄደህ እንደዚሁ አድርግ›› ብሎ ነገረው፡፡
የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ፡- ከሉቃስ 10፡25-37፡፡